መዝሙረ ዳዊት (Psalms)

እሱ ተከታታይ ጅማሬዎችን ያሳያል – የዓለም መጀመሪያ ፣ የሰው ልጅ እና እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የገባውን ቃል ኪዳን። የመጀመሪያው መጽሐፍ ዘፍጥረት በእግዚአብሔር ዓለም ፍጥረት ተከፈተ። የሰው ልጅ እግዚአብሔርን ባለመታዘዙ የሰው ልጅ ብዛት ወደ ተለያዩ ብሔሮች እና ቋንቋዎች ሲከፋፈል ፍጹምው ዓለም በክፋት ውስጥ ይወድቃል።

መጽሐፍ ቅዱስን በየቀኑ ያንብቡ

መዝሙረ ዳዊት (Psalms)

1 ምስጉን ነው በክፉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ።
2 ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለዋል፥ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል።
3 እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።
4 ክፉዎች እንዲህ አይደሉም፥ ነገር ግን ነፋስ ጠርጎ እንደሚወስደው ትቢያ ናቸው።
5 ስለዚህ ክፉዎች በፍርድ፥ ኃጢአተኞችም በጻድቃን ማኅበር አይቆሙም።
6 እግዚአብሔር የጻድቃንን መንገድ ያውቃልና፥ የክፉዎች መንገድ ግን ትጠፋለች።
1 አሕዛብ ለምን ያጕረመርማሉ? ወገኖችስ ለምን ከንቱን ይናገራሉ?
2 የምድር ነገሥታት ተነሡ፥ አለቆችም በእግዚአብሔርና በመሢሑ ላይ እንዲህ ሲሉ ተማከሩ።
3 ማሰርያቸውን እንበጥስ፥ ገመዳቸውንም ከእኛ እንጣል።
4 በሰማይ የሚኖር እርሱ ይሥቃል፥ ጌታም ይሣለቅባቸዋል።
5 በዚያን ጊዜ በቍጣው ይናገራቸዋል፥ በመዓቱም ያውካቸዋል።
6 እኔ ግን ንጉሤን ሾምሁ በተቀደሰው ተራራዬ በጽዮን ላይ።
7 ትእዛዙን እናገራለሁ፤ እግዚአብሔር አለኝ። አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ።
8 ለምነኝ፥ አሕዛብን ለርስትህ የምድርንም ዳርቻ ለግዛትህ እሰጥሃለሁ።
9 በብረት በትር ትጠብቃቸዋለህ፥ እንደ ሸክላ ሠሪ ዕቃዎች ትቀጠቅጣቸዋለህ።
10 አሁንም እናንት ነገሥታት፥ ልብ አድርጉ፤ እናንት የምድር ፈራጆችም፥ ተገሠጹ።
11 ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ፥ በረዓድም ደስ ይበላችሁ።
12 ተግሣጹን ተቀበሉ ጌታ እንዳይቈጣ እናንተም በመንገድ እንዳትጠፉ፥ ቍጣው ፈጥና ትነድዳለችና። በእርሱ የታመኑ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው።

ከልጁ ከአቤሴሎም ፊት በሸሸ ጊዜ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ! በኔ ላይ የሚቆሙት ብዙ ናቸው።
2 ብዙ ሰዎች ነፍሴን። አምላክሽ አያድንሽም አልዋት።
3 አንተ ግን አቤቱ፥ መጠጊያዬ ነህ፥ ክብሬንና ራሴንም ከፍ ከፍ የምታደርገው አንተ ነህ።
4 በቃሌ ወደ እግዚአብሔር እጮሃለሁ ከተቀደሰ ተራራውም ይሰማኛል።
5 እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም፤ እግዚአብሔርም ደግፎኛልና ነቃሁ።
6 ከሚከብቡኝ ከአእላፍ ሕዝብ አልፈራም።
7 ተነሥ፥ አቤቱ፤ አምላኬ ሆይ፥ አድነኝ፤ አንተ የጠላቶቼን መንጋጋ መትተሃልና፥ የክፉዎችንም ጥርስ ሰብረሃልና።
8 ማዳን የእግዚአብሔር ነው፥ በረከትህም በሕዝብህ ላይ ነው።

1 ለመዘምራን አለቃ በበገናዎች፤ የዳዊት መዝሙር።
የጽድቄ አምላክ በጠራሁት ጊዜ መለሰልኝ፥ በጭንቀቴም አሰፋህልኝ፤ ማረኝ፥ ጸሎቴንም ስማ።
2 እናንት የሰው ልጆች፥ እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ?
3 እግዚአብሔር በጻድቁ እንደ ተገለጠ እወቁ፤ እግዚአብሔር ወደ እርሱ በተጣራሁ ጊዜ ይሰማኛል።
4 ተቈጡ፥ ነገር ግን ኃጢአትን አታድርጉ፤ በመኝታችሁ ሳላችሁ በልባችሁ አስቡ፤ ዝም በሉ።
5 የጽድቅን መሥዋዕት ሠዉ፥ በእግዚአብሔርም ታመኑ።
6 በጎውን ማን ያሳየናል? የሚሉ ብዙ ናቸው። አቤቱ፥ የፊትህ ብርሃን በላያችን ታወቀ።
7 በልቤ ደስታን ጨመርህ፤ ከስንዴ ፍሬና ከወይን ከዘይትም ይልቅ በዛ።
8 በሰላም እተኛለሁ አንቀላፋለሁም፤ አቤቱ፥ አንተ ብቻህን በእምነት አሳድረኸኛልና።
ለመዘምራን አለቃ በዋሽንት፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ቃሌን አድምጥ፥ ጩኸቴንም አስተውል፤
2 የልመናዬን ቃል አድምጥ፥ ንጉሤና አምላኬ ሆይ፥ አቤቱ፥ ወደ አንተ እጸልያለሁና።
3 በማለዳ ድምፄን ትሰማለህ፥ በማለዳ በፊትህ እቆማለሁ፥ እጠብቃለሁም።
4 አንተ በደልን የማትወድድ አምላክ ነህና፤ ክፉ ከአንተ ጋር አያድርም።
5 በከንቱ የሚመኩ በዓይኖችህ ፊት አይኖሩም፤ ክፉ አድራጊዎችን ሁሉ ጠላህ።
6 ሐሰትን የሚናገሩትን ታጠፋቸዋለህ፤ ደም አፍሳሹንና ሸንጋዩን ሰው እግዚአብሔር ይጸየፋል።
7 እኔ ግን በምሕረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ፤ አንተን በመፍራት ወደ ቅድስናህ መቅደስ እሰግዳለሁ።
8 አቤቱ፥ ስለ ጠላቶቼ በጽድቅህ ምራኝ፤ መንገዴን በፊትህ አቅና።
9 በአፋቸው እውነት የለምና፥ ልባቸውም ከንቱ ነው፤ ጕሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው፤ በምላሳቸው ይሸነግላሉ።
10 አቤቱ፥ ፍረድባቸው፥ በምክራቸውም ይውደቁ፤ ስለ ክፋታቸውም ብዛት አሳድዳቸው፥ እነርሱ ዐምፀውብሃልና።
11 በአንተ የሚታመኑት ሁሉ ግን ደስ ይላቸዋል፤ ለዘላለሙ ደስ ይላቸዋል፥ እነርሱንም ትጠብቃለህ፤ ስምህንም የሚወድዱ ሁሉ በአንተ ይመካሉ።
12 አንተ ጻድቁን ትባርከዋለህና፤ አቤቱ፥ እንደ ጋሻ በሞገስ ከለልኸን።
ለመዘምራን አለቃ በበገናዎች ስለ ስምንተኛ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።
2 ድውይ ነኝና አቤቱ፥ ማረኝ፤ አጥንቶቼ ታውከዋልና ፈውሰኝ።
3 ነፍሴም እጅግ ታወከች፤ አንተም አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ነው?
4 አቤቱ፥ ተመለስ ነፍሴንም አድናት፥ ስለ ቸርነትህም አድነኝ።
5 በሞት የሚያስብህ የለምና፥ በሲኦልም የሚያመሰግንህ ማን ነው?
6 በጭንቀቴ ደክሜያለሁ፤ ሌሊቱን ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ፥ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ።
7 ዓይኔ ከቍጡ ዕንባ የተነሣ ታወከች፤ ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ።
8 ዓመፃን የምታደርጉ ሁሉ፥ ከእኔ ራቁ፥ እግዚአብሔር የልቅሶዬን ቃል ሰምቶአልና።
9 እግዚአብሔር ልመናዬን ሰማኝ፤ እግዚአብሔር ጸሎቴን ተቀበለ።
10 ጠላቶቼ ሁሉ ይፈሩ እጅግም ይጐስቍሉ፤ ወደ ኋላቸው ይመለሱ፥ በፍጥነትም ይፈሩ።

1 አቤቱ አምላኬ፥ በአንተ ታመንሁ፤ ከሚያሳድዱኝ ሁሉ አድነኝና አውጣኝ፥
2 ነፍሴን እንደ አንበሳ ነጥቀው እንዳይሰብሩዋት፥ የሚያድንና የሚታደግ ሳይኖር።
3 አቤቱ አምላኬ፥ እንዲህስ ካደረግሁ፥ ዓመፃም በእጄ ቢኖር፥
4 ክፉ ላደረጉብኝም ክፉን መልሼላቸው ብሆን፥ ጠላቴንም በከንቱ ገፍቼው ብሆን፥
5 ጠላት ነፍሴን ያሳድዳት ያግኛትም፥ ሕይወቴንም በምድር ላይ ይርገጣት፥ ክብሬንም በትቢያ ላይ ያዋርዳት።
6 አቤቱ፥ በመዓትህ ተነሥ፥ በጠላቶቼ ላይ በቍጣ ተነሣባቸው፤ አቤቱ አምላኬ፥ ባዘዝኸው ትእዛዝ ንቃ።
7 የአሕዛብም ጉባኤ ይከብብሃል፥ በእነርሱም ላይ ወደ ከፍታ ተመለስ።
8 እግዚአብሔር በአሕዛብ ይፈርዳል፤ አቤቱ፥ እንደ ጽድቄ ፍረድልኝ፥ እንደ የዋህነቴም ይሁንልኝ።
9 የኃጥኣን ክፋት ይጥፋ፥ ጻድቁን ግን አቅና፤ እግዚአብሔር ልቡናንና ኵላሊትን ይመረምራል።
10 እግዚአብሔር የጽድቅ ጋሻዬ ነው ልበ ቅኖችን የሚያድናቸው።
11 እግዚአብሔር የእውነት ዳኛ ነው፥ ኃይለኛም ታጋሽም ነው፥ ሁልጊዜም አይቈጣም።
12 ባትመለሱ ግን ሰይፉን ይስላል፥ ቀስቱን ገተረ አዘጋጀም፤
13 የሞት መሣርያንም አዘጋጀበት፥ ፍላጻዎቹንም የሚቃጠሉ አደረገ።
14 እነሆ፥ በዓመፃ ተጨነቀ ጉዳትን ፀነሰ ኃጢአትንም ወለደ።
15 ጕድጓድን ማሰ ቈፈረም። ባደረገውም ጕድጓድ ይወድቃል።
16 ጉዳቱ በራሱ ይመለሳል፥ ዓመፃውም በአናቱ ላይ ትወርዳለች።
17 እግዚአብሔርን እንደ ጽድቁ መጠን አመሰግናለሁ፥ ለልዑል እግዚአብሔርም ስም እዘምራለሁ።

1 ለመዘምራን አለቃ በዋሽንት፤ የዳዊት መዝሙር።
አቤቱ ጌታችን፥ ስምህ በምድር ሁሉ እጅግ ተመሰገነ፥ ምስጋናህ በሰማዮች ላይ ከፍ ከፍ ብሎአልና።
2 ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ፥ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት።
3 የጣቶችህን ሥራ ሰማዮችን ባየሁ ጊዜ፥ ጨረቃንና ከዋክብትን አንተ የሠራሃቸውን፥
4 ታስበው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ትጐበኘውም ዘንድ የሰው ልጅ ምንድር ነው?
5 ከመላእክት እጅግ ጥቂት አሳነስኸው፤ በክብርና በምስጋና ዘውድ ከለልኸው።
6 በእጆችህም ሥራ ሁሉ ላይ ሾምኸው፤ ሁሉን ከእግሮቹ በታች አስገዛህለት፥
7 በጎችንም ላሞችንም ሁሉ ደግሞም የምድረ በዳውን እንስሶች፥
8 የሰማይንም ወፎች የባሕርንም ዓሦች፥ በባሕር መንገድ የሚሄደውንም ሁሉ።
9 አቤቱ ጌታችን፥ ስምህ በምድር ሁሉ እጅግ ተመሰገነ።

1 ለመዘምራን አለቃ፤ በሙትላቤን፤ የዳዊት መዝሙር።
አቤቱ፥ በልቤ ሁሉ አመሰግንሃለሁ፥ ተአምራትህንም ሁሉ እነግራለሁ።
2 በአንተ ደስ ይለኛል፥ ሐሤትንም አደርጋለሁ፤ ልዑል ሆይ፥ ለስምህ እዘምራለሁ።
3 ጠላቶቼ ወደ ኋላ በተመለሱ ጊዜ፥ ይሰናከላሉ ከፊትህም ይጠፋሉ።
4 ፍርዴንና በቀሌን አድርገህልኛልና፤ ጽድቅን እየፈረድህ በዙፋንህ ላይ ተቀመጥህ።
5 አሕዛብን ገሠጽህ፥ ዝንጉዎችንም አጠፋህ፥ ስማቸውንም ለዘላለም ደመሰስህ።
6 ጠላቶች በጦር ለዘላለም ጠፉ፥ ከተሞቻቸውንም አፈረስህ፥ ዝክራቸውም በአንድነት ጠፋ።
7 እግዚአብሔር ግን ለዘላለም ይኖራል፥ ዙፋኑንም ለመፍረድ አዘጋጀ፤
8 እርሱም ዓለምን በጽድቅ ይፈርዳታል፥ አሕዛብንም በቅንነት ይዳኛቸዋል።
9 እግዚአብሔርም ለድሆች መጠጊያ ሆናቸው፥ እርሱም በመከራቸው ጊዜ ረዳታቸው ነው።
10 ስምህን የሚያውቁ ሁሉ በአንተ ይታመናሉ፥ አቤቱ፥ የሚሹህን አትተዋቸውምና።
11 በጽዮን ለሚኖር ለእግዚአብሔር ዘምሩ፥ በአሕዛብም መካከል አደራረጉን ንገሩ፤
12 ደማቸውን የሚመራመር እርሱ አስቦአልና፥ የድሆችንም ጩኸት አልረሳምና።
13 አቤቱ፥ እዘንልኝ፥ ጠላቶቼም የሚያመጡብኝን መከራ እይ፥ ከሞት ደጆች ከፍ ከፍ የምታደርገኝ፤
14 ምስጋናውን ሁሉ እናገር ዘንድ፤ በጽዮን ልጅ በደጆችዋ በማዳንህ ደስ ይለኛል።
15 አሕዛብ በሠሩት ጕድጓድ ወደቁ፥ በዚያችም በሸሸጓት ወጥመድ እግራቸው ተጠመደች።
16 እግዚአብሔር ፍርድን በማድረግ የታወቀ ነው፤ ኃጢአተኛው በእጆቹ ሥራ ተጠመደ።
17 ኃጢአተኞች ወደ ሲኦል ይመለሳሉ፥ እግዚአብሔርን የሚረሱ አሕዛብም ሁሉ።
18 ድሀ ለዘላለም አይረሳምና፥ የችግረኞችም ተስፋቸው ለዘላለም አይጠፋም።
19 አቤቱ፥ ተነሥ፤ ሰውም አይበርታ፥ አሕዛብም በፊትህ ይፈረድባቸው።
20 አቤቱ፥ ፍርሃትን በላያቸው ጫንባቸው፤ አሕዛብ ሰዎች እንደ ሆኑ ይወቁ።

1 አቤቱ፥ ለምን ርቀህ ቆምህ? በመከራም ጊዜ ለምን ትሰወራለህ?
2 በኃጢአተኛ ትዕቢት ድሀ ይናደዳል፤ ባሰቡት ተንኰላቸው ተጠመዱ።
3 ኃጢአተኛ በነፍሱ ፈቃድ ይወደሳልና፥ ዓመፀኛም ይባርካል።
4 ኃጢአተኛ እግዚአብሔርን አበሳጨው፥ እንደ ቍጣውም ብዛት አይመራመረውም በእርሱ ፊት እግዚአብሔር የለም።
5 መንገዱ ሁሉ የረከሰ ነው፥ ፍርድህም በፊቱ የፈረሰ ነው፥ ጠላቶችንም ሁሉ ይገዛቸዋል።
6 በልቡ ይላል። ለልጅ ልጅ አልታወክም ክፉም አያገኘኝም።
7 አፉ መርገምንና ሽንገላን ተንኰልን የተመላ ነው፤ ከምላሱ በታች ጉዳትና መከራ ነው።
8 በመንደሮች መሸመቅያ ይቀመጣል ንጹሓንን በስውር ይገድል ዘንድ፤ ዓይኖቹም ወደ ድኃ ይመለከታሉ።
9 እንደ አንበሳ በችፍግ ዱር በስውር ይሸምቃል፤ ድሀውን ለመንጠቅ ያደባል፤ ድሀውን ይነጥቀዋል በአሽክላውም ይስበዋል።
10 ድሀ ይዋረዳል፥ ይጐብጣል፤ በኃያላኑም እጅግ ይወድቃል።
11 በልቡም ይላል። እግዚአብሔር ረስቶኛል፤ ፈጽሞም እንዳያይ ፊቱን ሰወረ።
12 አቤቱ አምላክ ሆይ፥ ተነሥ እጅህም ከፍ ከፍ ትበል፤ ድሆችን አትርሳ።
13 ኃጢአተኛ ስለ ምን እግዚአብሔርን አስቈጣው? በልቡ። አይመራመረኝም ይላልና።
14 አየኸው፥ አንተ ክፋትንና ቍጣን ትመለከታለህና በእጅህ ፍዳውን ለመስጠት፤ ድሀ ራሱን ለአንተ ይተዋል፥ ለድሀ አደግም ረዳቱ አንተ ነህ።
15 የኃጢአተኛንና የክፉን ክንድ ስበር፥ የኃጢአቱንም ብድራት ክፈል ሌላ እስከማይገኝ ድረስ።
16 እግዚአብሔር ለዘላለም ይነግሣል፤ አሕዛብ ከምድሩ ይጠፋሉ።
17 እግዚአብሔር የድሆችን ምኞት ሰማ፥ ጆሮውም የልባቸውን አሳብ አደመጠች፥
18 ፍርዱ ለድሀ አደግና ለችግረኛ ይደረግ ዘንድ፥ ሰዎች በምድር ላይ አፋቸውን ከፍ ከፍ ማድረግ እንዳይደግሙ።

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 በእግዚአብሔር ታመንሁ፤ ነፍሴን። እንደ ወፍ ወደ ተራሮች ተቅበዝበዢ እንዴት ትሉአታላችሁ?
2 ኃጢአተኞች እነሆ ቀስታቸውን ገትረዋልና፥ ፍላጻቸውንም በአውታር አዘጋጅተዋልና፥ ልበ ቅኖችን በስውር ይነድፉ ዘንድ።
3 አንተ የሠራኸውን እነሆ እነርሱ አፍርሰዋልና፤ ጻድቅ ግን ምን አደረገ?
4 እግዚአብሔር በተቀደሰው መቅደሱ ነው፤ እግዚአብሔር፥ ዙፋኑ በሰማይ ነው፤ ዓይኖቹ ወደ ድሃ ይመለከታሉ፥ ቅንድቦቹም የሰው ልጆችን ይመረምራሉ።
5 እግዚአብሔር ጻድቅንና ኅጥእን ይመረምራል፤ ዓመፃን የወደዳት ግን ነፍሱን ጠልቶአል።
6 ወጥመድ በኅጥኣን ላይ ያዘንባል እሳትና ዲን ዐውሎ ነፋስም የጽዋቸው እድል ፈንታ ነው።
7 እግዚአብሔር ጻድቅ ነውና፥ ጽድቅንም ይወድዳል፤ ቅንነት ግን ፊቱን ታየዋለች።
ለመዘምራን አለቃ፥ ስለ ስምንተኛ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ አድነኝ፤ ደግ ሰው አልቆአልና፥ ከሰው ልጆችም መተማመን ጐድሎአልና።
2 እርስ በርሳቸው ከንቱ ነገርን ይናገራሉ፤ በሽንገላ ከንፈር ሁለት ልብ ሆነው ይናገራሉ።
3 የሽንገላን ከንፈሮች ሁሉ እግዚአብሔር ያጠፋቸዋል፥ ታላቅ ነገርን የምትናገረውን ምላስ፤
4 ምላሳችንን እናበረታለን፤ ከንፈራችን የእኛ ነው፥ ጌታችን ማን ነው? የሚሉትን።
5 ስለ ድሆች መከራ፥ ስለ ችግረኞች ጩኸት እግዚአብሔር። አሁን እነሣለሁ ይላል፤ መድኃኒትን አደርጋለሁ፥ በላዩም እገልጣለሁ።
6 በምድር ላይ እንደ ተፈተነ ሰባት ጊዜ እንደ ተጣራ ብር። የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው።
7 አቤቱ፥ አንተ ጠብቀን፥ ከዚህችም ትውልድ ለዘላለም ታደገን።
8 በሰው ልጆች ዘንድ ምናምንቴ ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ክፉዎች በዙሪያው ሁሉ ይመላለሳሉ።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እስከ መቼ ፈጽመህ ትረሳኛለህ? እስከ መቼስ ፊትህን ከእኔ ትሰውራለህ?
2 እስከ መቼ በነፍሴ እመካከራለሁ? ትካዜስ እስከ መቼ ሁልጊዜ ይሆናል? እስከ መቼ ጠላቴ በላዬ ይጓደዳል?
3 አቤቱ አምላኬ፥ እየኝ ስማኝም፤ ጠላቴ። አሸነፍሁት እንዳይል፥
4 የሚያስጨንቁኝም እኔ ብናወጥ ደስ እንዳይላቸው፥ ለሞትም እንዳልተኛ ዓይኖቼን አብራ።
5 እኔ ግን በቸርነትህ ታመንሁ፥ ልቤም በመድኃኒትህ ደስ ይለዋል።
6 የረዳኝን እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፥ ለልዑል እግዚአብሔር ስምም እዘምራለሁ።
1 ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
ሰነፍ በልቡ። አምላክ የለም ይላል። በሥራቸው ረከሱ፥ ጐስቈሉ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም።
2 የሚያስተውል እግዚአብሔርንም የሚፈልግ እንዳለ ያይ ዘንድ፤ እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ።
3 ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም።
4 ጕሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው፥ በምላሳቸው ሸነገሉ፤
5 ከከንፈራቸው በታች የእባብ መርዝ አለ፤ አፋቸው መርገምንና መራራን ተሞልቶአል፤
6 ደምን ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው፤ ጥፋትና ጕስቍልና በመንገዳቸው አለ፥ የሰላምን መንገድ አላወቁአትምና፤ እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም።
7 ሕዝቤን እንደ እንጀራ የሚበሉ ኃጢአት የሚሠሩ ሁሉ በውኑ አያውቁምን? እግዚአብሔርንም አይጠሩትም።
[8] በዚያ በታላቅ ፍርሃት እጅግ ፈሩ፥ እግዚአብሔር በጻድቃን ትውልድ ዘንድ ነውና።
[9] የድሆችን ምክር አሳፈራችሁ፥ እግዚአብሔር ግን ተስፋቸው ነው።
[10] ከጽዮን መድኃኒትን ለእስራኤል ማን ይሰጣል? እግዚአብሔር የሕዝቡን ምርኮ በመለሰ ጊዜ፥ ያዕቆብ ደስ ይለዋል፥ እስራኤልም ሐሤት ያደርጋል።

1 አቤቱ፥ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል? በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል?
2 በቅንነት የሚሄድ፥ ጽድቅንም የሚያደርግ፥ በልቡም እውነትን የሚናገር።
3 በአንደበቱ የማይሸነግል፥ በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ፥ ዘመዶቹንም የማይሰድብ።
4 ኃጢአተኛ በፊቱ የተናቀ፥ እግዚአብሔርንም የሚፈሩትን የሚያከብር፥ ለባልንጀራው የሚምል የማይከዳም።
5 ገንዘቡን በአራጣ የማያበድር፥ በንጹሑ ላይ መማለጃን የማይቀበል። እንዲህ የሚያደርግ ለዘላለም አይታወክም።

የዳዊት ቅኔ።
1 አቤቱ፥ በአንተ ታምኛለሁና ጠብቀኝ።
2 እግዚአብሔርን። አንተ ጌታዬ ነህ አልሁ፤ ከአንተ በቀር በጎነት የለኝም።
3 ፈቃድህ ሁሉ በምድር ባሉት ቅዱሳንና ክቡራን ላይ ነው።
4 ወደ ሌላ ለሚፋጠኑት መከራቸው ይበዛል፤ የቍርባናቸውን ደም እኔ አላፈስሰውም፥ ስማቸውንም በከንፈሬ አልጠራም።
5 እግዚአብሔር የርስቴ እድል ፈንታና ጽዋዬ ነው፥ ዕጣዬንም የምታጠና አንተ ነህ።
6 ገመድ ባማረ ስፍራ ወደቀችልኝ፥ ርስቴም ተዋበችልኝ።
7 የመከረኝን እግዚአብሔርን እባርካለሁ፤ ደግሞም በሌሊት ኵላሊቶቼ ይገሥጹኛል።
8 ሁልጊዜ እግዚአብሔርን በፊቴ አየዋለሁ፤ በቀኜ ነውና አልታወክም።
9 ስለዚህ ልቤን ደስ አለው ምላሴም ሐሴት አደረገች፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋ ታድራለች፤
10 ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተወውም።
11 የሕይወትን መንገድ አሳየኸኝ፤ ከፊትህ ጋር ደስታን አጠገብኸኝ፥ በቀኝህም የዘላለም ፍሥሐ አለ።
የዳዊት ጸሎት።
1 አቤቱ፥ ጽድቄን ስማ ጩኸቴንም አድምጥ፤ በተንኰለኛም ከንፈር ያልሆነውን ጸሎቴን አድምጥ።
2 ፍርዴ ከፊትህ ይውጣ፥ ዓይኖችህም በቅንነት ይዩ።
3 ልቤን ፈተንኸው በሌሊትም ጐበኘኸኝ፤ ፈተንኸኝ፥ ምንም አላገኘህብኝም።
4 የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፤ ስለ ከንፈሮችህ ቃል ጭንቅ የሆኑ መንገዶችን ጠበቅሁ።
5 እግሮች እንዳይናወጡ አረማመዴን በመንገድህ አጽና።
6 አቤቱ፥ ሰምተኸኛልና ወደ አንተ ጠራሁ፤ ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል፥ ቃሌንም ስማ።
7 የሚያምኑህን ከሚቃወሙ በቀኝህ የምታድናቸው፥ ቸርነትህን ድንቅ አድርገህ ግለጠው።
8 እንደ ዓይን ብሌን ጠብቀኝ፥ በክንፎችህ ጥላ ሰውረኝ፥
9 ከሚያስጨንቁኝ ከኃጢአተኞች፥ ነፍሴንም ከሚከብቡአት ከጠላቶቼ።
10 አንጀታቸውን በስብ ቋጠሩ፥ በአፋቸውም ትንቢትን ተናገሩ።
11 አሁንም እርምጃችንን ከበቡ፤ ዓይናቸውን ወደ ምድር ዝቅ ዝቅ አደረጉ።
12 እርሱ ንጥቂያን እንደሚናፍቅ አንበሳ ተሸጕጦም እንደሚኖር እንደ አንበሳ ደቦል ነው።
13 አቤቱ፥ ተነሥ፤ ቀድመህ ወደ ታች ጣለው፤ ነፍሴን ከኃጢአተኛ በሰይፍህ አድናት።
14 አቤቱ፥ ከሰዎች፥ እድል ፈንታቸው በሕይወታቸው ከሆነች ከዚህ ዓለም ሰዎች በእጅህ አድነኝ፤ ከሰወርኸው መዝገብህ ሆዳቸውን አጠገብህ፤ ልጆቻቸው ብዙ ናቸው የተረፋቸውንም ለሕፃናቶቻቸው ያተርፋሉ።
15 እኔ ግን በጽድቅ ፊትህን አያለሁ፤ ክብርህን ሳይ እጠግባለሁ።

ለመዘምራን አለቃ ከሳኦል እጅና ከጠላቶቹ ሁሉ እጅ እግዚአብሔር ባዳነው ቀን በዚህ መዝሙር ቃል ለእግዚአብሔር የተናገረው የእግዚአብሔር ባሪያ የዳዊት መዝሙር። እንዲህም አለ።
1 አቤቱ ጕልበቴ ሆይ፥ እወድድሃለሁ።
2 እግዚአብሔር ዓለቴ፥ አምባዬ፥ መድኃኒቴ፥ አምላኬ፥ በእርሱም የምተማመንበት ረዳቴ፥ መታመኛዬና የደኅንነቴ ቀንድ መጠጊያዬም ነው።
3 ምስጋና የሚገባውን እግዚአብሔርን እጠራለሁ፥ ከጠላቶቼም እድናለሁ።
4 የሞት ጣር ያዘኝ፥ የዓመፅ ፈሳሽም አስፈራኝ፤
5 የሲኦል ጣር ከበበኝ፤ የሞት ወጥመድም ደረሰብኝ።
6 በጨነቀኝ ጊዜ እግዚአብሔርን ጠራሁት፥ ወደ አምላኬም ጮኽሁ፤ ከመቅደሱም ቃሌን ሰማኝ፥ ጩኸቴም በፊቱ ወደ ጆሮው ገባ።
7 ምድርም ተንቀጠቀጠች ተናወጠችም፥ የተራሮችም መሠረቶች ተነቃነቁ፥ እግዚአብሔርም ተቈጥቶአልና ተንቀጠቀጡ።
8 ከቍጣው ጢስ ወጣ፥ ከፊቱም የሚበላ እሳት ነደደ፤ ፍምም ከእርሱ በራ።
9 ሰማዮችን ዝቅ ዝቅ አደረገ ወረደም፥ ጨለማ ከእግሩ በታች ነበረ።
10 በኪሩቤልም ላይ ተቀምጦ በረረ፥ በነፋስም ክንፍ በረረ።
11 መሰወሪያውን ጨለማ አደረገ፤ በዙሪያውም ድንኳኑ፤ በደመናት ውስጥ የጨለማ ውኃ ነበረ።
12 በፊቱ ካለው ብርሃን የተነሣ ደመናትና በረዶ የእሳት ፍምም አለፉ።
13 እግዚአብሔርም ከሰማያት አንጐደጐደ፥ ልዑልም ቃሉን ሰጠ።
14 ፍላጻውን ላከ በተናቸውም፤ መብረቆችን አበዛ አወካቸውም።
15 አቤቱ፥ ከዘለፋህ ከመዓትህም መንፈስ እስትንፋስ የተነሣ፥ የውኆች ምንጮች ታዩ፥ የዓለም መሠረቶችም ተገለጡ።
16 ከላይ ሰደደ ወሰደኝም፥ ከብዙ ውኆችም አወጣኝ።
17 ከብርቱዎች ጠላቶቼ ከሚጠሉኝም አዳነኝ፥ በርትተውብኝ ነበርና።
18 በመከራዬ ቀን ደረሱብኝ፤ እግዚአብሔር ግን ደገፋዬ ሆነ።
19 ወደ ሰፊ ስፍራም አወጣኝ፤ ወድዶኛልና አዳነኝ።
20 እግዚአብሔር እንደ ጽድቄ ይከፍለኛል፤ እንደ እጄ ንጽሕና ይመልስልኛል።
21 የእግዚአብሔርን መንገድ ጠብቄአለሁና፥ በአምላኬም አላመፅሁም።
22 ፍርዱ ሁሉ በፊቴ ነበረና፥ ሥርዓቱንም ከፊቴ አላራቅሁም።
23 በእርሱ ዘንድ ቅን ነበርሁ፥ ከኃጢአቴም ተጠበቅሁ።
24 እግዚአብሔርም እንደ ጽድቄ እንደ እጄም ንጽሕና በዓይኖቹ ፊት መለሰልኝ።
25 ከቸር ሰው ጋር ቸር ሆነህ ትገኛለህ፤ ከቅን ሰው ጋር ቅን ሆነህ ትገኛለህ፤
26 ከንጹሕ ጋር ንጹሕ ሆነህ ትገኛለህ፤ ከጠማማም ጋር ጠማማ ሆነህ ትገኛለህ።
27 አንተ የተጠቃውን ሕዝብ ታድናለህና፥ የትዕቢተኞችን ዓይን ግን ታዋርዳለህ።
28 አንተ መብራቴን ታበራለህና፤ እግዚአብሔር አምላኬ ጨለማዬን ያበራል።
29 በአንተ ከጥፋት እድናለሁና በአምላኬም ቅጥሩን እዘልላለሁ።
30 የአምላኬ መንገድ ፍጹም ነው፥ የእግዚአብሔር ቃል የነጠረ ነው፥ በእርሱ ለሚታመኑት ሁሉ ጋሻ ነው።
31 ከእግዚአብሔር በቀር አምላክ ማን ነው? ከአምላካችን በቀር አምላክ ማን ነው?
32 ኃይልን የሚያስታጥቀኝ መንገዴንም የሚያቃና፥
33 እግሮቼን እንደ ብሖር እግሮች የሚያረታ በኮረብቶችም የሚያቆመኝ እግዚአብሔር ነው።
34 እጆቼን ሰልፍ ያስተምራል፥ በክንዴም የናስ ቀስት እገትራለሁ።
35 ለደኅንነቴም መታመኛን ሰጠኸኝ፥ ቀኝህም ትረዳኛለች፥ ትምህርትህም ለዘላለም ታጠናኛለች፥ ተግሣጽህም ታስተምረኛለች።
36 አረማመዴን በበታቼ አሰፋህ፥ እግሮቼም አልተንሸራተቱም።
37 ጠላቶቼን አሳድዳቸዋለሁ እይዛቸዋለሁም፥ እስካጠፋቸውም ድረስ አልመለስም።
38 አስጨንቃቸዋለሁ መቆምም አይችሉም፥ ከእግሬም በታች ይወድቃሉ።
39 ለሰልፍም ኃይልን ታስታጥቀኛለህ፤ በበላዬ የቆሙትን ሁሉ በበታቼ ታስገዛቸዋለህ።
40 የጠላቶቼን ጀርባ ሰጠኸኝ፥ የሚጠሉኝንም አጠፋሃቸው።
41 ጮኹ የሚረዳቸውም አልነበረም፤ ወደ እግዚአብሔርም ጮኹ አልሰማቸውም።
42 እንደ ትቢያ በነፋስ ፊት እፈጫቸዋለሁ፥ እንደ አደባባይም ጭቃ እረግጣቸዋለሁ።
43 ከሕዝብ ክርክር ታድነኛለህ፥ የአሕዛብም ራስ አድርገህ ትሾመኛለህ፥ የማላውቀው ሕዝብም ይገዛልኛል።
44 በጆሮ ሰምተው ተገዙልኝ፤ የባዕድ ልጆች ደለሉኝ።
45 የባዕድ ልጆች አረጁ፥ በመንገዳቸውም ተሰናከሉ።
46 እግዚአብሔር ሕያው ነው፥ አምላኬም ቡሩክ ነው፥ የመድኃኒቴም አምላክ ከፍ ከፍ ይበል።
47 በቀሌን የሚመልስልኝ አምላክ አሕዛብን በበታቼ ያስገዛልኛል።
48 ከጠላቶቼ የሚታደገኝ እርሱ ነው፤ በእኔም ላይ ከቆሙ ከፍ ከፍ ታደርገኛለህ፥ ከግፈኛ ሰው ታድነኛለህ።
49 አቤቱ፥ ስለዚህ በአሕዛብ ዘንድ አመሰግንሃለሁ፥ ለስምህም እዘምራለሁ።
50 የንጉሡን መድኃኒት ታላቅ ያደርጋል፥ ቸርነቱንም ለቀባው ለዳዊትና ለዘሩ ለዘላለም ይሰጣል።

ለመዘምራን አለቃ የዳዊት መዝሙር።
1 ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፥ የሰማይም ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል።
2 ቀን ለቀን ነገርን ታወጣለች፥ ሌሊትም ለሌሊት እውቀትን ትናገራለች።
3 ነገር የለም መናገርም የለም፥ ድምፃቸውም አይሰማም።
4 ድምፃቸው ወደ ምድር ሁሉ፥ ቃላቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ወጣ።
5 በእነርሱም ውስጥ የፀሐይን ድንኳን አደረገ፥ እርሱም እንደ ሙሽራ ከእልፍኙ ይወጣል፤ እንደ አርበኛ በመንገዱ ለመሮጥ ደስ ይለዋል።
6 አወጣጡ ከሰማያት ዳርቻ ነው፥ ዙረቱም እስከ ዳርቻቸው ነው፤ ከትኩሳቱም የሚሰወር የለም።
7 የእግዚአብሔር ሕግ ፍጹም ነው፤ ነፍስን ይመልሳል፤ የእግዚአብሔር ምስክር የታመነ ነው፤ ሕፃናትን ጠቢባን ያደርጋል።
8 የእግዚአብሔር ሥርዓት ቅን ነው፥ ልብንም ደስ ያሰኛል፤ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ብሩህ ነው፥ ዓይንንም ያበራል።
9 የእግዚአብሔር ፍርሃት ንጹሕ ነው፤ ለዘላለም ይኖራል፤ የእግዚአብሔር ፍርድ እውነትና ቅንነት በአንድነት ነው።
10 ከወርቅና ከክቡር ዕንቍ ይልቅ ይወደዳል፤ ከማርና ከማር ወለላም ይጣፍጣል።
11 ባሪያህ ደግሞ ይጠብቀዋል፤ በመጠበቁም እጅግ ይጠቀማል።
12 ስሕተትን ማን ያስተውላታል? ከተሰወረ ኃጢአት አንጻኝ።
13 የድፍረት ኃጢአት እንዳይገዛኝ ባሪያህን ጠብቅ፤ የዚያን ጊዜ ፍጹም እሆናለሁ፥ ከታላቁም ኃጢአት እነጻለሁ።
14 አቤቱ፥ ረድኤቴ መድኃኒቴም፥ የአፌ ቃልና የልቤ አሳብ በፊትህ ያማረ ይሁን።

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 በመከራ ቀን እግዚአብሔር ይስማህ፤ የያዕቆብ አምላክ ስም ያቁምህ።
2 ከመቅደሱ ረድኤትን ይላክልህ፥ ከጽዮንም ያጥናህ።
3 ቍርባንህን ሁሉ ያስብልህ፤ የሚቃጠል መሥዋዕትህን ያለምልምልህ።
4 እንደ ልብህ ይስጥህ ፈቃድህንም ሁሉ ይፈጽምልህ።
5 በማዳንህ ደስ ይለናል፤ በአምላካችን ስም ከፍ ከፍ እንላለን፤ ልመናህን ሁሉ እግዚአብሔር ይፈጽምልህ።
6 እግዚአብሔር የቀባውን እንዳዳነው ዛሬ አወቅሁ፤ ከሰማይ መቅደሱ ይመልስለታል፤ በቀኙ ብርታት ማዳን።
7 እነዚያ በሰረገላ እነዚያም በፈረስ ይታመናሉ፤ እኛ ግን በአምላካችን በእግዚአብሔር ስም ከፍ ከፍ እንላለን።
8 እነርሱ ተሰነካክለው ወደቁ፤ እኛ ግን ተነሣን፥ ጸንተንም ቆምን።
9 አቤቱ፥ ንጉሥን አድነው፥ በጠራንህም ቀን ስማን።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ በኃይልህ ንጉሥ ደስ ይለዋል፤ በማዳንህ እጅግ ሐሤትን ያደርጋል።
2 የልቡን ፈቃድ ሰጠኽው፥ የከንፈሩንም ልመና አልከለከልኸውም።
3 በበጎ በረከት ደርሰህለታልና፤ ከክቡር ዕንቍ የሆነ ዘውድን በራሱ ላይ አኖርህ።
4 ሕይወትን ለመነህ ሰጠኸውም፥ ለረጅም ዘመን ለዘላለሙ።
5 በማዳንህ ክብሩ ታላቅ ነው፤ ክብርንና ምስጋናን ጨመርህለት።
6 የዘላለም በረከትን ሰጥተኸዋልና። በፊትህም ደስታ ደስ ታሰኘዋለህ።
7 ንጉሥ በእግዚአብሔር ተማምኖአልና፥ በልዑልም ምሕረት አይናወጥም።
8 እጅህ ጠላቶችህን ሁሉ ታግኛቸው፥ ቀኝህም የሚጠሉህን ሁሉ ታግኛቸው።
9 በተቈጣህም ጊዜ እንደ እሳት እቶን አድርጋቸው፤ እግዚአብሔር በቍጣው ያጠፋቸዋል፥ እሳትም ትበላቸዋለች።
10 ፍሬአቸውን ከምድር ዘራቸውንም ከሰው ልጆች ታጠፋለህ።
11 ክፋትን በአንተ ላይ ዘርግተዋልና፥ የማይቻላቸውንም ምክር አሰቡ።
12 ወደ ኋላቸው ትመልሳቸዋለህ፤ ፍላጻን በፊታቸው ላይ ታዘጋጃለህ።
13 አቤቱ፥ በኃይልህ ከፍ ከፍ በል፤ ጽናትህንም እናመሰግናለን እንዘምርማለን።
ለመዘምራን አለቃ ስለ ንጋት ኃይል፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አምላኬ፥ አምላኬ፥ ለምን ተውኸኝ? እኔን ከማዳንና ከጩኸቴ ቃል ሩቅ ነህ።
2 አምላኬ፥ በቀን ወደ አንተ እጠራለሁ፥ አልመለስህልኝም፤ በሌሊትም እንኳ ዕረፍት የለኝም።
3 በእስራኤል የተመሰገንህ አንተ ግን በቅድስና ትኖራለህ።
4 አባቶቻችን አንተን ተማመኑ፥ ተማመኑ አንተም አዳንሃቸው።
5 ወደ አንተ ጮኹ አመለጡም፥ አንተንም ተማመኑ አላፈሩም።
6 እኔ ግን ትል ነኝ ሰውም አይደለሁም፤ የሰው ማላገጫ በሕዝብም ዘንድ የተናቅሁ ነኝ።
7 የሚያዩኝ ሁሉ ይላገዱብኛል፤ ራሳቸውን እየነቀነቁ በከንፈሮቻቸው እንዲህ ይላሉ።
8 በእግዚአብሔር ተማመነ፥ እርሱንም ያድነው፤ ቢወድደውስ ያድነው።
9 አንተ ግን ከሆድ አውጥተኸኛልና፥ በእናቴ ጡት ሳለሁም በአንተ ታመንሁ።
10 ከማኅፀን ጀምሮ በአንተ ላይ ተጣልሁ፤ ከእናቴ ሆድ ጀምረህ አንተ አምላኬ ነህ።
11 ጭንቀት ቀርባለችና የሚረዳኝም የለምና ከእኔ አትራቅ።
12 ብዙ በሬዎች ከበቡኝ፥ የሰቡትም ፍሪዳዎች ያዙኝ፤
13 እንደ ነጣቂና እንደሚጮኽ አንበሳ በላዬ አፋቸውን ከፈቱ።
14 እንደ ውኃ ፈሰስሁ፤ አጥንቶቼም ሁሉ ተለያዩ፤ ልቤ እንደ ሰም ሆነ፥ በአንጀቴም መካከል ቀለጠ።
15 ኃይሌ እንደ ገል ደረቀ፥ በጕሮሮዬም ምላሴ ተጣጋ፥ ወደ ሞትም አሸዋ አወረድኸኝ።
16 ብዙ ውሾች ከብበውኛልና፤ የክፋተኞች ጉባኤም ያዘኝ፤ እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ።
17 አጥንቶቼ ሁሉ ተቈጠሩ፤ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም።
18 ልብሶቼን ለራሳቸው ተከፋፈሉ፥ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ።
19 አንተ ግን፥ አቤቱ፥ ከእኔ አትራቅ፤ አንተ ጕልበቴ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።
20 ነፍሴን ከሰይፍ አድናት፥ ብቻነቴንም ከውሾች እጅ።
21 ከአንበሳ አፍ አድነኝ፥ ብቻነቴንም አንድ ቀንድ ካላቸው።
22 ስምህን ለወንድሞቼ እነግራቸዋለሁ፥ በጉባኤም መካከል አመሰግንሃለሁ።
23 እግዚአብሔርን የምትፈሩ፥ አመስግኑት፤ የያዕቆብ ዘር ሁላችሁ፥ አክብሩት፥ የእስራኤልም ዘር ሁላችሁ፥ ፍሩት።
24 የችግረኛን ችግር አልናቀምና፥ ቸልም አላለምና፤ ፊቱንም ከእኔ አልሰወረምና፥ ነገር ግን ወደ እርሱ በጮኽሁ ጊዜ ሰማኝ።
25 በታላቅ ጉባኤ ምስጋናዬ ከአንተ ዘንድ ነው። እርሱን በሚፈሩት ፊት ስእለቴን እሰጣለሁ።
26 ችግረኞች ይበላሉ፥ ይጠግቡማል፤ እግዚአብሔርንም የሚሹት ያመሰግኑታል፤ ልባቸውም ለዘላለም ሕያው ይሆናል።
27 የምድር ዳርቻዎች ሁሉ ያስቡ፥ ወደ እግዚአብሔርም ይመለሱ፤ የአሕዛብ ነገዶች ሁሉ በፊቱ ይሰግዳሉ።
28 መንግሥት ለእግዚአብሔር ነውና፥ እርሱም አሕዛብን ይገዛል።
29 የምድር ደንዳኖች ሁሉ ይበላሉ ይሰግዳሉም፤ ወደ መሬት የሚወርዱት ሁሉ በፊቱ ይንበረከካሉ፤ ነፍሴም ስለ እርሱ በሕይወት ትኖራለች።
30 ዘሬ ይገዛለታል፤ የምትመጣው ትውልድ ለእግዚአብሔር ትነግረዋለች፤
31 ጽድቁንም ለሚወለደው ሕዝብ፥ እግዚአብሔር ያደረገውን ጽድቁን፥ ይነግራሉ።

የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፥ የሚያሳጣኝም የለም።
2 በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል።
3 ነፍሴን መለሳት፥ ስለ ስሙም በጽድቅ መንገድ መራኝ።
4 በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኵዝህ እነርሱ ያጸናኑኛል።
5 በፊቴ ገበታን አዘጋጀህልኝ በጠላቶቼ ፊት ለፊት ራሴን በዘይት ቀባህ፥ ጽዋዬም የተረፈ ነው።
6 ቸርነትህና ምሕረትህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ይከተሉኛል፥ በእግዚአሔርም ቤት ለዘላለም እኖራለሁ።
1 በመጀመሪያ ሰንበት የዳዊት መዝሙር። 1 ምድርና ሞላዋ ለእግዚአብሔር ናት፥ ዓለምም በእርስዋም የሚኖሩ ሁሉ።
2 እርሱ በባሕሮች መሥርቶአታልና፥ በፈሳሾችም አጽንቶአታልና።
3 ወደ እግዚአብሔር ተራራ ማን ይወጣል? በቅድስናውስ ስፍራ ማን ይቆማል?
4 እጆቹ የነጹ፥ ልቡም ንጹሕ የሆነ፥ ነፍሱን ለከንቱ ያላነሣ፥ ለባልንጀራውም በሽንገላ ያልማለ።
5 እርሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ በረከትን ከመድኃኒቱ አምላክም ምሕረትን ይቀበላል።
6 ይህች ትውልድ እርሱን የምትፈልግ ናት፥ የያዕቆብን አምላክ ፊት የምትፈልግ።
7 እናንት መኳንንቶች፥ በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ።
8 ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው? እግዚአብሔር ነው፥ ብርቱና ኃያል፥ እግዚአብሔር ነው፥ በሰልፍ ኃያል።
9 እናንተ መኳንንቶች፥ በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ።
10 ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው? የጭፍሮች አምላክ እግዚአብሔር፥ እርሱ የክብር ንጉሥ ነው።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ወደ አንተ ነፍሴን አነሣለሁ።
2 አምላኬ፥ አንተን ታመንሁ፤ አልፈር፥ ጠላቶቼ በእኔ አይሣቁብኝ።
3 አንተን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም፤ በከንቱ የሚገበዙ ያፍራሉ።
4 አቤቱ፥ መንገድህን አመልክተኝ፥ ፍለጋህንም አስተምረኝ።
5 አንተ የመድኃኒቴ አምላክ ነህና በእውነትህ ምራኝ፥ አስተምረኝም፤ ቀኑን ሁሉ አንተን ተስፋ አድርጌአለሁ።
6 አቤቱ፥ ምሕረትህንና ቸርነትህን አስብ፥ ከጥንት ጀምሮ ናቸውና።
7 የልጅነቴን ኃጢአትና መተላለፍ አታስብብኝ፤ አቤቱ፥ ስለ ቸርነትህ ብዛት እንደ ምሕረትህ አስበኝ።
8 እግዚአብሔር ቸር ቅንም ነው፤ ስለዚህ ኃጢአተኞችን በመንገድ ይመራቸዋል።
9 ገሮችን በፍርድ ይመራል፥ ለገሮችም መንገድን ያስተምራቸዋል።
10 የእግዚአብሔር መንገድ ሁሉ ቸርነትና እውነት ነው። ቃል ኪዳኑንና ምስክሩን ለሚጠብቁ።
11 አቤቱ፥ ኃጢአቴ እጅግ ነውና ስለ ስምህ ይቅር በለኝ።
12 እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ማን ነው? በሚመርጠው መንገድ ያስተምረዋል።
13 ነፍሱ በመልካም ታድራለች፥ ዘሩም ምድርን ይወርሳል።
14 እግዚአብሔር ለሚፈሩት ኃይላቸው ነው፥ ቃል ኪዳኑንም ያስታውቃቸዋል።
15 እርሱ እግሮቼን ከወጥመድ ያወጣቸዋልና ዓይኖቼ ሁልጊዜ ወደ እግዚአብሔር ናቸው።
16 እኔ ብቻዬንና ችግረኛ ነኝና ፊትህን ወደ እኔ አድርግ ማረኝም።
17 የልቤ ችግር ብዙ ነው፤ ከጭንቀቴ አውጣኝ።
18 ድካሜንና መከራዬን እይ፥ ኃጢአቴንም ሁሉ ይቅር በለኝ።
19 ጠላቶቼ እንደ በዙ እይ፥ የግፍም ጥል ጠልተውኛል።
20 ነፍሴን ጠብቅና አድነኝ፤ አንተን ታምኛለሁና አልፈር።
21 አንተን ተስፋ አድርጌአለሁና የውሃትና ቅንነት ይጠብቁኝ።
22 አቤቱ፥ እስራኤልን ከመከራው ሁሉ አድነው።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እኔ በየውሃቴ ሄጃለሁና ፍረድልኝ፤ በእግዚአብሔርም አምኛለሁና አልናወጥም።
2 አቤቱ፥ ፍተነኝ መርምረኝም፤ ኵላሊቴንና ልቤን ፍተን።
3 ምሕረትህ በዓይኔ ፊት ነውና፥ በእውነትህም ተመላለስሁ።
4 በከንቱ ሸንጎ አልተቀመጥሁም፥ ከዓመፀኞችም ጋር አልገባሁም።
5 የክፉዎችን ማኅበር ጠላሁ፥ ከዝንጉዎችም ጋር አልቀመጥም።
6 እጆቼን በንጽሕና አጥባለሁ፤ አቤቱ፥ መሠዊያህን እዞራለሁ፥
7 የምስጋናን ድምፅ እሰማ ዘንድ፥ ተአምራትህንም ሁሉ እነግር ዘንድ።
8 አቤቱ፥ የቤትህን ስፍራ የክብርህንም ማደሪያ ቦታ ወደድሁ።
9 ከኃጢአተኞች ጋር ነፍሴን፥ ከደም ሰዎችም ጋር ሕይወቴን አታጥፋ።
10 በእጃቸው ተንኰል አለባቸው፥ ቀኛቸውም መማለጃ ተሞልታለች።
11 እኔ ግን በየውሃቴ ሄጃለሁ፤ አድነኝ ማረኝም።
12 እግሮቼ በቅንነት ቆመዋልና፤ አቤቱ፥ በማኅበር አመሰግንሃለሁ።

ሳይቀባ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው፤ የሚያስፈራኝ ማን ነው? እግዚአብሔር የሕይወቴ መታመኛዋ ነው፤ የሚያስደነግጠኝ ማን ነው?
2 ክፉዎች፥ አስጨናቂዎቼ ጠላቶቼም፥ ሥጋዬን ይበሉ ዘንድ በቀረቡ ጊዜ፥ እነርሱ ተሰናከሉና ወደቁ።
3 ሠራዊትም ቢሰፍርብኝ ልቤ አይፈራም፤ ሰልፍም ቢነሣብኝ በዚህ እተማመናለሁ።
4 እግዚአብሔርን አንዲት ነገር ለመንሁት እርስዋንም እሻለሁ፤ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ፥ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውንም አይ ዘንድ፥ መቅደሱንም እመለከት ዘንድ።
5 በመከራዬ ቀን በድንኳኑ ሰውሮኛልና፥ በድንኳኑም መሸሸጊያ ሸሽጎኛልና፥ በዓለት ላይ ከፍ ከፍ አድርጎኛልና።
6 እነሆ፥ አሁን በዙሪያ ባሉ በጠላቶቼ ላይ ራሴን ከፍ ከፍ አደረገ፤ በድንኳኑም የእልልታ መሥዋዕትን ሠዋሁ፥ ለእግዚአብሔር እቀኛለሁ እዘምርለትማለሁ።
7 አቤቱ፥ ወደ አንተ የጮኽሁትን ቃሌን ስማኝ። ማረኝና አድምጠኝ።
8 አንተ ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ። አቤቱ፥ ፊትህን እሻለሁ ልቤ አንተን አለ።
9 ፊትህን ከእኔ አትሰውር፥ ተቈጥተህ ከባሪያህ ፈቀቅ አትበል፤ ረዳት ሁነኝ፥ አትጣለኝም፥ የመድኃኒቴም አምላክ ሆይ፥ አትተውኝ።
10 አባቴና እናቴ ትተውኛልና፥ እግዚአብሔር ግን ተቀበለኝ።
11 አቤቱ፥ መንገድህን አስተምረኝ፥ ስለ ጠላቶቼም በቀና መንገድ ምራኝ።
12 የሐሰት ምስክሮችና ዓመፀኞች ተነሥተውብኛልና ለጠላቶቼ ፈቃድ አትስጠኝ።
13 የእግዚአብሔርን ቸርነት በሕያዋን ምድር አይ ዘንድ አምናለሁ።
14 እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ፤ በርታ፥ ልብህም ይጽና፤ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ወደ አንተ እጠራለሁ፤ ዝም ብትለኝ ወደ ጓድጓድ እንደሚወርዱት እንዳልመስል፥ አንተ አምላኬ፥ ዝም አትበለኝ።
2 ወደ መቅደስህ ማደሪያ እጄን ባነሣሁ ጊዜ፥ ወደ አንተ የጮኽሁትን የልመናዬን ቃል ስማ።
3 ከኃጥኣንና ከክፉ አድራጊዎች ጋር ነፍሴን አትውሰዳት፤ ክፋትም በልባቸው እያለ ከባልንጀራቸው ጋር ሰላም ከሚናገሩት ጋር አትጣለኝ።
4 እንደ ሥራቸው እንደ አካሄዳቸውም ክፉት ስጣቸው፤ እንደ እጃቸውም ሥራ ስጣቸው፤ ፍዳቸውን ወደ ራሳቸው መልስ።
5 ወደ እግዚአብሔር ሥራ ወደ እጆቹም አደራረግ አላሰቡምና ያፈርሳቸዋል እንጂ አይሠራቸውም።
6 የልመናዬን ቃል ሰምቶኛልና እግዚአብሔር ይመስገን።
7 እግዚአብሔር ኃይሌና ጋሻዬ ነው፤ ልቤ በእርሱ ታመነ እኔም ተረዳሁ፤ ሥጋዬም ደስ ይለዋል፥ ፈቅጄም አመሰግነዋለሁ።
8 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ኃይላቸው ነው፥ ለቀባውም የመድኃኒቱ መታመኛ ነው።
9 ሕዝብህን አድን፥ ርስትህንም ባርክ፤ ጠብቃቸው፥ ለዘላለሙም ከፍ ከፍ አድርጋቸው።
ከድንኳን በመውጣት ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 የአምላክ ልጆች ሆይ፥ ለእግዚአብሔር አምጡ። ክብርንና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ።
2 የስሙን ክብር ለእግዚአብሔር አምጡ፥ በቅድስናው ስፍራ ለእግዚአብሔር ስገዱ።
3 የእግዚአብሔር ድምፅ በውኆች ላይ፥ የክብር አምላክ አንጐደጐደ፥ እግዚአብሔር በብዙ ውኆች ላይ።
4 የእግዚአብሔር ድምፅ በኃይል ነው፤ የእግዚአብሔር ድምፅ በታላቅ ክብር ነው።
5 የእግዚአብር ድምፅ ዝግባን ይሰብራል፤ እግዚአብሔር የሊባኖስን ዝግባ ይቀጠቅጣል።
6 እንደ ጥጃ ሊባኖስን፥ አንድ ቀን እንዳለው አውሬ ልጅ ስርዮንን ያዘልላቸዋል።
7 የእግዚአብሔር ድምፅ የእሳቱን ነበልባል ይቈርጣል።
8 የእግዚአብሔር ድምፅ ምድረ በዳውን ያናውጣል፥ እግዚአብሔር የቃዴስን ምድረ በዳ ያናውጣል።
9 የእግዚአብሔር ድምፅ ዋላዎችን ያጠነክራቸዋል፥ ጫካዎቹንም ይገልጣል፤ ሁሉም በመቅደሱ። ምስጋና ይላል።
10 እግዚአብሔር የጥፋት ውኃን ሰብስቦአል፤ እግዚአብሔር ለዘላለም ንጉሥ ሆኖ ይቀመጣል።
11 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ኃይልን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል።
ለቤቱ መመረቅ ምስጋና፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ተቀብለኸኛልና፥ ጠላቶቼንም ደስ አላሰኘህብኝምና ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ።
2 አቤቱ አምላኬ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ ምሕረትም አደረግህልኝ።
3 አቤቱ፥ ነፍሴን ከሲኦል አወጣሃት፥ ወደ ጕድጓድም እንዳልወርድ አዳንኸኝ።
4 ቅዱሳን ሆይ፥ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፥ ለቅድስናውም መታሰቢያ አመስግኑ።
5 ቍጣው ለጥቂት ጊዜ ነው፥ ሞገሱ ግን ለሕይወት ዘመን፤ ልቅሶ ማታ ይመጣል፥ ጥዋት ግን ደስታ ይሆናል።
6 እኔም በደስታዬ። ለዘላለም አልታወክም አልሁ።
7 አቤቱ፥ በፈቃድህ ለሕይወቴ ኃይልን ሰጠሃት፤ ፊትህን መለስህ፥ እኔም ደነገጥሁ።
8 አቤቱ፥ ወደ አንተ ጠራሁ፥ ወደ አምላኬም ለመንሁ።
9 ወደ ጥፋት ብወርድ በደሜ ምን ጥቅም አለ? አፈር ያመሰግንሃልን? እውነትህንም ይናገራልን?
10 እግዚአብሔር ሰማ ማረኝም፤ እግዚአብሔር ረዳቴ ሆነኝ።
11 ክብሬ ትዘምርልህ ዘንድ ዝምም እንዳትል ልቅሶዬን ለደስታ ለወጥህልኝ፥ ማቄን ቀድደህ ደስታንም አስታጠቅኸኝ።
12 አቤቱ አምላኬ፥ ለዘላለም አመሰግንሃለሁ።

ለመዘምራን አለቃ፤ በማድነቅ ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ አንተን ታመንሁ፤ ለዘላለም አልፈር፤ በጽድቅህም አድነኝ።
2 ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል፥ ፈጥነህም አድነኝ፤ ታድነኝ ዘንድ መታመኛ አምላክና የመጠጊያ ቤት ሁነኝ።
3 አምባዬና መጠጊያዬ አንተ ነህና ስለ ስምህ መንገዴን አቅና ምራኝም።
4 አንተ መታመኛዬ ነህና ከደበቁብኝ ወጥመድ አውጣኝ።
5 በእጅህ ነፍሴን እሰጣለሁ፤ የእውነት አምላክ አቤቱ፥ ተቤዥተኸኛል።
6 ከንቱ ምናምንቴነትን የጠበቁትን ጠላህ፤ እኔ ግን በእግዚአብሔር ታመንሁ።
7 መከራዬን አይተሃልና፥ ነፍሴንም ከጭንቀት አድነሃታልና በምሕረትህ ደስ ይለኛል ሐሤትም አደርጋለሁ።
8 በጠላቴ እጅ አልዘጋኸኝም፥ በሰፊም ስፍራ እግሮቼን አቆምህ።
9 ተቸግሬአለሁና አቤቱ ምራኝ፤ ዓይኔም ከኃዘን የተነሣ ተፈጀች፥ ነፍሴም ሆዴም።
10 ሕይወቴ በኅዘን አልቃለችና፥ ዓመታቴም በልቅሶ ጩኸት፤ ኃይሌ በችግር ደከመ፥ አጥንቶቼም ተነዋወጡ።
11 በጠላቶቼ ዘንድ ተነወርኹ፥ ይልቁንም በጎረቤቶቼ ዘንድ፥ ለሚያውቁኝም ፍርሃት ሆንሁ፤ በሜዳ ያዩኝም ከእኔ ሸሹ።
12 እንደ ሞተ ሰው ከልብ ተረሳሁ፥ እንደ ተበላሸ ዕቃም ሆንሁ።
13 የብዙ ሰዎችን ስድብ ሰምቻለሁና፤ በዙሪያው ፍርሃት ነበረ፤ በላዬ በአንድነት በተሰበሰቡ ጊዜ ነፍሴን ለመንጠቅ ተማከሩ።
14 አቤቱ፥ እኔ ግን በአንተ ታመንሁ፤ አንተ አምላኬ ነህ አልሁ።
15 ርስቴ በእጅህ ነው፤ ከጠላቶቼ እጅና ከሚያሳድዱኝ አድነኝ።
16 ፊትህን በባሪያህ ላይ አብራ፥ ስለ ምሕረትህም አድነኝ።
17 አቤቱ፥ አንተን ጠርቻለሁና አልፈር፤ ክፉዎች ይፈሩ በሲኦልም ዝም ይበሉ።
18 በድፍረትና በትዕቢት በመናቅም በጻድቅ ላይ የሚናገሩ የሽንገላ ከንፈሮች ድዳ ይሁኑ።
19 በአንተ ለሚያምኑ በሰው ልጆች ፊት ያዘጋጀሃት ለሚፈሩህም የሰወርሃት፥ ቸርነትህ እንደ ምን በዛች!
20 በፊትህ መጋረጃ ከሰው ክርክር ትጋርዳቸዋለህ፥ በድንኳንህም ከአንደበት ክርክር ትሸፍናቸዋለህ።
21 በተከበበ ከተማ የሚያስደንቅ ምሕረቱን በእኔ የገለጠ እግዚአብሔር ይመስገን።
22 እኔስ ከዓይንህ ፊት ተጣልሁ፥ በድንጋጤ አልሁ፤ አንተ ግን ወደ አንተ በጮኽሁ ጊዜ የልመናዬን ቃል ሰማኸኝ።
23 ሁላችሁ ቅዱሳኑ፥ እግዚአብሔርን ውደዱት፤ እግዚአብሔር እውነተኞችን ይፈልጋል፥ ትዕቢተኞችንም ፈጽሞ ይበቀላቸዋል።
24 በእግዚአብሔር የምታምኑ ሁላችሁ፥ በርቱ ልባችሁም ይጥና።

የዳዊት ትምህርት።
1 መተላለፉ የቀረችለት ኃጢአቱም የተከደነችለት ምስጉን ነው።
2 እግዚአብሔር በደልን የማይቈጥርበት በመንፈሱም ሽንገላ የሌለበት ሰው ምስጉን ነው።
3 ሁልጊዜ ከመጮኼ የተነሣ ዝም ባልሁ ጊዜ አጥንቶቼ ተበላሹ፤
4 በቀንና በሌሊት እጅህ ከብዳብኛለችና፥ እርጥበቴም ለበጋ ትኵሳት ተለወጠ።
5 ኃጢአቴን ለአንተ አስታወቅሁ፥ በደሌንም አልሸፈንሁም፤ ለእግዚአብሔር መተላለፌን እነግራለሁ አልሁ፤ አንተም የልቤን ኃጢአት ተውህልኝ።
6 ስለዚህ ቅዱስ ሁሉ በምቹ ጊዜ ወደ አንተ ይለምናል፤ ብዙ የጥፋት ውኃም ወደ እርሱ አይቀርብም።
7 አንተ ለእኔ መሸሸጊያዬ ነህ፥ ከጣርም ትጠብቀኛለህ፤ ከከበቡኝ ታድነኝ ዘንድ ደስታዬ ነህ።
8 አስተምርሃለሁ በምትሄድበትም መንገድ እመራሃለሁ፤ ዓይኖቼን በአንተ ላይ አጠናለሁ።
9 ወደ አንተ እንዳይቀርቡ በልባብና በልጓም ጉንጫቸውን እንደሚለጕሙአቸው፥ ልብ እንደሌላቸው እንደ ፈረስና እንደ በቅሎ አትሁኑ።
10 በኃጢአተኛ ብዙ መቅሠፍት አለበት፤ በእግዚአብሔር የሚታመነውን ግን ምሕረት ይከብበዋል።
11 ጻድቃን ሆይ፥ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ ሐሤትም አድርጉ፤ ልባችሁም የቀና ሁላችሁ፥ እልል በሉ።
የዳዊት መዝሙር።
1 ጻድቃን ሆይ፥ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፤ ለቅኖች ምስጋና ይገባል።
2 እግዚአብሔርን በመሰንቆ አመስግኑት፥ አሥር አውታርም ባለው በበገና ዘምሩለት።
3 አዲስ ቅኔም ተቀኙለት፥ በእልልታም መልካም ዝማሬ ዘምሩ፤
4 የእግዚአብሔር ቃል ቅን ነውና ሥራውም ሁሉ በእምነት ነውና።
5 ጽድቅንና ፍርድን ይወድዳል፤ የእግዚአብሔር ቸርነት ምድርን ሞላች።
6 በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ጸኑ፥ ሠራዊታቸውም ሁሉ በአፉ እስትንፋስ፤
7 የባሕርን ውኃ እንደ ረዋት የሚሰበስበው፥ ቀላዮችንም በመዝገቦች የሚያኖራቸው።
8 ምድር ሁሉ እግዚአብሔርን ትፍራው፥ በዓለም የሚኖሩ ሁሉም ከእርሱ የተነሣ ይደንግጡ።
9 እርሱ ተናግሮአልና፥ ሆኑም፤ እርሱ አዘዘ፥ ጸኑም።
10 እግዚአብሔር የአሕዛብን ምክር ያጠፋል፥ የአሕዛብንም አሳብ ይመልሳል።
11 የእግዚአብሔር ምክር ግን ለዘላለም ይኖራል። የልቡም አሳብ ለልጅ ልጅ ነው።
12 እግዚአብሔር አምላኩ የሚሆንለት ሕዝብ ምስጉን ነው፥ እርሱ ለርስቱ የመረጠው ሕዝብ።
13 እግዚአብሔር ከሰማይ ተመለከተ፥ የሰውንም ልጆች ሁሉ አየ።
14 ከማደሪያው ቦታ ሆኖ በምድር ወደሚኖሩ ሁሉ ተመለከተ፥
15 እርሱ ብቻውን ልባቸውን የሠራ ሥራቸውንም ሁሉ የሚያስተውል።
16 ንጉሥ በሠራዊቱ ብዛት አይድንም ኃያልም በኃይሉ ብዛት አያመልጥም።
17 ፈረስም ከንቱ ነው፥ አያድንም፤ በኃይሉም ብዛት አያመልጥም።
18 እነሆ፥ የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደሚፈሩት ናቸው፥ በምሕረቱም ወደሚታመኑ፥
19 ነፍሳቸውን ከሞት ያድን ዘንድ፥ በራብም ጊዜ ይመግባቸው ዘንድ።
20 ነፍሳችን እግዚአብሔርን ተስፋ ታደርገዋለች፥ ረዳታችንና መጠጊያችን እርሱ ነውና።
21 ልባችን በእርሱ ደስ ይለዋልና፥ በቅዱስ ስሙም ታምነናልና።
22 አቤቱ፥ ምሕረትህ በላያችን ትሁን፥ በአንተ እንደ ታመንን።
ባሳደደው በአቤሜሌክ ፊት መልኩን በለወጠ ጊዜ በሄደም ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔርን ሁልጊዜ እባርከዋለሁ፥ ምስጋናውንም ዘወትር በአፌ ነው።
2 ነፍሴ በእግዚአብሔር ትከብራለች፥ ገሮችም ሰምተው ደስ ይላቸዋል።
3 እግዚአብሔርን ከእኔ ጋር ታላቅ አድርጉት፥ በአንድነትም ስሙን ከፍ ከፍ እናድርግ።
4 እግዚአብሔርን ፈለግሁት መለሰልኝም፥ ከመከራዬም ሁሉ አዳነኝ።
5 ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችሁማል፥ ፊታችሁም አያፍርም።
6 ይህ ችግረኛ ጮኸ፥ እግዚአብሔርም ሰማው፥ ከመከራውም ሁሉ አዳነው።
7 የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።
8 እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም፤ በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው።
9 የሚፈሩት አንዳችን አያጡምና ቅዱሳኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፍሩት።
10 ባለጠጎች ደኸዩ፥ ተራቡም፥ እግዚአብሔርን የሚፈልጉትን ግን ከመልካም ነገር ሁሉ አይጐድሉም።
11 ልጆቼ ኑ፥ ስሙኝ፤ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ።
12 ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎንም ዘመን ለማየት የሚወድድ?
13 አንደበትህን ከክፉ ከልክል፥ ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ።
14 ከክፉ ሽሽ መልካምንም አድርግ፤ ሰላምን እሻ ተከተላትም።
15 የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደ ጻድቃን ጆሮቹም ወደ ጩኸታቸው ናቸውና።
16 መታሰቢያቸውን ከምድር ያጠፋ ዘንድ የእግዚአብሔር ፊት ክፉን በሚያደርጉ ላይ ነው።
17 ጻድቃን ጮኹ፥ እግዚአብሔርም ሰማቸው ከመከራቸውም ሁሉ አዳናቸው።
18 እግዚአብሔር ልባቸው ለተሰበረ ቅርብ ነው፥ መንፈሳቸው የተሰበረውንም ያድናቸዋል።
19 የጻድቃን መከራቸው ብዙ ነው፥ እግዚአብሔርም ከሁሉ ያድናቸዋል።
20 እግዚአብሔር አጥንቶቻቸውን ሁሉ ይጠብቃል፥ ከእነርሱም አንድ አይሰበርም።
21 ኃጢአተኞችን ክፋት ይገድላቸዋል ጻድቃንንም የሚጠሉ ይጸጸታሉ።
22 የባሪያዎቹን ነፍስ እግዚአብሔር ይቤዣል፥ በእርሱም የሚያምኑ ሁሉ አይጸጸቱም።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ የሚበድሉኝን በድላቸው፥ የሚዋጉኝንም ተዋጋቸው።
2 ጥሩርና ጋሻ ያዝ፥ እኔንም ለመርዳት ተነሥ።
3 ሰይፍህን ምዘዝ የሚያሳድዱኝንም መንገዳቸውን ዝጋ፤ ነፍሴን። መድኃኒትሽ እኔ ነኝ በላት።
4 ነፍሴን የሚሹ ሁሉ ይፈሩ ይጐስቈሉም፤ ክፉትን በእኔ ላይ የሚያስቡ ይፈሩ ወደ ኋላቸውም ይበሉ።
5 በነፋስ ፊት እንዳለ ትቢያ ይሁኑ፥ የእግዚአብሔርንም መልአክ ያስጨንቃቸው።
6 መንገዳቸው ዳጥና ጨለማ ይሁን፥ የእግዚአብሔርም መልአክ ያሳድዳቸው።
7 በከንቱ ያጠፉኝ ዘንድ ወጥመዳቸውን ሸሽገውብኛልና፥ ነፍሴን በከንቱ አበሳጭተዋልና።
8 ያላወቁት ወጥመድ ይምጣባቸው፥ የሸሸጉትም ወጥመድ ይያዛቸው፤ በዚህ ወጥመድ ውስጥ ይውደቁ።
9 ነፍሴ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይላታል፥ በማዳኑም ሐሴት ታደርጋለች።
10 አጥንቶቼ ሁሉ እንዲህ ይሉሃል። አቤቱ፥ እንደ አንተ ማን ነው? ችግረኛን ከሚቀማው እጅ፥ ችግረኛንና ድሀውንም ከሚነጥቀው እጅ ታድነዋለህ።
11 የክፋት ምስክሮች ተነሡብኝ፥ የማላውቀውንም በእኔ ላይ ተናገሩ።
12 ስለ በጎ ክፋትን መለሱልኝ፥ ነፍሴንም ልጆችን አሳጡአት።
13 እኔስ እነርሱ በታመሙ ጊዜ ማቅ ለበስሁ፥ ነፍሴንም በጾም አደከምኋት፤ ጸሎቴም ወደ ብብቴ ተመለሰ።
14 ለወዳጄና ለወንድሜ እንደማደርግ አደረግሁ፤ ለእናቱም እንደሚያለቅስ ራሴን ዝቅ ዝቅ አደረግሁ።
15 በእኔ ላይ ተሰበሰቡ ደስም አላቸው፤ ግፈኞች በእኔ ላይ ተሰበሰቡ እኔም አላውቅሁም፤ ቀደዱኝ አልተውኝምም።
16 ፈተኑኝ በሣቅም ዘበቱብኝ፥ ጥርሳቸውንም በእኔ ላይ አንቀጫቅጩ።
17 አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ታይልኛለህ? ነፍሴን ከክፉ ሥራቸው ብችነቴንም ከአንበሶች አድናት።
18 አቤቱ፥ በታላቁ ጉባኤ ውስጥ እገዛልሃለሁ፥ በብዙ ሕዝብ መካከልም አመሰግንሃለሁ።
19 በግፍ የሚጠሉኝ በላዬ ደስ አይበላቸው፥ በከንቱ የሚጣሉኝም በዓይናቸው አይጣቀሱብኝ።
20 ለእኔስ ሰላምን ይናገሩኛልና፥ በቍጣም ሽንገላን ይመክራሉ።
21 አፋቸውንም በእኔ ላይ አላቀቁ፤ እሰይ እሰይ፥ ዓይናችን አየው ይላሉ።
22 አቤቱ፥ አንተ አየኸው፤ ዝም አትበል፤ አቤቱ፥ ከእኔ አትራቅ።
23 አምላኬ ጌታዬም፥ ወደ ፍርዴ ተነሥ፥ አቤቱ፥ ፍርዴን አድምጥ።
24 አቤቱ አምላኬ፥ እንደ ጽድቅህ ፍረድልኝ፥ በላዬም ደስ አይበላቸው።
25 በልባቸው። እሰይ እሰይ፥ ነፍሳችንን ደስ አላት አይበሉ፤ ደግሞም። ዋጥነው አይበሉ።
26 በመከራዬ ደስ የሚላቸው ይፈሩ፥ በአንድነትም ይጐስቍሉ፤ በእኔ ላይ የሚታበዩ እፍረትንና ጕስቍልናን ይልበሱ።
27 ጽድቄን የሚወድዱአት ደስ ይበላቸው ሐሴትንም ያድርጉ፤ የባሪያውን ሰላም የሚወድድ እግዚአብሔር ታላቅ ይሁን ዘወትር ይበሉ።
28 ምላሴ ጽድቅህን ሁልጊዜም ምስጋናህን ይናገራል።

ለመዘምራን አለቃ፤ የእግዚአብሔር ባሪያ የዳዊት መዝሙር።
1 ኃጢአተኛ በራሱ የሚያስት ነገርን ይናገራል፥ የእግዚአብሔርም ፍርሃት በዓይኖቹ ፊት የለም።
2 በአንደበቱ ሸንግሎአልና፤ ኃጢአቱ ባገኘችው ጊዜ ይጠላታል።
3 የአፉ ቃል ግፍና ሽንገላ ነው፤ ማስተዋልን በጎ ማድረግንም ተወ።
4 በመኝታው ጠማማነትን አሰበ፤ መልካም ባልሆነች መንገድ ቆሞአል፤ ክፋትን አይንቃትም።
5 አቤቱ፥ ምሕረትህ በሰማይ ነው፥ እውነትህም ወደ ደመናት ትደርሳለች።
6 ጽድቅህም እንደ እግዚአብሔር ተራሮች፥ ፍርድህም እጅግ ጥልቅ ናት፤ አቤቱ፥ ሰውንና እንስሳን ታድናለህ።
7 አቤቱ፥ ምሕረትህን እንዴት አበዛህ! የሰው ልጆች በክንፎችህ ጥላ ይታመናሉ።
8 ከቤትህ ጠል ይጠጣሉ፥ ከተድላም ፈሳሽ ታጠጣቸዋለህ።
9 የሕይወት ምንጭ ከአንተ ዘንድ ነውና፤ በብርሃንህ ብርሃንን እናያለን።
10 ምሕረትህን በሚያውቁህ ላይ፥ ጽድቅህንም ልባቸው በቀና ላይ ዘርጋ።
11 የትዕቢት እግር አይምጣብኝ፥ የኃጢአተኞችም እጅ አያውከኝ።
12 ዓመፃን የሚያደርጉ ሁሉ ከዚያ ወደቁ፤ ወድቀዋል፥ መቆምም አይችሉም።
የዳዊት መዝሙር።
1 በክፉዎች ላይ አትቅና፥ ዓመፃንም በሚያደርጉ ላይ አትቅና፤
2 እንደ ሣር ፈጥነው ይደርቃሉና፥ እንደ ለመለመ ቅጠልም ይረግፋሉና።
3 በእግዚአብሔር ታመን፥ መልካምንም አድርግ፥ በምድርም ተቀመጥ፥ ታምነህም ተሰማራ።
4 በእግዚአብሔር ደስ ይበልህ፥ የልብህንም መሻት ይሰጥሃል።
5 መንገድህን ለእግዚአብሔር አደራ ስጥ፥ በእርሱም ታመን፥ እርሱም ያደርግልሃል።
6 ጽድቅህን እንደ ብርሃን። ፍርድህንም እንደ ቀትር ያመጣል።
7 ለእግዚአብሔር ተገዛ ተስፋም አድርገው። መንገድም በቀናችለትና ጥመትን በሚያደርግ ሰው አትቅና።
8 ከቁጣ ራቅ መዓትንም ተው፤ እንዳትበድል አትቅና።
9 ክፉ አድራጊዎች ይጠፋሉና፤ እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ ግን እነርሱ ምድርን ይወርሳሉ።
10 ገና ጥቂት፥ ኃጢአተኛም አይኖርም፤ ትፈልገዋለህ ቦታውንም አታገኝም።
11 ገሮች ግን ምድርን ይወርሳሉ፥ በብዙም ሰላም ደስ ይላቸዋል።
12 ኃጢአተኛ ጻድቁን ይመለካከተዋል፥ ጥርሱንም በእርሱ ላይ ያንገጫግጫል።
13 እግዚአብሔር ይሥቅበታል፥ ቀኑ እንደሚደርስ አይቶአልና።
14 ኃጢአተኞች ሰይፋቸውን መዘዙ፥ ቀስታቸውንም ገተሩ ድሀውንና ችግረኛውን ይጥሉ ዘንድ ልበ ቅኖችንም ይወጉ ዘንድ፤
15 ሰይፋቸው ወደ ልባቸው ይግባ፥ ቀስታቸውም ይሰበር።
16 ለጻድቅ ያለው ጥቂት ከብዙ ከኃጢአተኞች ሀብት ይበልጣል።
17 የኃጥአን ክንድ ትሰበራለችና፤ እግዚአብሔር ግን ጻድቃንን ይደግፋቸዋል።
18 የንጹሓንን መንገድ እግዚአብሔር ያውቃል፥ ርስታቸውም ለዘላለም ነው፤
19 በክፉ ዘመንም አያፍሩም በራብ ዘመንም ይጠግባሉ።
20 ኅጥአን ግን ይጠፋሉ፥ የእግዚአብሔር ጠላቶች በከበሩና ከፍ ከፍ ባሉ ጊዜ እንደ ጢስ ይጠፋሉ።
21 ኃጢአተኛ ይበደራል አይከፍልምም፤ ጻድቅ ግን ይራራል ይሰጣልም።
22 እርሱን የሚባርኩት ምድርን ይወርሳሉና፤ የሚረግሙት ግን ይጠፋሉ።
23 የሰው አካሄድ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይጸናል፥ መንገዱንም ይወድዳል።
24 ቢወድቅም ለድንጋፄ አይጣልም፥ እግዚአብሔር እጁን ይዞ ይደግፈዋልና።
25 ጐለመስሁ አረጀሁም፤ ጻድቅ ሲጣል፥ ዘሩም እህል ሲለምን አላየሁም።
26 ሁልጊዜ ይራራል ያበድርማል፥ ዘሩም በበረከት ይኖራል።
27 ከክፉ ሽሽ፥ መልካምንም አድርግ፤ ለዘላለምም ትኖራለህ።
28 እግዚአብሔር ፍርዱን ይወድዳልና፥ ቅዱሳኑንም አይጥላቸውምና፤ ለዘላለምም ይጠብቃቸዋል ለንጹሓንም ይበቀልላቸዋል፤ የኅጥኣን ዘር ግን ይጠፋል።
29 ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፥ በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ።
30 የጻድቅ አፍ ጥበብን ያስተምራል፥ አንደበቱም ፍርድን ይናገራል።
31 የአምላኩ ሕግ በልቡ ውስጥ ነው፥ በእርምጃውም አይሰናከልም።
32 ኃጢአተኛ ጻድቁን ይመለከተዋል፥ ሊገድለውም ይወድዳል።
33 እግዚአብሔር ግን በእጁ አይተወውም፥ በተፋረደውም ጊዜ አያሸንፈውም።
34 እግዚአብሔርን ደጅ ጥና፥ መንገዱንም ጠብቅ፥ ምድርንም ትወርስ ዘንድ ከፍ ከፍ ያደርግሃል፤ ኃጢአተኞችም ሲጠፉ ታያለህ።
35 ኃጥአን ከፍ ከፍ ብሎ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ለምልሞ አየሁት።
36 ብመለስ ግን አጣሁት፤ ፈለግሁት ቦታውንም አላገኘሁም።
37 ቅንነትን ጠብቅ፥ ጽድቅንም እይ፤ ለሰላም ሰው ቅሬታ አለውና።
38 በደለኞች በአንድነት ይጠፋሉ። የኃጢአተኞች ቅሬታ ይጠፋል።
39 የጻድቃን መድኃኒታቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው፤ በመከራቸውም ጊዜ መጠጊያቸው እርሱ ነው።
40 እግዚአብሔር ይረዳቸዋል፥ ያድናቸዋልም፥ ከኃጢአተኞችም እጅ ያወጣቸዋል፥ ያድናቸዋል፥ በእርሱ ታምነዋልና።
ለሰንበት መታሰቢያ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።
2 ፍላጾችህ ወግተውኛልና፥ እጅህንም አክብደህብኛልና።
3 ከቍጣህ የተነሣ ለሥጋዬ ጤና የለውም፤ ከኃጢአቴም የተነሣ ለአጥንቶቼ ሰላም የላቸውም።
4 ኃጢአቴ በራሴ ላይ ከፍ ከፍ ብሎአልና፥ እንደ ከባድ ሸክምም በላዬ ከብዶአልና።
5 ከስንፍናዬ የተነሣ ቍስሌ ሸተተ በሰበሰም፤
6 እጅግ ጐሰቈልሁ ተዋረድሁም፥ ሁልጊዜም በትካዜ እመላለሳለሁ።
7 ነፍሴ ስድብን ተሞልታለችና፥ ለሥጋዬም ጤና የላትምና።
8 ታመምሁ፤ እጅግም ተቸገርሁ፥ ከልቤ ውዝዋዜም የተነሣ ጮኽሁ።
9 አቤቱ፥ ፈቃዴ ሁሉ በፊትህ ነው፥ ጭንቀቴም ከአንተ አይሰወርም።
10 ልቤ ደነገጠብኝ፥ ኃይሌም ተወችኝ፥ የዓይኖቼም ብርሃን ፈዘዘ።
11 ወዳጆቼም ባልንጀሮቼም ከቍስሌ ገለል ብለው ቆሙ፥ ዘመዶቼም ርቀው ቆሙ።
12 ነፍሴንም የሚሹአት በረቱብኝ፥ መከራዬንም የሚፈልጉ ከንቱን ተናገሩ፥ ሁልጊዜም በሽንገላ ይመክራሉ።
13 እኔ ግን እንደማይሰማ ደንቆሮ አፉንም እንደማይከፍት ዲዳ ሆንሁ።
14 እንደማይሰማ ሰው በአፉም ተግሣጽ እንደሌለው ሰው ሆንሁ።
15 አቤቱ፥ በአንተ ታምኛለሁና፤ አቤቱ አምላኬ፥ አንተ ትሰማኛለህ።
16 ጠላቶቼ በእኔ ላይ ደስ እንዳይላቸው ብያለሁና፥ እግሮቼም ቢሰናከሉ ራሳቸውን በእኔ ላይ ከፍ ከፍ ያደርጋሉ።
17 እኔስ ወደ ማንከስ ቀርቤአለሁና፥ ቍስሌም ሁልጊዜም በፊቴ ነውና።
18 በደሌን እናገራለሁና፥ ስለ ኃጢአቴም እተክዛለሁ።
19 ጠላቶቼ ሕያዋን ናቸው ይበረቱብኝማል፥ በጠማማነትም የሚጠሉኝ በዙ።
20 ጽድቅን ስለ ተከተልሁ፥ በበጎ ፋንታ ክፉን የሚመልሱልኝ ይጠሉኛል።
21 አቤቱ፥ አንተ አትጣለኝ፤ አምላኬ፥ ከኔ አትራቅ።
22 አቤቱ መድኃኒቴ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።

ለመዘምራን አለቃ፥ ለኤዶታም፤ የዳዊት መዝሙር።
1 በአንደበቴ እንዳልስት መንገዴን እጠብቃለሁ፤ ኃጢአተኛ በፊቴ በተቃወመኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ አልሁ።
2 ከዝምታ የተነሣ እንደ ዲዳ ሆንሁ፥ ለበጎ እንኳ ዝም አልሁ፥ ቍስሌም ታደሰብኝ።
3 ልቤም በውስጤ ሞቀብኝ፤ ከማሰቤም የተነሣ እሳት ነደደ፥ በአንደበቴም ተናገርሁ።
4 አቤቱ፥ ፍጻሜዬን አስታውቀኝ፥ የዘመኔ ቍጥሮች ምን ያህል እንደ ሆኑ፥ እኔ ምን ያህል ወደ ኋላ እንደምቀር አውቅ ዘንድ።
5 እነሆ፥ ዘመኖቼን አስረጀሃቸው፤ አካሌም በፊትህ እንደ ኢምንት ነው። ሕያው የሆነ ሰው ሁሉ በእውነት ከንቱ ብቻ ነው።
6 በከንቱ ይታወካል እንጂ በእውነት ሰው እንደ ጣላ ይመላለሳል፤ ያከማቻል የሚሰበስብለትንም አያውቅም።
7 አሁንስ ተስፋዬ ማን ነው? እግዚአብሔር አይደለምን? ትዕግሥቴም ከአንተ ዘንድ ነው።
8 ከኃጢአቴ ሁሉ አድነኝ፥ ለሰነፎችም ስድብ አታድርገኝ።
9 አንተ ሠርተኸኛልና ዝም አልሁ አፌንም አልከፈትሁም።
10 መቅሠፍትህን ከእኔ አርቅ፥ ከእጅህ ብርታት የተነሣ አልቄአለሁና።
11 በተግሣጽህ ስለ ኃጢአቱ ሰውን ዘለፍኸው፥ ነፍሱም እንደ ሸረሪት ድር ታልቃለች፤ በእውነት ሰው ሁሉ ከንቱ ነው።
12 አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማ፥ ጩኸቴንም አድምጥ፥ ልቅሶዬንም ቸል አትበለኝ፤ እኔ በምድር ላይ መጻተኛ ነኝና፥ እንደ አባቶችም እንግዳ ነኝና።
13 ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 ቆይቼ እግዚአብሔር ደጅ ጠናሁት፥ እርሱም ዘንበል አለልኝ ጩኽቴንም ሰማኝ።
2 ከጥፋት ጕድጓድ ከረግረግም ጭቃ አወጣኝ፥ እግሮቼንም በድንጋይ ላይ አቆማቸው፥ አረማመዴንም አጸና።
3 አዲስ ዝማሬን ለአምላካችን ምስጋና በአፌ ጨመረ፤ ብዙዎች ያያሉ ይፈሩማል፥ በእግዚአብሔርም ይታመናሉ።
4 እግዚአብሔርን የታመነ ወደ ትዕቢተኛና ወደ ሐሰተኛ ያልተመለከተ ሰው ምስጉን ነው።
5 አቤቱ አምላኬ፥ ያደረግኸው ተአምራት ብዙ ነው፥ አሳብህንም ምንም የሚመስለው የለም፤ ባወራም ብናገርም ከቍጥር ሁሉ በዛ።
6 መሥዋዕትንና ቍርባንን አልወደድህም፤ ሥጋን አዘጋጀህልኝ፤ የሚቃጠለውንና ስለ ኃጢአት የሚቀርበውን መሥዋዕት አልሻህም።
7 በዚያን ጊዜ አልሁ። እነሆ፥ መጣሁ፤ ስለ እኔ በመጽሐፍ ራስ ተጽፎአል፤
8 አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው።
9 በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፤ እነሆ፥ ከንፈሮቼን አልከለክልም፤ አቤቱ፥ አንተ ጽድቄን ታውቃለህ።
10 እውነትህንም በልቤ ውስጥ አልሰወርሁም፥ ማዳንህንም ተናገርሁ፤ ምሕረትህንና እውነትህን ከታላቅ ጉባኤ አልሰወርሁም።
11 አቤቱ፥ አንተ ምሕረትህን ከእኔ አታርቅ፤ ቸርነትህና እውነትህ ዘወትር ይጠብቁኝ።
12 ቍጥር የሌላት ክፋት አግኝታኛለችና፤ ኃጢአቶቼ ያዙኝ፥ ማየትም ተስኖኛል ከራሴ ጠጕር ይልቅ በዙ፥ ልቤም ተወኝ።
13 አቤቱ፥ ታድነኝ ዘንድ ፍቀድ፤ አቤቱ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።
14 ነፍሴን ለማጥፋት የሚወድዱ ይፈሩ፥ በአንድነትም ይጐስቍሉ፤ በእኔ ላይ ክፋትን ሊያደርጉ የሚወድዱ ወደ ኋላቸው ይመለሱ ይጐስቍሉም።
15 እሰይ እሰይ የሚሉኝ እፍረታቸውን ወዲያው ይከፈሉ።
16 አቤቱ፥ የሚፈልጉህ ሁሉ በአንተ ደስ ይበላቸው ሐሤትም ያድርጉ፤ ሁልጊዜ ማዳንህን የሚወድዱ ዘወትር። እግዚአብሔር ታላቅ ይሁን ይበሉ።
17 እኔ ችግረኛና ምስኪን ነኝ፥ ጌታ ግን ያስብልኛል፤ አንተ ረዳቴና መድኃኒቴ ነህ፤ አምላኬ ሆይ፥ አትዘግይ።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው፤ እግዚአብሔር በክፉ ቀን ያድነዋል።
2 እግዚአብሔር ይጠብቀዋል፥ ሕያውም ያደርገዋል፥ በምድር ላይም ያስመሰግነዋል፥ በጠላቶቹም እጅ አያሳልፈውም።
3 እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል።
4 እኔስ። አቤቱ ማረኝ፤ አንተን በድያለሁና ነፍሴን ፈውሳት አልሁ።
5 ጠላቶቼም በላዬ ክፋትን ይናገራሉ። መቼም ይሞታል ስሙስ መቼ ይሻራል? ይላሉ።
6 እኔን ለማየት ቢገባ ከንቱን ይናገራል፤ ልቡ ኃጢአትን ሰበሰበለት፤ ወደ ሜዳ ይወጣል ይናገራልም።
7 በላዬ በመተባበር ጠላቶቼ ሁሉ ይሾካሾኩብኛል፥ በእኔ ላይም ክፋትን ያስባሉ።
8 ክፉ ነገር መጣበት፤ ተኝቶአል ከእንግዲህ ወዲህ አይነሣም ይላሉ።
9 ደግሞ የሰላሜ ሰው የታመንሁበት እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ።
10 አንተ ግን አቤቱ፥ ማረኝ እመልስላቸውም ዘንድ አስነሣኝ።
11 ጠላቴ እልል አይልብኝምና ስለዚህ እንደ ወደድኸኝ አወቅሁ።
12 እኔን ግን ስለ ቅንነቴ ተቀበልኸኝ፥ በፊትህም ለዘላለም አጸናኸኝ።
13 ከዘላለም እስከ ዘላለም የእስራኤል አምላክ እግዚአሔር ይባረክ። አሜን አሜን።

ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች ትምህርት።
1 ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፥ አቤቱ፥ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች።
2 ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ?
3 ዘወትር። አምላክህ ወዴት ነው? ሲሉኝ እንባዬ በቀንና በሌሊት ምግብ ሆነኝ።
4 ይህን ሳስብ ነፍሴ በእኔ ውስጥ ፈሰሰች፥ ወደ እግዚአብሔር ቤት ወደ ምስጋና መኖሪያ ስፍራ እገባለሁና፤ በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታና ምስጋና ቃል አሰሙ።
5 ነፍሴ ሆይ፥ ለምን ታዝኛለሽ? ለምንስ ታውኪኛለሽ? የፊቴን መድኃኒት አምላኬን አመሰግነው ዘንድ በእግዚአብሔር ታመኚ።
6 አምላኬ ሆይ፥ ነፍሴ በእኔ ውስጥ ታወከች፤ ስለዚህ በዮርዳኖስ ምድር በአርሞንኤምም በታናሹ ተራራ አስብሃለሁ።
7 በፍዋፍዋቴህ ድምፅ ቀላይ ቀላይን ትጠራታለች፤ ማዕበልህና ሞገድህ ሁሉ በላዬ አለፈ።
8 እግዚአብሔር በቀን ቸርነቱን ያዝዛል፥ በሌሊትም ዝማሬው በእኔ ዘንድ ይሆናል፤ የእኔ ስእለት ለሕይወቴ አምላክ ነው።
9 እግዚአብሔርን። አንተ መጠጊያዬ ነህ፤ ለምን ረሳኸኝ? ጠላቶቼ ሲያስጨንቁኝ ለምን አዝኜ እመላለሳለሁ? እለዋለሁ።
10 ጠላቶቼ ሁልጊዜ። አምላክህ ወዴት ነው? ባሉኝ ጊዜ አጥንቶቼን እየቀለጣጠሙ ሰደቡኝ።
11 ነፍሴ ሆይ፥ ለምን ታዝኛለሽ? ለምንስ ታውኪኛለሽ? የፊቴን መድኃኒት አምላኬን አመሰግነው ዘንድ በእግዚአብሔር ታመኚ።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ፍረድልኝ፥ ከጽድቅ ከራቁ ሕዝብም ክርክሬን ተከራከር፤ ከሸንጋይና ከግፈኛ ሰው አድነኝ።
2 አንተ አምላኬ ኃይሌም፥ ለምን ትተውኛለህ? ጠላቶቼ ሲያስጨንቁኝ ለምን አዝኜ እመላለሳለሁ?
3 ብርሃንህንና እውነትህን ላክ፤ እነርሱ ይምሩኝ፥ ወደ ቅድስናህ ተራራና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ።
4 ወደ እግዚአብሔር መሠዊያ፥ ጕልማስነቴንም ደስ ወዳሰኛት ወደ አምላኬ እገባለሁ፤ አቤቱ አምላኬ፥ በበገና አመሰግንሃለሁ።
5 ነፍሴ ሆይ፥ ለምን ታዝኛለሽ? ለምንስ ታውኪኛለሽ? የፊቴን መድኃኒት አምላኬን አመሰግነው ዘንድ በእግዚአብሔር ታመኚ።
ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች ትምህርት።
1 አቤቱ፥ በጆሮአችን ሰማን፥ አባቶቻችንም በዘመናቸው በቀድሞ ዘመን የሠራኸውን ሥራ ነገሩን።
2 እጅህ አሕዛብን አጠፋች፥ እነርሱንም ተከልህ፤ አሕዛብን ሣቀይኻቸው አሳደድኻቸውም።
3 በሰይፋቸው ምድርን አልወረሱም ክንዳቸውም አላዳናቸው፤ ቀኝህና ክንድህ የፊትህም ብርሃን ነው እንጂ ወድደሃቸዋልና።
4 አምላኬና ንጉሤ አንተ ነህ፤ ለያዕቆብ መድኃኒትንህ እዘዝ።
5 በአንተ ጠላቶቻችንን እንወጋቸዋለን፥ በስምህም በላያችን የቆሙትን እናዋርዳቸዋለን።
6 በቀስቴ የምታመን አይደለሁምና፥ ሰይፌም አያድነኝምና፤
7 አንተ ግን ከጠላቶቻችን አዳንኸን፥ የሚጠሉንንም አሳፈርሃቸው።
8 ሁልጊዜ በእግዚአብሔር እንከብራለን፥ ስምህንም ለዘላለም እናመሰግናለን።
9 አሁን ግን ጠላኸን አሳፈርኸንም፥ ከሠራዊታችንም ጋር አትወጣም።
10 ከጠላቶቻችንም ፊት ወደ ኋላችን መለስኸን፥ የሚጠሉንም ተነጣጠቁን።
11 እንደ በጎች ሊበሉን ሰጠኸን፥ ወደ አሕዛብም በተንኸን።
12 ሕዝብህን ያለ ዋጋ ሰጠህ፥ በመለወጣቸውም ትርፍ የለም።
13 ለጎረቤቶቻችን ስድብ፥ በዙሪያችንም ላሉ መሣቂያና መዘበቻ አደረግኸን።
14 በአሕዛብ ዘንድ ምሳሌ፥ በሕዝብም ዘንድ የራስ መንቀሳቀሻ አደረግኸን።
15 ጕስቍልናዬ ሁልጊዜም በፊቴ ነው፥ የፊቴም እፍረት ሸፈነኝ።
16 ከሚሳደብና ከሚላገድ ቃል የተነሣ፥ ከጠላትና ከቂመኛ ፊት የተነሣ ነው።
17 ይህ ሁሉ በእኛ ላይ ደረሰ፥ አልረሳንህም፥ ኪዳንህንም አልወነጀልንም።
18 ልባችን ወደ ኋላው አልተመለሰም፥ ፍለጋችንም ከመንገድህ ፈቀቅ አላለም፤
19 በክፉ ስፍራ አዋርደኸናልና፥ በሞት ጥላም ሰውረኸናልና።
20 የአምላካችንን ስም ረስተንስ ቢሆን፥ እጃችንንም ወደ ሌላ አምላክ አንሥተንስ ቢሆን፥
21 እግዚአብሔር ይህንን አይመረምርም ነበርን? እርሱ ልብ የሰወረውን ያውቃልና።
22 ስለ አንተ ሁልጊዜም ተገድለናል፥ እንደሚታረዱም በጎች ሆነናል።
23 አቤቱ፥ ንቃ፤ ለምንስ ትተኛለህ? ተነሥ፥ ለዘወትርም አትጣለን።
24 ለምንስ ፊትህን ትሰውራለህ? መከራችንንና ችግራችንንስ ለምን ትረሳለህ?
25 ነፍሳችን በመሬት ላይ ተጐሳቍላለችና፥ ሆዳችንም ወደ ምድር ተጣብቃለችና።
26 አቤቱ፥ ተነሥና እርዳን፥ ስለ ስምህም ተቤዠን።

ለመዘምራን አለቃ፤ በመለኮቶች፤ የቆሬ ልጆች ትምህርት፤ የፍቅር መዝሙር።
1 ልቤ መልካም ነገርን አፈለቀ፥ እኔ ሥራዬን ለንጉሥ እነግራለሁ፤ አንደበቴ እንደ ፈጣን ጸሓፊ ብርዕ ነው።
2 ውበትህ ከሰው ልጆች ይልቅ ያምራል፤ ሞገስ በከንፈሮችህ ፈሰሰ፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ባረከህ።
3 ኃያል ሆይ፥ በቍንጅናህና በውበትህ ሰይፍህን በወገብህ ታጠቅ።
4 ስለ ቅንነትና ስለ የዋህነት ስለ ጽድቅም አቅና ተከናወን ንገሥም፤ ቀኝህም በክብር ይመራሃል።
5 ኃያል ሆይ፥ ፍላጻዎችህ የተሳሉ ናቸው፥ እነርሱም በንጉሥ ጠላቶች ልብ ውስጥ ይገባሉ፥ አሕዛብም በበታችህ ይወድቃሉ።
6 አምላክ ሆይ፥ ዙፋንህ ለዘላለም ነው፤ የመንግሥትህ በትር የቅንነት በትር ነው።
7 ጽድቅን ወደድህ ዓመፃንም ጠላህ፤ ስለዚህ ከባልንጀሮችህ ይልቅ እግዚአብሔር አምላክ የደስታ ዘይትን ቀባህ።
8 በልብሶችህ ሁሉ ከርቤና ሽቱ ዝባድም አሉ፤ ከዝሆን ጥርሶች አዳራሽ ደስ ያሰኙሃል።
9 የንጉሦች ሴት ልጆች ለክብርህ ናቸው፤ በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች።
10 ልጄ ሆይ፥ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ፤ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ፤
11 ንጉሥ ውበትሽን ወድዶአልና፥ እርሱ ጌታሽ ነውና።
12 የጢሮስ ሴቶች ልጆች እጅ መንሻን ይዘው ይሰግዱለታል። የምድር ባለጠጎች አሕዛብ በፊትህ ይማለላሉ።
13 ለሐሴቦን ንጉሥ ልጅ ሁሉ ክብርዋ ነው፤ ልብስዋ የወርቅ መጐናጸፊያ ነው።
14 በኋላዋ ደናግሉን ለንጉሥ ይወስዳሉ፥ ባልንጀሮችዋንም ወደ አንተ ያቀርባሉ፤
15 በደስታና በሐሴት ይወስዱአቸዋል፥ ወደ ንጉሥ እልፍኝም ያስገቡአቸዋል።
16 በአባቶችሽ ፋንታ ልጆች ተወለዱልሽ፥ በምድርም ሁሉ ላይ ገዥዎች አድርገሽ ትሾሚያቸዋለሽ።
17 ለልጅ ልጅ ሁሉ ስምሽን ያሳስባሉ፤ ስለዚህ ለዓለምና ለዘላለም አሕዛብ ይገዙልሃል።
ለመዘምራን አለቃ፤ ስለ ምሥጢር፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።
1 አምላካችን መጠጊያችንና ኃይላችን፥ ባገኘን በታላቅ መከራም ረዳታችን ነው።
2 ስለዚህ ምድር ብትነዋወጥ፥ ተራሮችም ወደ ባሕር ልብ ቢወሰዱ አንፈራም።
3 ውኆቻቸው ጮኹ ተናወጡም፥ ተራሮችም ከኃይሉ የተነሣ ተናወጡ።
4 የወንዝ ፈሳሾች የእግዚአብሔርን ከተማ ደስ ያሰኛሉ፤ ልዑል ማደሪያውን ቀደሰ።
5 እግዚአሔር በመካከልዋ ነው አትናወጥም፥ እግዚአብሔርም ፈጥኖ ይረዳታል።
6 አሕዛብ ተናወጡ መንግሥታትም ተመለሱ፤ እርሱ ቃሉን ሰጠ፥ ምድርም ተንቀጠቀጠች።
7 የሠራዊት ጌታ ከእኛ ጋር ነው፤ የያዕቆብ አምላክ መጠጊያችን ነው።
8 የእግዚአብሔርን ሥራ፥ በምድር ያደረገውንም ተኣምራት እንድታዩ ኑ።
9 እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ጦርነት ይሽራል። ቀስትን ይሰብራል፥ ጦርንም ይቈርጣል በእሳትም ጋሻን ያቃጥላል።
10 ዕረፉ፥ እኔም አምላክ እንደ ሆንሁ እወቁ፤ በአሕዛብ ዘንድ ከፍ ከፍ እላለሁ፥ በምድርም ላይ ከፍ ከፍ እላለሁ።
11 የሠራዊት ጌታ ከእኛ ጋር ነው፤ የያዕቆብ አምላክ መጠጊያችን ነው።

ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።
1 አሕዛብ ሁላችሁ፥ እጆቻችሁን አጨብጭቡ፥ በደስታ ቃልም ለእግዚአብሔር እልል በሉ።
2 እግዚአብሔር ልዑል ግሩምም ነውና፥ በምድር ሁሉ ላይም ታላቅ ንጉሥ ነውና።
3 አሕዛብን ከእኛ በታች፥ ወገኖችንም ከእግራችን በታች አስገዛልን።
4 ለርስቱ እኛን መረጠን፥ የወደደውን የያዕቆብን ውበት።
5 አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።
6 ዘምሩ፥ ለአምላካችን ዘምሩ፤ ዘምሩ፥ ለንጉሣችን ዘምሩ።
7 እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና፤ በማስተዋል ዘምሩ።
8 እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ነገሠ፤ እግዚአብሔር በቅድስናው ዙፋን ይቀመጣል።
9 የምድር ኃይለኞች ለእግዚአብሔር ናቸውና የአሕዛብ አለቆች ወደ አብርሃም አምላክ ተሰበሰቡ፤ እርሱንም ከፍ ከፍ አደረጉት።
በሁለተኛ ሰንበት የቆሬ ልጆች፤ የምስጋና መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ትልቅ ነው፤ በአምላካችን ከተማ በተቀደሰ ተራራ ምስጋናው ብዙ ነው።
2 በሰሜን ወገን በመልካም ስፍራ የቆመ የምድር ሁሉ ደስታ የጽዮን ተራራ ነው፤ እርሱም የትልቁ ንጉሥ ከተማ ነው።
3 እግዚአብሔር በአዳራሾችዋ መጠጊያ ሆኖ ይታወቃል።
4 እነሆ፥ ነገሥታት ተከማችተው በአንድነት መጥተዋል።
5 እነርሱስ አይተው ተደነቁ፥ ደነገጡ፥ ታወኩ።
6 መንቀጥቀጥ እንደ ወላድ ምጥ በዚያ ያዛቸው።
7 በኃይለኛ ነፋስ የተርሴስን መርከቦች ትሰብራለህ።
8 እንደ ሰማን እንዲሁ አየን በሠራዊት ጌታ ከተማ፥ በአምላካችን ከተማ፤ እግዚአብሔር ለዘላለም ያጸናታል።
9 አምላክ ሆይ፥ በሕዝብህ መካከል ምሕረትህን ተቀበልን።
10 አምላክ ሆይ፥ እንደ ስምህ እንዲሁም እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ምስጋናህ ነው፤ ቀኝህ ጽድቅን የተሞላች ናት።
11 አቤቱ፥ ስለ ፍርድህ የጽዮን ተራራ ደስ ይበለው፥ የአይሁድም ሴት ልጆች ሐሤት ያድርጉ።
12 ጽዮንን ክበቡአት፥ በዙሪያዋም ተመላለሱ፥ ግንቦችዋንም ቍጠሩ፤
13 በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ፤ አዳራሽዋን አስቡ፤ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ።
14 ለዓለምና ለዘላለም ይህ አምላካችን ነው፥ እርሱም ለዘላለም ይመራናል።

ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።
1 አሕዛብ ሁላችሁ፥ ይህን ስሙ፤ በዓለም የምትኖሩትም ሁላችሁ፥ አድምጡ፤
2 ዝቅተኞችና ከፍተኞች፥ ባለጠጎችና ድሆች በአንድነት።
3 አፌ ጥበብን ይናገራል፥ የልቤም አሳብ ማስተዋልን።
4 ጆሮዬን ወደ ምሳሌ አዘነብላለሁ፥ በበገናም ምሥጢሬን እገልጣለሁ።
5 ኃጢአት ተረከዜን በከበበኝ ጊዜ በክፉ ቀን ለምን እፈራለሁ?
6 በኃይላቸው የሚታመኑ፥ በባለጠግነታቸውም ብዛት የሚመኩ፤
7 ወንድም ወንድሙን አያድንም፥ ሰውም አያድንም፤ ቤዛውን ለእግዚአብሔር አይሰጥም፥
8 –
9 ለዘላለም እንዲኖር፥ ጥፋትንም እንዳያይ፤ የነፍሳቸው ለውጥ ከብሮአልና፥ ለዘላለምም ቀርቶአልና።
10 ብልሃተኞች እንዲሞቱ፥ ሰነፎችችና ደንቆሮች በአንድነት እንዲጠፉ፥ ገንዘባቸውንም ለሌሎች እንዲተዉ አይቶአል።
11 በልባቸውም ቤታቸው ለዘላለም የሚኖር፥ ማደሪያቸውም ለልጆች ልጅ የሚሆን ይመስላቸዋል፤ በየአገራቸውም ስማቸው ይጠራል።
12 ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም፤ እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ።
13 ይህች መንገዳቸው መሰናክላቸው ናት፥ ከእነርሱም በኋላ የሚመጡ በአፋቸው እሺ ይላሉ።
14 እንደ በጎች ወደ ሲኦል የሚሄዱ ናቸው፥ እረኛቸውም ሞት ነው፤ ቅኖችንም በማለዳ ይገዙአቸዋል፥ ውበታቸውም ከመኖሪያቸው ተለይታ በሲኦል ታረጃለች።
15 ነገር ግን እግዚአብሔር ይቀበለኛልና ነፍሴን ከሲኦል እጅ ይቤዣታል።
16 የሰው ባለጠግነት የቤቱም ክብር በበዛ ጊዜ አትፍራ፥
17 በሞተ ጊዜ ከእርሱ ጋር ምንም አይወስድምና፥ ክብሩም ከእርሱ በኋላ አይወርድምና።
18 በሕይወቱ ሳለ ነፍሱን ባርኮአልና ለሰውነቱ መልካም ብታደርግለት ያመሰግንሃል።
19 ሆኖም ወደ አባቶቹ ትውልድ ይወርዳል፤ ለዘላለም ብርሃንን አያይም።
20 አእምሮ የሌለው ክቡር ሰው እንደሚጠፋ እንስሶች መሰለ።
የአሳፍ መዝሙር።
1 የአማልክት አምላክ እግዚአብሔር ተናገረ፥ ከፀሓይም መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ምድርን ጠራት።
2 ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል።
3 አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊት ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ።
4 በላይ ያለውን ሰማይን ምድርንም በሕዝቡ ለመፍረድ ይጠራል፤
5 ከእርሱ ጋር ለመሥዋዕት ኪዳን የቆሙትን ቅዱሳኑን ሰብስቡለት።
6 ሰማያት ጽድቁን ይናገራሉ፥ እግዚአብሔር ፈራጅ ነውና።
7 ሕዝቤ፥ ስማኝ፥ ልንገርህ፤ እስራኤልም፥ ስማኝ፥ ልመስክርብህ፤ አምላክስ እኔ አምላክህ ነኝ።
8 ስለ ቍርባንህ የምዘልፍህ አይደለሁም፤ የሚቃጠል መሥዋዕትህ ሁልጊዜ በፊቴ ነው።
9 ከቤትህ ፍሪዳን ከመንጋህም አውራ ፍየልን አልወስድም፤
10 የምድረ በዳ አራዊት ሁሉ በሺህ ተራራዎች ያሉ እንስሶችም የእኔ ናቸውና።
11 የሰማይን አዕዋፍ ሁሉ አውቃለሁ፥ የምድረ በዳ አራዊትም በእኔ ዘንድ ናቸው።
12 ብራብም ለአንተ አልነግርህም፥ ዓለምና ሞላው የእኔ ነውና።
13 የፍሪዳውን ሥጋ እበላለሁን? የፍየሉንስ ደም እጠጣለሁን?
14 ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት ሠዋ፥ ለልዑልም ስእለትህን ስጥ፤
15 በመከራ ቀን ጥራኝ፥ አድንህማለሁ አንተም ታከብረኛለህ።
16 ኃጢአተኛውን ግን እግዚአብሔር አለው። ለምን አንተ ሕጌን ትናገራለህ? ኪዳኔንም በአፍህ ለምን ትወስዳለህ?
17 አንተስ ተግሣጼን ጠላህ፥ ቃሎቼንም ወደ ኋላህ ጣልህ።
18 ሌባውን ባየህ ጊዜ ከእርሱ ጋር ትሮጥ ነበር እድል ፈንታህንም ከአመንዝሮች ጋር አደረግህ።
19 አፍህ ክፋትን አበዛ፥ አንደበትህም ሽንገላን ተበተበ።
20 ተቀምጠህ ወንድምህን አማኸው፥ ለእናትህም ልጅ ዕንቅፋት አኖርህ።
21 ይህን አድርገህ ዝም አልሁህ፤ እኔ እንደ አንተ እሆን ዘንድ ጠረጠርህ፤ እዘልፍሃለሁ በፊትህም እቆማለሁ።
22 እግዚአብሔርን የምትረሱ እናንተ፥ ይህን አስተውሉ፤ አለዚያ ግን ይነጥቃል የሚያድንም የለም።
23 ምስጋና የሚሠዋ ያከብረኛል፤ የእግዚአብሔርን ማዳን ለእርሱ የማሳይበት መንገድ ከዚያ አለ።
ለመዘምራን አለቃ፤ ወደ ቤርሳቤህ ከገባ በኋላ ነቢዩ ናታን ወደ እርሱ በመጣ ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እንደ ቸርነትህ መጠን ማረኝ፤ እንደ ምሕረትህም ብዛት መተላለፌን ደምስስ።
2 ከበደሌ ፈጽሞ እጠበኝ፥ ከኃጢአቴም አንጻኝ፤
3 እኔ መተላለፌን አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና።
4 አንተን ብቻ በደልሁ፥ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ፥ በነገርህም ትጸድቅ ዘንድ በፍርድህም ንጹሕ ትሆን ዘንድ።
5 እነሆ፥ በዓመፃ ተፀነስሁ፥ እናቴም በኃጢአት ወለደችኝ።
6 እነሆ፥ እውነትን ወደድህ፤ የማይታይ ስውር ጥበብን አስታወቅኸኝ።
7 በሂሶጵ እርጨኝ፥ እነጻማለሁ፤ እጠበኝ፥ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እሆናለሁ።
8 ሐሤትንና ደስታን አሰማኝ፥ የሰበርሃቸውም አጥንቶቼ ደስ ይላቸዋል።
9 ከኃጢአቴ ፊትህን መልስ፥ በደሌንም ሁሉ ደምስስልኝ።
10 አቤቱ፥ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ፥ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ።
11 ከፊትህ አትጣለኝ፥ ቅዱስ መንፈስህንም ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ።
12 የማዳንህን ደስታ ስጠኝ፥ በእሽታ መንፈስም ደግፈኝ።
13 ለሕግ ተላላፎች መንገድህን አስተምራለሁ፥ ኃጢአተኞችም ወደ አንተ ይመለሳሉ።
14 የመድኃኒቴ አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፥ ከደም አድነኝ፥ አንደበቴም በአንተ ጽድቅ ትደሰታለች።
15 አቤቱ፥ ከንፈሮቼን ክፈት፥ አፌም ምስጋናህን ያወራል።
16 መሥዋዕትን ብትወድድስ በሰጠሁህ ነበር፤ የሚቃጠለውም መሥዋዕት ደስ አያሰኝህም።
17 የእግዚአብሔር መሥዋዕት የተሰበረ መንፈስ ነው፥ የተሰበርውንና የተዋረደውን ልብ እግዚአብሔር አይንቅም።
18 አቤቱ፥ በውዴታህ ጽዮንን አሰማምራት፤ የኢየሩሳሌምንም ቅጽሮች ሥራ።
19 የጽድቁን መሥዋዕት መባውንም የሚቃጠለውንም መሥዋዕት በወደድህ ጊዜ፥ ያን ጊዜ በመሠዊያህ ላይ ፍሪዳዎችን ይሠዋሉ።
ለመዘምራን አለቃ፤ ኤዶማዊው ዶይቅ መጥቶ ለሳኦል። ዳዊት ወደ አቢሜሌክ ቤት መጥቶአል ብሎ በነገረው ጊዜ፤ የዳዊት ትምህርት።
1 ኃያል ሆይ፥ በክፋት ለምን ትጓደዳለህ? ሁልጊዜስ በመተላለፍ?
2 አንደበትህ ኃጢአትን ያስባል፤ እንደ ተሳለ ምላጭ ሽንገላን አደረግህ።
3 ከመልካም ይልቅ ክፋትን፥ ጽድቅንም ከመናገር ይልቅ ዓመፃን ወደድህ።
4 የሚያጠፉ ቃልን ሁሉ፥ የሽንገላ ምላስን ወደድህ።
5 ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ያፈርስሃል፤ ከቤትህም ይነቅልሃል ያፈልስሃልም፥ ሥርህንም ከሕያዋን ምድር።
6 ጻድቃን አይተው ይፈራሉ፤ በእርሱም ይሥቃሉ እንዲህም ይላሉ።
7 እግዚአብሔርን ረዳቱ ያላደረገ፥ በባለጠግነቱም ብዛት የታመነ፥ በከንቱ ነገርም የበረታ ያ ሰው እነሆ።
8 እኔስ በእግዚአብሔር ቤት እንደ ለመለመ እንደ ወይራ ዛፍ ነኝ፤ ለዓለምና ለዘላለም በእግዚአብሔር ምሕረት ታመንሁ።
9 አድርገህልኛልና ለዘላለም አመሰግንሃለሁ፥ በቅዱሳንህም ዘንድ መልካም ነውና ስምህን ተስፋ አደርጋለሁ።
ለመዘምራን አለቃ በማኽላት፤ የዳዊት ትምህርት።
1 ሰነፍ በልቡ። አምላክ የለም ይላል። ረከሱ በበደላቸውም ጐሰቈሉ፤ በጎ ነገርን የሚያደርጋት የለም።
2 የሚያስተውል እግዚአብሔርንም የሚፈልግ እንዳለ ያይ ዘንድ እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ።
3 ሁሉ በደሉ፥ አብረውም ረከሱ፤ አንድ ስንኳ በጎን ነገር የሚያደርጋት የለም።
4 ሕዝቤን እንጀራ እንደሚበላ የሚበሉ ግፍ አድራጊዎች ሁሉ አያውቁምን? እግዚአብሔርንም አይጠሩትም።
5 እግዚአብሔር የግብዞችን አጥንቶች በትኖአልና። በዚያ የሚያስፈራ ሳይኖር እጅግ ፈሩ፤ እግዚአብሔር ንቆአቸዋልና አሳፈርሃቸው።
6 መድኃኒትን ከጽዮን ለእስራኤል ማን በሰጠ! እግዚአብሔር የሕዝቡን ምርኮ በመለሰ ጊዜ፥ ያዕቆብ ደስ ይለዋል እስራኤልም ሐሤት ያደርጋል።
ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ ዜፋውያን መጥተው ለሳኦል። እነሆ ዳዊት በእኛ ዘንድ ተሸሽጓል ብለው በነገሩት ጊዜ፤ የዳዊት ትምህርት።
1 አቤቱ፥ በስምህ አድነኝ፥ በኃይልህም ፍረድልኝ።
2 አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማኝ፥ የአፌንም ቃል አድምጥ፤
3 እንግዶች ቁመውብኛልና፥ ኃያላንም ነፍሴን ሽተዋታልና። እግዚአብሔርን በፊታቸው አላደረጉትም።
4 እነሆ፥ እግዚአብሔር ይረዳኛል፥ ጌታዬም ለነፍሴ ደጋፊዋ ነው።
5 ክፋትን ወደ ጠላቶቼ ይመልሳታል፤ በእውነትህም አጥፋቸው።
6 ከፈቃዴ እሠዋልሃለሁ፤ አቤቱ፥ መልካም ነውና ስምህን አመሰግናለሁ፤
7 ከመከራ ሁሉ አድኖኛልና፥ ዓይኔም በጠላቶቼ ላይ አይታለችና።
ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ የዳዊት ትምህርት።
1 አቤቱ፥ ጸሎቴን አድምጥ፥ ልመናዬንም ቸል አትበል።
2 ተመልከተኝ ስማኝም። በኀዘኔ ተቅበዘበዝሁ ተናወጥሁም፤
3 ከጠላት ድምፅ ከዓመፀኛም ግፍ የተነሣ፤ ዓመፃን በላዬ ጥለውብኛልና፥ በቁጣም ጠልተውኛልና።
4 ልቤ በላዬ ተናወጠብኝ፥ የሞት ድንጋጤም ወደቀብኝ።
5 ፍርሃትና እንቅጥቅጥ መጡብኝ፥ ጨለማም ሸፈነኝ።
6 በርሬ ዐርፍ ዘንድ እንደ ርግብ ክንፍን ማን በሰጠኝ!
7 እነሆ፥ ኰብልዬ በራቅሁ በምድረ በዳም በተቀመጥሁ፤
8 ከዐውሎና ከብርቱ ንፋስ ሸሽቼ በፈጠንሁ አልሁ።
9 አቤቱ፥ ግፍንና ጠብን በከተማ ውስጥ አይቼአለሁና አስጥማቸው እንደበታቸውንም ቍረጥ።
10 በቀንና በሌሊት በቅጥርዋ ይከብቡአታል፤ ዓመፃና ድካም ኃጢአትም በመካከልዋ ነው፤
11 ተንኰልና ሽንገላ ከአደባባይዋ አይርቁም።
12 ጠላትስ ቢሰድበኝ፥ በታገሥሁ ነበር፤ የሚጠላኝም ራሱን በላዬ ከፍ ከፍ ቢያደርግ፥ ከእርሱ በተሸሸግሁ ነበር።
13 አንተ ግን፥ እኩያዬ ሰው፥ ባልንጀራዬና የልቤ ወዳጅ፤
14 መብልን ከእኔ ጋር በአንድነት ያጣፈጥህ፤ በአንድ ልብ በእግዚአብሔር ቤት ተራመድን።
15 ሞት ይምጣባቸው፤ በሕይወት ሳሉ ወደ ሲኦል ይውረዱ፤ ክፋት በማደሪያቸውና በመካከላቸው ነውና።
16 እኔ ግን ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፥ እግዚአብሔርም ሰማኝ።
17 በማታና በጥዋት በቀትርም እናገራለሁ እጮኽማለሁ፥ ቃሌንም ይሰማኛል።
18 በእኔ ላይ ብዙ ነበሩና ከሚቃረቡኝ ነፍሴን በሰላም አድናት።
19 ቤዛ የላቸውምና፥ እግዚአብሔርንም አልፈሩትምና ከጥንት ጀምሮ የነበረ እግዚአብሔር ሰምቶ ያጐሰቍላቸዋል።
20 ከእርሱ ጋር ሰላም በነበሩት ላይ እጁን ዘረጋ፤ ኪዳኑንም አረከሱ።
21 አፉ ከቅቤ ይልቅ ለዘበ፥ በልቡ ግን ሰልፍ ነበረ፤ ቃሎቹም ከዘይት ይልቅ ለሰለሱ፥ እነርሱ ግን እንደ ተመዘዘ ሰይፍ ናቸው።
22 ትካዜህን በእግዚአብሔር ላይ ጣል፥ እርሱም ይደግፍሃል፤ ለጻድቁም ለዘላለም ሁከትን አይሰጠውም።
23 አንተ ግን፥ አቤቱ፥ ወደ ሞት ጕድጓድ ታወርዳቸዋለህ፤ የደም ሰዎችና ሸንጋዮች ዘመናቸው ግማሽ አይሞላም፤ እኔ ግን፥ አቤቱ፥ እታመንሃለሁ።

ለመዘምራን አለቃ፤ ከቅዱሳን ስለ ራቁ ሕዝብ፤ ፍልስጥኤማውያን በጌት በያዙት ጊዜ፤ የዳዊት ቅኔ።
1 አቤቱ፥ ሰው ረግጦኛልና ማረኝ፤ ሁልጊዜም በሰልፍ አስጨንቆኛል።
2 የሚዋጉኝ በዝተዋልና ሁልጊዜ ቀኑን ሁሉ ጠላቶቼ ረገጡኝ።
3 እኔ ግን ፈራሁ በአንተም ታመንሁ።
4 በእግዚአብሔር ቃሉን አመሰግናለሁ፤ በእግዚአብሔር ታመንሁ፥ አልፈራም፤ ሰው ምን ያደርገኛል?
5 ሁልጊዜ ቃሎቼን ያጸይፉብኛል፤ በእኔ ላይም የሚመክሩት ሁሉ ለክፉ ነው።
6 ይሸምቁብኛል ይሸሽጉኝማል፥ እነርሱም ተረከዜን ይመለካከታሉ፥ ሁልጊዜም ነፍሴን ይሸምቁባታል።
7 በምንም ምን አታድናቸውም፤ አሕዛብን በቍጣ ትጥላቸዋለህ።
8 አምላክ ሆይ፥ ሕይወቴን ነገርሁህ፤ እንባዬን እንደ ትእዛዝህ በፊተህ አኖርህ።
9 በጠራሁህ ጊዜ ጠላቶቼ ወደ ኋላቸው ይመለሳሉ፤ አንተ አምላኬ እንደ ሆንህ እነሆ፥ አወቅሁ።
10 በእግዚአብሔር ቃሉን አመሰግናለሁ፤ በእግዚአብሔር ቃሉን አከብራለሁ።
11 በእግዚአብሔር ታመንሁ፥ አልፈራም ሰው ምን ያደርገኛል?
12 አቤቱ፥ የምስጋና ስእለት የምሰጥህ ከእኔ ዘንድ ነው፤
13 ነፍሴን ከሞት፥ እግሮቼን ከመውደቅ አድነሃልና፥ በሕያዋን ብርሃን እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው ዘንድ።
ለመዘምራን አለቃ፤ አታጥፋ። ከሳኦል ፊት ሸሽቶ በዋሻ በነበረበት ጊዜ፤ የዳዊት ቅኔ።
1 ማረኝ፥ አቤቱ፥ ማረኝ፥ ነፍሴ አንተን ታምናለችና፤ ጉዳት እስክታልፍ ድረስ በክንፎችህ ጥላ እታመናለሁ።
2 ወደሚረዳኝ እግዚአብሔር ወደ ልዑል እግዚአብሔር እጮኻለሁ።
3 ከሰማይ ልኮ አዳነኝ፥ ለረገጡኝም ውርደትን ሰጣቸው፤ እግዚአብሔር ቸርነቱንና እውነቱን ላከ።
4 ነፍሴን ከአንበሶች መካከል አዳናት። ደንግጬ ተኛሁ፤ የሰው ልጆች ጥርሳቸው ጦርና ፍላጻ፥ አንደበታቸው የተሳለ ሾተል ነው።
5 አምላክ ሆይ፥ በሰማያት ላይ ከፍ ከፍ በል፤ ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትሁን።
6 ለእግሮቼ ወጥመድን አዘጋጁ፥ ነፍሴንም አጐበጡአት፤ ጕድጓድ በፊቴ ቈፈሩ፥ በእርሱም ወደቁ።
7 ልቤ ጨካኝ ነው፥ አቤቱ፥ ልቤ ጨካኝ ነው፤ እቀኛለሁ፥ እዘምራለሁ።
8 ክብሬ ይነሣ፥ በገናና መሰንቆም ይነሡ፤ እኔም ማልጄ እነሣለሁ።
9 አቤቱ፥ በአሕዛብ ዘንድ አመሰግንሃለሁ፥ በወገኖችም ዘንድ እዘምርልሃለሁ፤
10 ምሕረትህ እስከ ሰማይ ድረስ ከፍ ብላለችና፥ እውነትህም እስከ ደመናት ድረስ።
11 አምላክ ሆይ፥ በሰማያት ላይ ከፍ ከፍ በል፤ ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትሁን።
ለመዘምራን አለቃ፤ አታጥፋ። የዳዊት ቅኔ።
1 በእውነት ጽድቅን ብትናገሩስ፥ የሰው ልጆች ሆይ፥ በቅን ትፈርዳላችሁ፤
2 በልባችሁ በምድር ላይ ኃጢአትን ትሠራላችሁና፥ እጆቻችሁም ግፍን ይታታሉና።
3 ኅጥኣን ከማኅፀን ጀምረው ተለዩ፤ ከሆድም ጀምረው ሳቱ፥ ሐሰትንም ተናገሩ።
4 ቍጣቸው እንደ እባብ መርዝ ነው፥ እንደ ምድር አውሬም ጆሮዋ የተደፈነ ነው፥
5 አዋቂ ሲደግምባት የአስማተኛውን ቃል እንደማትሰማ።
6 እግዚአብሔር ጥርሳቸውን በአፋቸው ውስጥ ይሰብራል፤ እግዚአብሔር የአንበሶቹን መንጋጋቸውን ያደቅቃል።
7 እንደሚፈስስ ውኃ ይቀልጣሉ፤ እስኪያደክማቸው ድረስ ፍላጾቹን ይገትራል።
8 እንደሚቀልጥ ሰም ያልቃሉ፤ እሳት ወደቀች፥ ፀሐይንም አላዩአትም።
9 እሾኻችሁ ሳይታወቅ በትር ሆነ፤ ሕያዋን ሳላችሁ በመዓቱ ይነጥቃችኋል።
10 ጻድቅ በቀልን ባየ ጊዜ ደስ ይለዋል፤ በኃጢአተኛው ደምም እጁን ይታጠባል።
11 ሰውም። በእውነት ለጻድቅ ፍሬ አለው፤ በእውነት በምድር ላይ የሚፈርድ አምላክ አለ ይላል።
ለመዘምራን አለቃ፤ አታጥፋ። ሳኦል ይገድሉት ዘንድ ቤቱን እንዲጠብቁ በላከ ጊዜ፤ የዳዊት ቅኔ።
1 አምላኬ ሆይ፥ ከጠላቶቼ አድነኝ፤ በላዬም ከቆሙት አስጥለኝ።
2 ከግፍ አድራጊዎች ታደገኝ፥ ከደም ሰዎችም አድነኝ።
3 እነሆ፥ ነፍሴን ሸምቀውባታልና፥ ብርቱዎችም በላዬ ተሰበሰቡ። አቤቱ፥ በበደሌም አይደለም፥ በኃጢአቴም አይደለም።
4 ያለ በደል ሮጥሁ ተዘጋጀሁም፤ ተነሥ፥ ተቀበለኝ፥ እይም።
5 አንተም አቤቱ፥ የኃያላን አምላክ፥ የእስራኤል አምላክ፥ አሕዛብን ሁሉ ትጐበኛቸው ዘንድ ተነሥ፤ ዓመፅ የሚያደርጉትን ሁሉ አትማራቸው።
6 ማታ ይመለሱ እንደ ውሾችም ይራቡ፥ በከተማም ይዙሩ።
7 እነሆ፥ በአፋቸው አሰምተው ይናገራሉ፤ ሰይፍም በከንፈሮቻቸው አለ፤ ማን ይሰማል? ይላሉ።
8 አንተ ግን አቤቱ፥ ትሥቅባቸዋለህ፥ አሕዛብንም ሁሉ ትንቃቸዋለህ።
9 እግዚአብሔር መጠጊያዬ ነውና ኃይሌን ወደ አንተ አስጠጋለሁ።
10 የአምላኬ ቸርነቱ ይገናኘኛል አምላኬ በጠላቶቼ ላይ ያሳየኛል።
11 ሕግህን እንዳይረሱ አትግደላቸው፤ አቤቱ ጋሻዬ፥ በኃይልህ በትናቸው አውርዳቸውም።
12 ስለ አፋቸው ኃጢአት ስለ ከንፈራቸውም ቃል፥ መርገምንና ሐሰትን ስለሚናገሩ፥ በትዕቢታቸው ይጠመዱ።
13 በቍጣ አጥፋቸው፥ እንዳይኖሩም አጥፋቸው፤ የያዕቆብም አምላክ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ እንዲገዛ ይወቁ።
14 ማታ ይመለሱ እንደ ውሾችም ይራቡ፥ በከተማም ይዙሩ።
15 እነርሱም መብል ለመፈለግ ይበተኑ፤ ያልጠገቡ እንደ ሆነም ያንጐረጕራሉ።
16 እኔ ግን ለኃይልህ እቀኛለሁ፤ በምሕረትህም ማልዶ ደስ ይለኛል፤ በመከራዬ ቀን መጠጊያዬና አምባዬ ሆነኸኛልና።
17 ረዳቴ ሆይ፥ ለአንተ ለአምላኬ እዘምራለሁ፤ አንተ፥ አምላኬ፥ መጠጊያዬ ምሕረቴም ነህና።

ለመዘምራን አለቃ፤ የሶርያን ሁለቱን ወንዞችና የሶርያን ሶባልን ባቃጠለ ጊዜ ኢዮአብም ተመልሶ ከኤዶማውያን ሰዎች በጨው ሸለቆ አሥራ ሁለት ሺህ በገደለ ጊዜ ለትምህርት የዳዊት ቅኔ።
1 አቤቱ፥ ጣልኸን አፈረስኸንም፤ ተቈጣኸን ይቅርም አልኸን።
2 ምድርን አናወጥሃት አወክሃትም፤ ተናውጣለችና ቍስልዋን ፈውስ።
3 ለሕዝብህ ጭንቅን አሳየሃቸው፥ አስደንጋጩንም ወይን አጠጣኸን።
4 ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ፥ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው።
5 ወዳጆችህ እንዲድኑ በቀኝህ አድን፥ አድምጠኝም።
6 እግዚአብሔር በቅድስናው ተናገረ፤ ደስ ይለኛል፥ ሴኬምንም እካፈላለሁ፥ የሱኮትንም ሸለቆ እሰፍራለሁ።
7 ገለዓድ የእኔ ነው፥ ምናሴም የእኔ ነው፤ ኤፍሬም የራሴ መጠጊያ ነው። ይሁዳ ንጉሤ ነው፤
8 ሞዓብ መታጠቢያዬ ነው፥ በኤዶምያስ ላይ ጫማዬን እዘረጋለሁ፤ ፍልስጥኤም ይገዙልኛል።
9 ወደ ጽኑ ከተማ ማን ይወስደኛል? ማንስ እስከ ኤዶምያስ ይመራኛል?
10 አቤቱ፥ የጣልኸን አንተ አይደለህምን? አምላክ ሆይ፥ ከሠራዊታችን ጋር አትወጣም።
11 በመከራችን ረድኤትን ስጠን የሰውም ማዳን ከንቱ ነው።
12 በእግዚአብሔር ኃይልን እናደርጋለን እርሱ የሚያስጨንቁንን ያዋርዳቸዋልና።

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አምላክ ሆይ፥ ልመናዬን ስማ፥ ጸሎቴንም አድምጥ።
2 ልቤ ተስፋ በቈረጠ ጊዜ ከምድር ዳርቻ ወደ አንተ እጮኻለሁ፤ በድንጋይ ላይ ከፍ ከፍ አደረግኸኝ።
3 ጽኑ ግንብ በጠላት ፊት ተስፋዬም ሆነኸኛልና መራኸኝ።
4 በድንኳንህ ለዘላለም እኖራለሁ፤ በክንፎችህም ጥላ እጋረዳለሁ፤
5 አቤቱ፥ አንተ ስእለቴን ሰምተሃልና፤ ስምህንም ለሚፈሩ ርስትህን ሰጠሃቸው።
6 ለንጉሥ ከቀን በላይ ቀን ትጨምራለህ፥ ዓመታቱም ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሆናሉ።
7 በእግዚአብሔር ፊት ለዘላለም ይኖራል፤ ይጠብቁት ዘንድ ምሕረትንና እውነትን አዘጋጅለት።
8 እንዲሁ ለስምህ ለዘላለም እዘምራለሁ ስእለቴን ሁልጊዜ እፈጽም ዘንድ።
ለመዘምራን አለቃ፤ ስለ ኤዶታም፤ የዳዊት መዝሙር።
1 ነፍሴ ለእግዚአብሔር የምትገዛ አይደለችምን? መድኃኒቴ ከእርሱ ዘንድ ናትና።
2 እርሱ አምላኬ መድኃኒቴም ነውና፤ እርሱ መጠጊያዬ ነው፥ እጅግም አልታወክም።
3 እስከ መቼ በሰው ላይ ትቆማላችሁ? እናንተ ሁላችሁ እንዳዘነበለ ግድግዳ እንደ ፈረሰም ቅጥር ትገድላላችሁ።
4 ነገር ግን ክብሬን ይሽሩ ዘንድ መከሩ፥ ሐሰትንም ይወድዳሉ፤ በአፋቸው ይባርካሉ፥ በልባቸውም ይረግማሉ።
5 ነገር ግን፥ ነፍሴ ሆይ፥ አንቺ ለእግዚአብሔር ተገዢ፥ ተስፋዬ ከእርሱ ዘንድ ናትና።
6 እርሱ አምላኬ መድኃኒቴም ነውና፤ እርሱ መጠጊያዬ ነው፤ አልታወክም።
7 መድኃኒቴና ክብሬ በእግዚአብሔር ነው፤ የረድኤቴ አምላክ ተስፋዬም እግዚአብሔር ነው።
8 የሕዝብ ማኅበር ሁላችሁ፥ በእርሱ ታመኑ፥ ልባችሁንም በፊቱ አፍስሱ፤ እግዚአብሔር ረዳታችን ነው።
9 ነገር ግን የሰው ልጆች ከንቱ ናቸው፥ የሰው ልጆችም ሐሰተኞች ናቸው፤ በሚዛንም ይበድላሉ፥ እነርሱስ በፍጹም ከንቱ ናቸው።
10 ዓመፃን ተስፋ አታድርጉ፥ ቅሚያንም አትተማመኑት፤ ባለጠግነት ቢበዛ ልባችሁ አይኵራ።
11 እግዚአብሔር አንድ ጊዜ ተናገረ፥ እኔም ይህን ብቻ ሰማሁ፤ ኃይል የእግዚአብሔር ነው፥
12 አቤቱ፥ ምሕረትም ያንተ ነው፤ አንተ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ፍዳውን ትሰጣለህና።
በኤዶምያስ ምድረ በዳ በነበረ ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አምላኬ፥ አምላኬ፥ ወደ አንተ እገሠግሣለሁ፤ ነፍሴ አንተን ተጠማች፥ ሥጋዬ አንተን እንዴት ናፈቀች እንጨትና ውኃ በሌለበት በምድረ በዳ።
2 ኃይልህንና ክብርህን አይ ዘንድ እንዲሁ በመቅደስ ውስጥ ተመለከትሁህ።
3 ምሕረትህ ከሕይወት ይሻላልና ከንፈሮቼ ያመሰግኑሃል።
4 እንዲህ በሕይወቴ ዘመን አመሰግንሃለሁ፥ በአንተም ስም እጆቼን አነሣለሁ።
5 ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች፥ ከንፈሮቼም ስምህን በደስታ ያመሰግናሉ።
6 በመኝታዬም አስብሃለሁ፥ በማለዳም እናገርልሃለሁ፤
7 ረዳቴ ሆነኸኛልና፥ በክንፎችህም ጥላ ደስ ይለኛልና።
8 ነፍሴ በኋላህ ተከታተለች፥ እኔንም ቀኝህ ተቀበለችኝ።
9 እነርሱ ግን ነፍሴን ለከንቱ ፈለጓት፤ ወደ ምድር ጥልቅ ይገባሉ።
10 ለሰይፍ እጅ አልፈው ይሰጣሉ፥ የቀበሮም እድል ፈንታ ይሆናሉ።
11 ንጉሥ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለዋል፤ በእርሱ የሚምል ሁሉ ይከብራል፥ ሐሰትን የሚናገር አፍ ይዘጋልና።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ወደ አንተ በለመንሁ ጊዜ ጸሎቴን ስማኝ፥ ከጠላትም ፍርሃት ነፍሴን አድን።
2 ከክፉዎች ሸንጎ ከዓመፀኞችም ብዛት ሰውረኝ።
3 እንደ ሰይፍ ምላሳቸውን አሰሉ፤ መራራ ነገርን ለማድረግ፥
4 ንጹሕንም በስውር ለመንደፍ ቀስትን ገተሩ፤ ድንገት ይነድፉታል አይፈሩምም።
5 ለእነርሱ ለራሳቸው ክፉ ነገርን አጸኑ፤ ወጥመድን ይሰውሩ ዘንድ ተማከሩ፤ ማንስ ያየናል? ይላሉ።
6 ዓመፃን ፈልጓት፥ ሲፈትኑም አለቁ፤ የሰው የውስጥ አሳቡና ልቡ የጠለቀ ነው፥
7 እግዚአብሔርም ከፍ ከፍ ይላል። የድንገትም ፍላጻ፤ ያቈስላቸዋል፤
8 አንደበታቸው ያሰናክላቸዋል፥ የሚያዩአቸውም ሁሉ ይደነግጣሉ።
9 ሰዎች ሁሉ ፈሩ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ ተናገሩ፥ ሥራውንም አስተዋሉ።
10 ጻድቅ በእግዚአብሔር ደስ ይለዋል፥ በእርሱም ይታመናል፤ ልባቸውም የቀና ሁሉ እልል ይላሉ።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት የምስጋና መዝሙር።
1 አቤቱ፥ በጽዮን ለአንተ ምስጋና ይገባል፥ ለአንተም ጸሎት ይቀርባል።
2 ሥጋ ሁሉ ጸሎትን ወደምትሰማ ወደ አንተ ይመጣል።
3 የዓመፃ ነገር በረታብን፤ ኃጢአታችንንስ አንተ ይቅር ትላለህ።
4 አንተ የመረጥኸው በአደባባዮችህም ለማደር የተቀበልኸው ምስጉን ነው፤ ከቤትህ በረከት እንጠግባለን።
5 ቤተ መቅደስህ ቅዱስ ነው በጽድቅም ድንቅ ነው። በምድር ዳርቻ ሁሉና በሩቅ ባሕር ውስጥ ላሉ ተስፋቸው የሆንህ፥ አምላካችንና መድኃኒታችን ሆይ፥ ስማን።
6 በጉልበትህ ተራሮችን አጸናሃቸው፥ በኃይልም ታጥቀሃል።
7 የባሕሩን ጥልቀት የሞገድንም ጩኸት ታናውጣለህ።
8 ከተአምራትህ የተነሣ አሕዛብ ይደነግጣሉ፥ በምድር ዳርቻም የሚኖሩ ይፈራሉ፤ የጥዋትንና የማታን መውጫ ደስ ታሰኛቸዋለህ።
9 ምድርን ጐበኘሃት አጠጣሃትም፥ ብልጥግናዋንም እጅግ አበዛህ፤ የእግዚአብሔርን ወንዝ ውኃን የተመላ ነው፤ ምግባቸውን አዘጋጀህ እንዲሁ ታሰናዳለህና።
10 ትልምዋን ታረካለህ፥ ቦይዋንም ታስተካክላለህ፤ በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ፥ ቡቃያዋንም ትባርካለህ።
11 በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።
12 የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ።
13 ማሰማርያዎች መንጎችን ለበሱ፥ ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ፤ በደስታ ይጮኻሉ ይዘምራሉም።

ለመዘምራን አለቃ፤ የመነሣት የምስጋና መዝሙር።
1 በምድር ያላችሁ ሁሉ ለእግዚአብሔር እልል በሉ፥
2 ለስሙም ዘምሩ፥ ለምስጋናውም ክብርን ስጡ።
3 እግዚአብሔርን እንዲህ በሉት። ሥራህ ግሩም ነው፤ ኃይልህ ብዙ ሲሆን ጠላቶች ዋሹብህ።
4 በምድር ያሉ ሁሉ ለአንተ ይሰግዳሉ፥ ለአንተም ይዘምራሉ፥ ለስምህም ይዘምራሉ።
5 ኑ የእግዚአብሔርንም ሥራ እዩ፤ ከሰው ልጆች ይልቅ በምክር ግሩም ነው።
6 ባሕርን የብስ አደረጋት፥ ወንዙንም በእግር ተሻገሩ፤ በዚያ በእርሱ ደስ ይለናል።
7 በኃይሉ ለዘላለም ይገዛል፤ ዓይኖቹ ወደ አሕዛብ ይመለከታሉ፤ ዓመፀኞች ራሳቸውን ከፍ ከፍ አያድርጉ።
8 አሕዛብ ሆይ፥ አምላካችንን ባርኩ፥ የምስጋናውንም ድምፅ አሰሙ።
9 ነፍሴን በሕይወት ያኖራታል፥ እግሮቼንም ለመናወጥ አልሰጠም።
10 አቤቱ፥ ፈትነኸናልና፥ ብርንም እንደሚያነጥሩት አንጥረኸናልና።
11 ወደ ወጥመድ አገባኸን፥ በጀርባችንም መከራን አኖርህ።
12 በራሳችን ላይ ሰውን አስረገጥኸን፤ በእሳትና በውኃ መካከል አለፍን፥ ወደ ዕረፍትም አወጣኸን።
13 – 14 ከሚቃጠል መሥዋዕት ጋር ወደ ቤትህ እገባለሁ፤ በመከራዬ ጊዜ በአፌ የተናገርሁትን ከንፈሮቼም ያሉትን ስእለቴን ለአንተ እፈጽማለሁ።
15 ከዕጣንና ከወጠጤዎች ጋር ለሚቃጠል መሥዋዕት ፍሪዳን አቀርባለሁ፤ ላሞችንና ፍየሎችን እሠዋልሃለሁ።
16 እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሁሉ፥ ኑ፥ ስሙኝ፤ ለነፍሴ ያደረገላትን ልንገራችሁ።
17 በአፌ ወደ እርሱ ጮኽሁ፥ በአንደበቴም አመሰገንሁት።
18 በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር።
19 ስለዚህ እግዚአብሔር ሰማኝ፤ የልመናዬን ድምፅ አደመጠ።
20 ጸሎቴን ያልከለከለኝ ምሕረቱንም ከእኔ ያላራቀ እግዚአብሔር ይመስገን።

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ይማረን ይባርከንም፥ ፊቱንም በላያችን ያብራ፤
2 በአሕዛብ ሁሉ መካከል ማዳንህን፥ መንገድህንም በምድር እናውቅ ዘንድ።
3 አቤቱ፥ አሕዛብ ያመስግኑህ፥ አሕዛብ ሁሉ ያመስግኑህ።
4 ለአሕዛብ በቅን ትፈርድላቸዋለህና፥ አሕዛብንም በምድር ላይ ትመራለህና አሕዛብ ደስ ይበላቸው ሐሤትም ያድርጉ።
5 አቤቱ፥ አሕዛብ ያመስግኑህ፥ አሕዛብ ሁሉ ያመስግኑህ።
6 ምድር ፍሬዋን ሰጠች፤ እግዚአብሔር አምላካችንም ይባርከናል።
7 እግዚአብሔር ይባርከናል፥ የምድርም ዳርቻ ሁሉ ይፈሩታል።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት የምስጋና መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ይነሣ፥ ጠላቶቹም ይበተኑ፥ የሚጠሉትም ከፊቱ ይሽሹ።
2 ጢስ እንደሚበንን እንዲሁ ይብነኑ፤ ሰም በእሳት ፊት እንደሚቀልጥ፥ እንዲሁ ኅጥኣን ከእግዚአብሔር ፊት ይጥፉ።
3 ጻድቃንም ደስ ይበላቸው፥ በእግዚአብሔርም ፊት ሐሤት ያድርጉ፥ በደስታም ደስ ይበላቸው።
4 ለእግዚአብሔር ተቀኙ ለስሙም ዘምሩ፤ ወደ ምድረ በዳ ለወጣም መንገድ አድርጉ፤ ስሙ እግዚአብሔር ነው፥ በፊቱም ደስ ይበላችሁ፤ በፊቱም ይደነግጣሉ።
5 እግዚአብሔር በቅዱስ ቦታው ለድሀ አደጎች አባት፥ ለባልቴቶችም ዳኛ ነው።
6 እግዚአብሔር ብቸኞችን በቤት ያሳድራቸዋል፥ እስረኞችንም በኃይሉ ያወጣቸዋል፤ ዓመፀኞች ግን በምድረ በዳ ይኖራሉ።
7 አቤቱ፥ በሕዝብም ፊት በወጣህ ጊዜ፥ በምድረ በዳም ባለፍህ ጊዜ፥ ምድር ተናወጠች፥
8 ከሲና አምላክ ፊት፥ ከእስራኤል አምላክ ፊት ሰማያትም አንጠበጠቡ።
9 አቤቱ፥ የሞገስን ዝናብ ለርስትህ አዘነብህ፥ በደከመም ጊዜ አንተ አጸናኸው።
10 እንስሶችህ በውስጡ አደሩ፤ አቤቱ፥ በቸርነትህ ለድሆች አዘጋጀህ።
11 እግዚአብሔር ቃሉን ሰጠ፤ የሚያወሩት ብዙ ሠራዊት ናቸው።
12 የሠራዊት ነገሥታት ፈጥነው ይሸሻሉ፤ በቤትም የምትኖር ምርኮን ተካፈለች።
13 በርስቶች መካከል ብታድሩ፥ ከብር እንደ ተሠሩ እንደ ርግብ ክንፎች፥ በቅጠልያ ወርቅም እንደ ተለበጡ ላባዎችዋ ትሆናላችሁ።
14 ሰማያዊ ንጉሥ በላይዋ ባዘዘ ጊዜ፥ በሰልሞን ላይ በረዶ ዘነበ።
15 የእግዚአብሔር ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፤ የጸና ተራራና የለመለመ ተራራ ነው።
16 የጸኑ ተራራዎች ለምን ይነሣሉ? እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው፤ በእውነት እግዚአብሔር ለዘላለም ያድርበታል።
17 የእግዚአብሔር ሰረገላዎች የብዙ ብዙ ሺህ ናቸው፤ ጌታ በመቅደሱ በሲና በመካከላቸው ነው።
18 ወደ ላይ ዓረግህ፥ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ፥ ደግሞም ለዓመፀኞች በዚያ ያድሩ ዘንድ።
19 እግዚአብሔር አምላክ ቡሩክ ነው፤ እግዚአብሔር በየዕለቱ ቡሩክ ነው፤ የመድኃኒታችን አምላክ ይረዳናል።
20 አምላካችንስ የደኅንነት አምላክ ነው፤ ከሞት መውጣትም ከእግዚአብሔር ነው።
21 ነገር ግን እግዚአብሔር የጠላቶቹን ራስ፥ በኃጢአት የሚሄድንም የጠጕሩን አናት ይቀጠቅጣል።
22 እግዚአብሔር እንዲህ አለ። ከባሳን አመጣቸዋለሁ፥ ከባሕርም ጥልቅ እመልሳቸዋለሁ፥
23 እግሮችህ በደም ይረገጡ ዘንድ፥ የውሾችህ ምላስ በጠላቶች ላይ ይሆን ዘንድ።
24 የአምላኬ የንጉሥ መንገድ በመቅደሱ፥ አቤቱ፥ መንገድህ ተገለጠ።
25 አለቆች ቀደሙ፥ መዘምራንም ተከተሉ፤ ከበሮን በሚመቱ በቈነጃጅት መካከል።
26 እግዚአብሔርን በጉባኤ፥ ጌታችንንም በእስራኤል ምንጭ አመስግኑት።
27 ወጣቱ ብንያም በጕልበቱ በዚያ አለ፥ ገዦቻቸው የይሁዳ አለቆች የዛብሎን አለቆችና የንፍታሌምም አለቆች።
28 አቤቱ፥ ኃይልህን እዘዝ፤ አቤቱ፥ ይህንም ለእኛ የሠራኸውን አጽናው።
29 በኢየሩሳሌም ስላለው መቅደስህ ነገሥታት እጅ መንሻን ለአንተ ያመጣሉ።
30 በሸምበቆ ውስጥ ያሉትን አራዊት፥ በአሕዛብ ውስጥ ያሉትን የበሬዎችንና የወይፈኖችን ጉባኤ ገሥጽ፥ እንደ ብር የተፈተኑት አሕዛብ እንዳይዘጉ፤ ሰልፍን የሚወድዱትን አሕዛብን በትናቸው።
31 መኳንንት ከግብጽ ይመጣሉ፤ ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች።
32 የምድር ነገሥታት፥ ለእግዚአብሔር ተቀኙ፥ ለጌታም ዘምሩ።
33 በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ የኃይል ቃል የሆነ ቃሉን፥ እነሆ፥ ይሰጣል።
34 ለእግዚአብሔር ክብርን ስጡ፤ ግርማው በእስራኤል ላይ፥ ኃይሉም በደመናት ላይ ነው።
35 እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው፤ የእስራኤል አምላክ እርሱ ኃይልን ብርታትንም ለሕዝቡ ይሰጣል፤ እግዚአብሔርም ይመስገን።

ለመዘምራን አለቃ፤ በመለከቶች፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ውኃ እስከ ነፍሴ ደርሶብኛልና አድነኝ።
2 በጥልቅ ረግረግ ጠለቅሁ መቋሚያም የለኝም። ወደ ጥልቅ ባሕር ገባሁ ማዕበልም አሰጠመኝ።
3 በጩኸት ደከምሁ ጕሮሮዬም ሰለለ፤ አምላኬን ስጠብቅ ዓይኖቼ ፈዘዙ።
4 በከንቱ የሚጠሉኝ ከራሴ ጠጕር በዙ፤ በዓመፅ ያሚያሳድዱኝ ጠላቶቼ በረቱ፤ በዚያን ጊዜ ያልቀማሁትን መለስሁ።
5 አቤቱ፥ አንተ ስንፍናዬን ታውቃለህ፥ ኃጢአቴም ከአንተ አልተሰወረም።
6 አቤቱ የሠራዊት አምላክ፥ ተስፋ የሚያደርጉህ በእኔ አይፈሩ፤ የእስራኤል አምላክ ሆይ፥ የሚሹህ በእኔ አይነወሩ።
7 ስለ አንተ ስድብን ታግሻለሁና፥ እፍረትም ፊቴን ሸፍናለችና።
8 ለወንድሞቼ እንደ ሌላ፥ ለእናቴ ልጆችም እንደ እንግዳ ሆንሁባቸው፥
9 የቤትህ ቅንዓት በልታኛለችና፥ የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቆአልና።
10 ነፍሴን በጾም አስመረርሁአት፥ ለስድብም ሆነብኝ።
11 ማቅ ለበስሁ ምሳሌም ሆንሁላቸው።
12 በደጅ የሚቀመጡ በእኔ ይጫወታሉ፤ ወይን የሚጠጡ እኔን ይዘፍናሉ።
13 አቤቱ፥ በመልካሙ ጊዜ ጸሎቴ ወደ አንተ ነው፤ አቤቱ፥ በምሕረትህ ብዛት በማዳንህም እውነት አድምጠኝ።
14 እንዳይውጠኝ ከረግረግ አውጣኝ፤ ከሚጠሉኝና ከጥልቅ ውኃ አስጥለኝ።
15 የውኃው ማዕበል አያስጥመኝ፥ ጥልቁም አይዋጠኝ፥ ጕድጓድም አፉን በእኔ ላይ አይዝጋ።
16 አቤቱ፥ ምሕረትህ መልካም ናትና ስማኝ። እንደ ርኅራኄህም ብዛት ወደ እኔ ተመልከት፤
17 ከባሪያህም ፊትህን አትሰውር፤ ተጨንቄአለሁና ፈጥነህ አድምጠኝ።
18 ነፍሴን ተመልክተህ ተቤዣት፤ ስለ ጠላቶቼም አድነኝ።
19 አንተ ስድቤን እፍረቴንም ነውሬንም ታውቃለህ፤ የሚያስጨንቁኝ ሁሉ በፊትህ ናቸው።
20 ነፍሴ ስድብንና ኃሣርን ታገሠች፤ አስተዛዛኝም ተመኘሁ አላገኘሁም። የሚያጽናናኝም አጣሁ።
21 ለመብሌ ሐሞት ሰጡኝ፥ ለጥማቴም ሆምጣጤ አጠጡኝ።
22 ማዕዳቸው በፊታቸው ለወጥመድ ለፍዳ ለዕንቅፋት ትሁንባቸው፤
23 ዓይኖቻቸው እንዳያዩ ይጨልሙ፥ ጀርባቸውም ዘወትር ይጕበጥ።
24 መዓትህን በላያቸው አፍስስ፥ የቍጣህ መቅሠፍትም ያግኛቸው።
25 ማደሪያቸው በረሃ ትሁን፥ በድንኳኖቻቸውም የሚቀመጥ አይገኝ፤
26 አንተ የቀሠፍኸውን እነርሱ አሳድደዋልና፥ በቍስሌም ላይ ጥዝጣዜ ጨመሩብኝ።
27 በኃጢአታቸው ላይ ኃጢአትን ጨምርባቸው፥ በጽድቅህም አይግቡ።
28 ከሕያዋን መጽሐፍ ይደምሰሱ፥ ከጻድቃንም ጋር አይጻፉ።
29 እኔ ችግረኛና ቍስለኛ ነኝ፤ አቤቱ፥ የፊትህ መድኃኒት ይቀበለኝ።
30 የእግዚአብሔርን ስም በዝማሬ አመሰግናለሁ፥ በምስጋናም ከፍ ከፍ አደርገዋለሁ።
31 ቀንድና ጥፍር ካበቀለ ከእምቦሳ ይልቅ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘዋል።
32 ችግረኞች ያያሉ ደስ ይላቸዋል፤ እግዚአብሔርን ፈልጉ ሕያዋንም ሁኑ።
33 እግዚአብሔር ችግረኞችን ሰምቶአልና፥ እስረኞቹንም አልናቀምና።
34 ሰማይና ምድር ባሕርም በእርስዋም የሚንቀሳቀስ ሁሉ ያመሰግኑታል።
35 እግዚአብሔር ጽዮንን ያድናታልና፥ የይሁዳንም ከተሞች ይሠራልና፤ በዚያም ይቀመጣሉ ይወርሱአትማል።
36 የባሪያዎቹ ዘር ይኖሩባታል። ስሙንም የሚወድዱ በዚያ ይቀመጣሉ።

ለመዘምራን አለቃ፤ ለመታሰቢያ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እኔን ለማዳን ተመልከት፤ አቤቱ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።
2 ነፍሴን የሚሹአት ይፈሩ ይጐስቍሉም፥ ክፉንም የሚመክሩብኝ ወደ ኋላቸው ይመለሱ ይፈሩም።
3 እንኳ እንኳ የሚሉኝ አፍረው ወዲያው ወደ ኋላቸው ይመለሱ።
4 የሚሹህ ሁሉ በአንተ ሐሤት ያድርጉ ደስ ይበላቸው፤ ማዳንህን የሚወድዱ ሁልጊዜ። እግዚአብሔር ታላቅ ነው ይበሉ።
5 እኔ ችግረኛና ምስኪን ነኝ፤ አቤቱ፥ እርዳኝ፤ ረዳቴ ታዳጊዬም አንተ ነህ፤ አቤቱ፥ አትዘግይ።
አስቀድመው ስለ ማረኩ ስለ አሚናዳብ ልጆች የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ አንተን ታመንሁ፤ ለዘላለም አልፈር።
2 በጽድቅህ አስጥለኝ ታደገኝም፤ ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል አድነኝም።
3 በጠንካራ ቦታ ታድነኝ ዘንድ አምላክና መሸሸጊያ ሁነኝ፤ ኃይሌ መጠጊያዬ አንተ ነህና።
4 አምላኬ፥ ከኃጢአተኛ እጅ፥ ከዓመፀኛና ከግፈኛም እጅ አድነኝ።
5 አቤቱ፥ አንተ ተስፋዬ ነህና፥ እግዚአብሔር ሆይ፥ ከታናሽነቴ ጀምረህ መታመኛዬ ነህና።
6 ከማኅፀን ጀምሮ በአንተ ተደገፍሁ፥ ከእናቴም ሆድ ጀምሮ አንተ መሸሸጊያዬ ነህ፤ ሁልጊዜም ዝማሬዬ ለአንተ ነው።
7 ለብዙዎች መደነቂያ ሆንሁ፤ አንተ ግን ብርቱ መጠጊያዬ ነህ።
8 አፌን ምስጋና ምላ ሁልጊዜ ክብርህንና ግርማህን እዘምር ዘንድ።
9 በእርጅናዬ ዘመን አትጣለኝ፥ ጕልበቴም ባለቀ ጊዜ አትተወኝ።
10 ጠላቶቹ በላዬ ተናግረዋልና፤ ነፍሴንም የሚሹአት በአንድነት ተማክረዋልና፥ እንዲህም አሉ።
11 እግዚአብሔር ትቶታል፤ የሚያድነው የለምና ተከትላችሁ ያዙት።
12 አምላክ ሆይ፥ ከእኔ አትራቅ፤ አምላኬ ሆይ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።
13 ነፍሴን የሚቃወሙአት ይፈሩ ይጥፉም፥ ጕዳቴንም የሚፈልጉ እፍረትንና ኃሣርን ይልበሱ።
14 እኔ ግን ሁልጊዜ ተስፋ አደርጋለሁ፥ በምስጋናህም ሁሉ ላይ እጨምራለሁ።
15 ሥራን አላውቅምና አፌ ጽድቅህን ሁልጊዜም ማዳንህን ይናገራል።
16 በእግዚአብሔር ኃይል እገባለሁ፤ አቤቱ፥ ጽድቅህን ብቻ አስባለሁ።
17 አምላኬ፥ ከታናሽነቴ ጀምረህ አስተማርኸኝ፤ እስከ ዛሬም ተአምራትህን እነግራለሁ።
18 እስካረጅም እስክሸመግልም ድረስ፥ ለሚመጣ ትውልድም ሁሉ ክንድህን ኃይልህንም ጽድቅህንም እስክነግር ድረስ፥ አቤቱ፥ አትተወኝ።
19 አቤቱ፥ እስከ አርያም ታላላቅ ነገሮችን አደረግህ፤ አምላክ ሆይ፥ እንደ አንተ ያለ ማን ነው?
20 ብዙ ጭንቀትንና መከራን አሳይተኸኛልና፥ ተመለስህ ሕያውም አደረግኸኝ፤ ከምድር ጥልቅም እንደ ገና አወጣኸኝ።
21 ጽድቅህንም አብዛው፥ ተመልሰህም ደስ አሰኘኝ፥ ከጥልቅም እንደ ገና አወጣኸኝ።
22 እኔም በበገና ስለ እውነትህ አመሰግንሃለሁ፤ የእስራኤል ቅዱስ አምላክ ሆይ፥ በመሰንቆ እዘምርልሃለሁ።
23 ዝማሬን ባቀርብሁልህ ጊዜ ከንፈሮቼ ደስ ይላቸዋል፥ አንተ ያዳንሃትም ነፍሴ።
24 ጕዳቴን የሚሹ ባፈሩና በተነወሩ ጊዜ አንደበቴ ደግሞ ሁልጊዜ ጽድቅህን ይናገራል።

ስለ ሰሎሞን።
1 አቤቱ፥ ፍርድህን ለንጉሥ ስጥ፥ ጽድቅህንም ለንጉሥ ልጅ፥
2 ሕዝብህን በጽድቅ፥ ችግረኞችህንም በፍርድ ይዳኝ ዘንድ።
3 ተራሮችና ኰረብቶች ለሕዝብህ ሰላምን ይቀበሉ።
4 ለችግረኞች ሕዝብ በጽድቅ ትፈርዳለህ የድሆችንም ልጆች ታድናለህ፤ ክፉውንም ታዋርደዋለህ።
5 ፀሐይ በሚኖርበት ዘመን ሁሉ፥ በጨረቃም ፊት ለፊት ለልጅ ልጅ ይኖራል።
6 እንደ ዝናብ በታጨደ መስክ ላይ፥ በምድርም ላይ እንደሚንጠባጠብ ጠብታ ይወርዳል።
7 በዘመኑም ጽድቅ ያብባል፥ ጨረቃም እስኪያልፍ ድረስ ሰላም ብዙ ነው።
8 ከባሕር እስከ ባሕር ድረስ፥ ከወንዝም እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ይገዛል።
9 በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፥ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ።
10 የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብና የሳባ ነገሥታት እጅ መንሻን ያቀርባሉ።
11 ነገሥታት ሁሉ ይሰግዱለታል። አሕዛብም ሁሉ ይገዙለታል።
12 ችግረኛውን ከቀማኛው እጅ፥ ረዳት የሌለውንም ምስኪን ያድነዋልና።
13 ለችግረኛና ለምስኪን ይራራል፥ የችግረኞችንም ነፍስ ያድናል።
14 ከግፍና ከጭንቀት ነፍሳቸውን ያድናል፤ ስማቸው በፊቱ ክቡር ነው።
15 እርሱ ይኖራል ከዓረብም ወርቅ ይሰጡታል፤ ሁልጊዜም ወደ እርሱ ይጸልያሉ፥ ዘወትርም ይባርኩታል።
16 በምድር ውስጥ በተራሮች ላይ መጠጊያ ይሆናል፤ ፍሬውም ከሊባኖስ ይልቅ ከፍ ከፍ ይላል፤ እንደ ምድር ሣር በከተማ ይበቅላል።
17 ስሙ ለዘላለም ቡሩክ ይሆናል፥ ከፀሐይም አስቀድሞ ስሙ ይኖራል፤ የምድር አሕዛብ ሁሉ በእርሱ ይባረካሉም አሕዛብ ሁሉ ያመሰግኑታል።
18 ብቻውን ተአምራትን የሚያደርግ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይባረክ።
19 የምስጋናው ስም ለዓለምና ለዘላለም ይባረክ፤ ምስጋናውም ምድርን ሁሉ ይምላ። ይሁን፤ ይሁን።
20 የእሴይ ልጅ የዳዊት መዝሙር ተፈጸመ።
የአሳፍ መዝሙር።
1 ልባቸው ለቀና ለእስራኤል እግዚአብሔር እንዴት ቸር ነው።
2 እኔ ግን እግሮቼ ሊሰናከሉ፥ አረማመዴም ሊወድቅ ትንሽ ቀረ።
3 የኃጢአተኞችን ሰላም አይቼ በዓመፀኞች ቀንቼ ነበርና።
4 ለሞታቸው መጣጣር የለውምና፤ ኃይላቸውም ጠንካራ ነውና።
5 እንደ ሰው በድካም አልሆኑም፥ ከሰው ጋርም አልተገረፉም።
6 ስለዚህ ትዕቢት ያዛቸው፤ ኃጢአትንና በደልን ተጐናጸፉአት።
7 ዓይናቸው ስብ ስለ ሆነ ወጣ፤ ልባቸውም ከምኞታቸው ይልቅ አገኘ።
8 አስበው ክፉ ነገርን ተናገሩ። ከፍ ከፍ ብለውም በዓመፃ ተናገሩ።
9 አፋቸውን በሰማይ አኖሩ፥ አንደበታቸውም በምድር ውስጥ ተመላለሰ።
10 ስለዚህ ሕዝቤ ወደዚህ ይመለሳሉ፤ ፍጹም ጊዜም በላያቸው ይገኛል፤
11 እግዚአብሔር እንዴት ያውቃል? በልዑልስ ዘንድ በውኑ እውቀት አለ? ይላሉ።
12 እነሆ፥ እነዚህ ኃጢአተኞች ይደሰታሉ፥ ሁልጊዜም ባለጠግነታቸውን ያበዛሉ።
13 እንዲህም አልሁ። በውኑ ልቤን በከንቱ አጸደቅሁ፥ እጆቼንም በንጽሕና በከንቱ አጠብሁ።
14 ሁልጊዜም የተገረፍሁ ሆንሁ፥ መሰደቤም በማለዳ ነው።
15 እንደዚህ ብዬ ብናገር ኖሮ፥ እነሆ፥ የልጆችህን ትውልድ በበደልሁ ነበር።
16 አውቅም ዘንድ አሰብሁ፥ ይህ ግን በፊቴ ችግር ነበረ።
17 ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እስክገባ ድረስ፥ ፍጻሜአቸውንም እስካስተውል ድረስ።
18 በድጥ ስፍራ አስቀመጥኻቸው፥ ወደ ጥፋትም ጣልኻቸው።
19 እንዴት ለጥፋት ሆኑ! በድንገት አለቁ ስለ ኃጢአታቸውም ጠፉ።
20 ከሕልም እንደሚነቃ፥ አቤቱ፥ ስትነቃ ምልክታቸውን ታስነውራለህ።
21 ልቤ ነድዶአልና፥ ኵላሊቴም ቀልጦአልና፤
22 እኔ የተናቅሁ ነኝ አላውቅሁምም፥ በአንተ ዘንድም እንደ እንስሳ ሆንሁ።
23 እኔ ግን ዘወትር ከአንተ ጋር ነኝ፥ ቀኝ እጄንም ያዝኸኝ።
24 በአንተ ምክር መራኸኝ፤ ከክብር ጋር ተቀበልኸኝ።
25 በሰማይ ያለኝ ምንድር ነው? በምድርስ ውስጥ ከአንተ ዘንድ ምን እሻለሁ?
26 የልቤ አምላክ ሆይ፥ ልቤና ሥጋዬ አለቀ፤ እግዚአብሔር ግን ለዘላለም እድል ፈንታዬ ነው።
27 እነሆ፥ ከአንተ የሚርቁ ይጠፋሉና ከአንተ ርቀው የሚያመነዝሩትንም ሁሉ አጠፋኻቸው።
28 ለእኔ ግን ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ይሻለኛል፤ መታመኛዬም እግዚአብሔር ነው በጽዮን ልጅ በሮች ምስጋናህን ሁሉ እናገር ዘንድ።

የአሳፍ ትምህርት።
1 አቤቱ፥ ስለ ምን ለዘወትር ጣልኸኝ? በማሰማርያህ በጎች ላይስ ቍጣህን ስለ ምን ተቈጣህ?
2 አስቀድመህ የፈጠርሃትን ማኅበርህን፥ የተቤዤሃትንም የርስትህን በትር፥ በእርስዋ ያደርህባትን የጽዮንን ተራራ አስብ።
3 ጠላት በቅዱሳንህ ላይ እንደ ከፋ መጠን፥ ሁልጊዜም በትዕቢታቸው ላይ እጅህን አንሣ።
4 ጠላቶችህ በበዓል መካከል ተመኩ፤ የማያውቁትንም ምልክት ምልክታቸው አደረጉ።
5 እንደ ላይኛው መግቢያ ውስጥ በዱር እንዳሉም እንጨቶች፥ በመጥረቢያ በሮችዋን ሰበሩ።
6 እንዲሁ በመጥረቢያና በመዶሻ ሰበሩአት።
7 መቅደስህን በእሳት አቃጠሉ፤ የስምህንም ማደሪያ በምድር ውስጥ አረከሱ።
8 አንድ ሆነው በልባቸው በየሕዝባቸው። ኑ፥ የእግዚአብሔርን በዓሎች ከምድር እንሻር አሉ።
9 ምልክታችንን አናይም ከእንግዲህ ወዲህም ነቢይ የለም፤ እስከ መቼ እንዲኖር የሚያውቅ በኛ ዘንድ የለም።
10 አቤቱ፥ ጠላት እስከ መቼ ይሳደባል? ስምህን ጠላት ሁልጊዜ ያቃልላልን?
11 ቀኝህንም በብብትህ መካከል፥ እጅህንም ፈጽመህ ለምን ትመልሳለህ?
12 እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፥ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ።
13 አንተ ባሕርን በኃይልህ አጸናሃት፤ አንተ የእባቦችን ራስ በውኃ ውስጥ ሰበርህ።
14 አንተም የዘንዶውን ራሶች ቀጠቀጥህ፤ ለኢትዮጵያ ሰዎችም ምግባቸውን ሰጠሃቸው።
15 አንተ ምንጮቹንና ፈሳሾቹን ሰነጠቅህ፤ አንተ ሁልጊዜ የሚፈስሱትን ወንዞች አደረቅህ።
16 ቀኑ የአንተ ነው ሌሊቱም የአንተ ነው፤ አንተ ፀሓዩንና ጨረቃውን አዘጋጀህ።
17 አንተ የምድርን ዳርቻ ሁሉ ሠራህ፤ በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ።
18 ይህን ፍጥረትህን አስብ። ጠላት እግዚአብሔርን ተላገደ፥ ሰነፍ ሕዝብም ስሙን አስቈጣ።
19 የምትገዛልህን ነፍስ ለአራዊት አትስጣት፤ የችግረኞችህን ነፍስ ለዘወትር አትርሳ።
20 ወደ ኪዳንህ ተመልከት፥ የምድር የጨለማ ስፍራዎች በኅጥኣን ቤቶች ተሞልተዋልና።
21 ችግረኛ አፍሮ አይመለስ፤ ችግረኛና ምስኪን ስምህን ያመሰግናሉ።
22 አቤቱ፥ ተነሥ በቀልህንም ተበቀል፤ ሰነፎች ሁልጊዜም የተላገዱህን አስብ።
23 የባሪያዎችህን ቃል አትርሳ፤ የጠላቶችህ ኵራት ሁልጊዜ ወደ አንተ ይወጣል።

ለመዘምራን አለቃ፤ አታጥፋ። የአሳፍ የምስጋና መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እናመሰግንሃለን እናመሰግንሃለን ስምህንም እንጠራለን፤ ተኣምራትህን ሁሉ እናገራለሁ።
2 ጊዜውን ስቀበል እኔ በቅን እፈርዳለሁ።
3 ምድርና በእርስዋ ውስጥ የሚኖሩት ሁሉ ቀለጡ፥ እኔም ምሰሶችዋን አጠናሁ።
4 ዓመፀኞችን። አትበድሉ አልኋቸው፥ ኃጢአተኞችንም። ቀንዳችሁን አታንሡ፤
5 ቀንዳችሁን እስከ ላይ አታንሡ፥ በእግዚአብሔርም ላይ ዓመፅን አትናገሩ።
6 ክብር ከምሥራቅ ወይም ከምዕራብ ወይም ከምድረ በዳ የለምና፤
7 እግዚአብሔር ፈራጅ ነውና ይህን ያዋርዳል ይህንም ያከብራል።
8 ጽዋ በእግዚአብሔር እጅ ነውና፤ ያልተቀላቀለ የወይን ጠጅ ሞላበት፤ ከዚህ ወደዚያ አገላበጠው፥ ነገር ግን አተላው አልፈሰሰም፤ የምድር ኃጢአተኞች ሁሉ ይጠጡታል።
9 እኔ ግን ለዘላለም ደስ ይለኛል፥ ለያዕቆብም አምላክ ዝማሬን አቀርባለሁ።
10 የኅጥኣንን ቀንዶች ሁሉ እሰብራለሁ፤ የጻድቃን ቀንዶች ግን ከፍ ከፍ ይላሉ።
ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ ስለ አሦራውያን፤ የአሳፍ የምስጋና መዝሙር።
1 እግዚአብሔር በይሁዳ ታወቀ፥ ስሙም በእስራኤል ታላቅ ነው።
2 ስፍራው በሳሌም፥ ማደሪያውም በጽዮን ነው።
3 በዚያም የቀስትን ኃይል፥ ጋሻን ሰይፍን ሰልፍንም ሰበረ፤ በዚያም ቀንዶችን ሰበረ።
4 አንተ በዘላለም ተራሮች ሆነህ በድንቅ ታበራለህ።
5 ልበ ሰነፎች ሁሉ ደነገጡ፥ እንቅልፋቸውንም አንቀላፉ፤ ባለጠጎች ሁሉ በእነርሱ እጅ ምንም አላገኙም።
6 የያዕቆብ አምላክ ሆይ፥ ከተግሣጽህ የተነሣ ፈረሰኞች ሁሉ አንቀላፉ።
7 አንተ ግን፥ አንተ ግሩም ነህ፤ ቍጣህን ማን ይቃወማል?
8 ፍርድን ከሰማይ አሰማህ፤ ምድር ፈራች ዝምም አለች፥
9 ልበ የዋሃን ያድን ዘንድ እግዚአብሔር ለፍርድ በተነሣ ጊዜ።
10 ሰው በፈቃዱ ያመሰግንሃልና፥ ከሕሊናቸው ትርፍም በዓልህን ያደርጋሉ።
11 ለአምላካችን ለእግዚአብሔር ስእለትን ክፈሉ፤ በዙሪያው ያሉ ሁሉ እጅ መንሻን ለሚያስፈራው ያገባሉ።
12 የመኳንንትን ነፍስ ያወጣል፤ በምድርም ነገሥታት ዘንድ ያስፈራል።
ለመዘምራን አለቃ፤ ስለ ኤዶታም፤ የአሳፍ መዝሙር።
በቃሌ ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፥ ቃሌም ወደ 1 እግዚአብሔር ነው፥ እርሱም አደመጠኝ።
2 በመከራዬ ቀን እግዚአብሔርን ፈለግሁት፤ እጆቼ በሌሊት በፊቱ ናቸው፥ አላረፍሁምም፥ ነፍሴም መጽናናትን አልቻለችም።
3 እግዚአብሔርን አሰብሁት ደስ አለኝም፤ ተናገርሁ፥ ነፍሴም ፈዘዘች።
4 ዓይኖቼ እንዲተጉ ያዝሃቸው፤ ደነገጥሁ አልተናገርሁም።
5 የዱሮውን ዘመን አሰብሁ፤ የዘላለሙን ዓመታት አሰብሁ፤ አጠናጠንሁም
6 በሌሊት ከልቤ ጋር ተጫወትሁ፥ ነፍሴንም አነቃቃኋት።
7 እግዚአብሔር ለዘላለም ይጥላልን? እንግዲህስ ቸርነቱን አይጨምርምን?
8 ለዘላለምስ ምሕረቱ ለልጅ ልጅ ተቈረጠችን? የተናገረውስ ቃል አልቆአልን?
9 እግዚአብሔርስ ሞገሱን ረሳን? በቍጣውስ ምሕረቱን ዘጋውን?
10 ይህ ድካሜ ነው አልሁ፥ የልዑል ቀኝ እንደ ተለወጠ።
11 የእግዚአብሔርን ሥራ አስታወስሁ፤ የቀደመውን ተአምራትህን አስታወሳለሁና፤
12 በምግባርህም ሁሉ እናገራለሁ፥ በሥራህም እጫወታለሁ።
13 አቤቱ፥ መንገድህ በመቅደስ ውስጥ ነው፤ እንደ አምላካችን ያለ ታላቅ አምላክ ማን ነው?
14 ተኣምራትን የምታደርግ አምላክ አንተ ነህ። ለሕዝብህ ኃይልን አስታወቅሃቸው።
15 የያዕቆብንና የዮሴፍን ልጆች፥ ሕዝብህን በክንድህ አዳንሃቸው።
16 አቤቱ፥ ውኆች አዩህ፥ ውኆችም አይተውህ ፈሩ፤ ጥልቆች ተነዋወጡ፥ ውኆችም ጮኹ።
17 ደመኖች ድምፅን ሰጡ፥ ፍላጾችህም ወጡ።
18 የነጐድጓድህ ድምፅ በዐውሎ ነበረ፤ መብረቆች ለዓለም አበሩ፤ ምድር ተናወጠች ተንቀጠቀጠችም።
19 መንገድህ በባህር ውስጥ ነው፥ ፍለጋህም በብዙ ውኆች ነው፥ አረማመድህም አልታወቀም።
20 በሙሴና በአሮን እጅ ሕዝብህን እንደ በጎች መራሃቸው።

የአሳፍ ትምህርት።
1 ሕዝቤ ሆይ፥ ሕጌን አድምጡ፤ ጆሮአችሁንም ወደ አፌ ቃል አዘንብሉ።
2 አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ፥ ያለውንም ተምሳሊት እናገራለሁ።
3 የሰማነውንና ያውቅነውን፥ አባቶቻችንም የነገሩንን፥ ለሚመጣ ትውልድ ከልጆቻቸው አልሰወሩም።
4 የእግዚአብሔርን ምስጋናና ኃይሉን ያደረገውንም ተኣምራት ተናገሩ።
5 ለልጆቻቸው ያስታውቅ ዘንድ ለአባቶቻችን ያዘዘውን ምስክር በያዕቆብ አቆመ፥ በእስራኤልም ሕግን ሠራ፤
6 የሚመጣ፥ ትውልድ የሚወለዱም ልጆች ያውቁ ዘንድ፥ ተነሥተው ለልጆቻቸው ይነግራሉ፤
7 ተስፋቸውን በእግዚአብሔር እንዲያደርጉ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እንዳይረሱ፥ ትእዛዙንም እንዲጠብቁ፤
8 እንደ አባቶቻቸው እንዳይሆኑ ጠማማና የምታስመርር ትውልድ፥ ልብዋን ያላቀናች ትውልድ፥ ነፍስዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታመነች።
9 የኤፍሬም ልጆች ለሰልፍ ታጥቀው ቀስትንም ገትረው በሰልፍ ቀን ወደ ኋላ ተመለሱ።
10 የእግዚአብሔርን ኪዳን አልጠበቁም፥ በሕጉም ለመመላለስ እንቢ አሉ፤
11 መልካም ሥራውንና ያሳያቸውን ተኣምራቱን ረሱ፥
12 በግብጽ አገርና በጣኔዎስ በረሃ በአባቶቻቸው ፊት የሠራውን ተኣምራት።
13 ባሕርን ከፍሎ አሳለፋቸው፤ ውኆችን እንደ ክምር አቆመ።
14 ቀን በደመና መራቸው፥ ሌሊቱንም ሁሉ በእሳት ብርሃን።
15 ዓለቱን በምድረ በዳ ሰነጠቀ፤ ከጥልቅ እንደሚገኝ ያህል በብዙ አጠጣቸው።
16 ውኃን ከጭንጫ አወጣ፥ ውኃንም እንደ ወንዞች አፈሰሰ።
17 ነገር ግን ይበድሉት ዘንድ እንደ ገና ደገሙ፥ ልዑልንም በምድረ በዳ አስቈጡት።
18 ለነፍሳቸው መብልን ይፈልጉ ዘንድ፥ እግዚአብሔርን በልባቸው ፈተኑት።
19 እግዚአብሔርን እንዲህ ብለው አሙት። እግዚአብሔር በምድረ በዳ ማዕድን ያሰናዳ ዘንድ ይችላልን?
20 ዓለቱን መታ፤ ውኆችም ወጡ፥ ወንዞችም ጐረፉ፤ እንጀራን መስጠትስ ይችላልን? ለሕዝቡስ ማዕድን ያዘጋጃልን?
21 እግዚአብሔርም ይህን ሰምቶ ተቈጣ፤ በያዕቆብም ላይ እሳት ነደደ፥ መዓትም በእስራኤል ላይ መጣ፤
22 በእግዚአብሔር አላመኑምና፥ በመድኃኒቱም አልተማመኑምና።
23 ደመናውንም ከላይ አዘዘ፥ የሰማይንም ደጆች ከፈተ፤
24 ይበሉም ዘንድ መናን አዘነበላቸው፥ የሰማይንም እንጀራ ሰጣቸው።
25 የመላክትንም እንጀራ ሰው በላ ስንቅንም እስኪተርፋቸው ላከላቸው።
26 ከሰማይ የምሥራቅን ነፋስ አስነሣ፥ በኃይሉም የደቡብን ነፋስ አመጣ፤
27 ሥጋን እንደ አፈር፥ የሚበርሩትንም ወፎች እንደ ባሕር አሸዋ አዘነበላቸው፤
28 በሰፈራቸው መካከል፥ በድንኳናቸውም ዙሪያ ወደቀ።
29 በሉ እጅግም ጠገቡ፤ ምኞታቸውንም ሰጣቸው።
30 ከወደዱትም አላሳጣቸውም፤ መብላቸውም ገና በአፋቸው ሳለ፥
31 የእግዚአብሔር ቍጣ በላያቸው መጣ፥ ከእነርሱም ከፍ ያሉትን ገደለ፥ የእስራኤልንም ምርጦች አሰናከለ።
32 ከዚህም ሁሉ ጋር እንደ ገና በደሉ፥ ተኣምራቱንም አላመኑም፤
33 ቀኖቻቸውም በከንቱ አለቁ፥ ዓመቶቻቸውም በችኰላ።
34 በገደላቸውም ጊዜ ወዲያው ፈለጉት፤ ተመለሱ ወደ እግዚአብሔርም ገሠገሡ፤
35 ረዳታቸውም እግዚአብሔር፥ መድኃኒታቸውም ልዑል አምላክ እንደ ሆነ አሰቡ።
36 በአፋቸው ብቻ ወደዱት፤ በአንደበታቸውም ዋሹበት፤ v
37 ልባቸውም ከእርሱ ጋር አልቀናም፥ በቃል ኪዳኑም አልተማመኑትም።
38 እርሱ ግን መሓሪ ነው፥ ኃጢአታቸውንም ይቅር አላቸው፥ አላጠፋቸውምም፤ ቍጣውንም መመለስ አበዛ፥ መዓቱንም ሁሉ አላቃጠለም።
39 ወጥቶ የማይመለስ መንፈስ፥ ሥጋም እንደ ሆኑ አሰበ።
40 በምድረ በዳ ምን ያህል አስቈጡት፥ በበረሃም አሳዘኑት።
41 ተመለሱ፥ እግዚአብሔርንም ፈተኑት፥ የእስራኤልንም ቅዱስ አሳዘኑት።
42 እነርሱም እጁን አላሰቡም፥ ከጠላቶቻቸው እጅ ያዳነበትን ቀን፥
43 በግብጽ ያደረገውን ተኣምራቱን፥ በጣኔዎስም በረሃ ያደረገውን ድንቁን።
44 ወንዞቻቸውንም ወደ ደም ለወጠ፥ ምንጮቻቸውን ደግሞ እንዳይጠጡ።
45 ዝንቦችንም በላያቸው ሰደደባቸው፥ በሉአቸውም፤ በጓጉንቸርም አጠፋቸው።
46 ፍሬያቸውን ለኩብኩባ፥ ሥራቸውንም ለአንበጣ ሰጠ።
47 ወይናቸውን በበረዶ፥ በለሳቸውንም በአመዳይ አጠፋ።
48 እንስሶቻቸውን ለበረዶ፥ ሀብታቸውንም ለእሳት ሰጠ።
49 የመዓቱን መቅሠፍት በላያቸው ሰደደ፤ መቅሠፍትን መዓትንም መከራንም በክፉዎች መላእክት ሰደደ።
50 ለቍጣው መንገድን ጠረገ፤ ነፍሳቸውንም ከሞት አላዳናትም፥ እንስሶቻቸውንም በሞት ውስጥ ዘጋ፤
51 በኵሮቻቸውን ሁሉ በግብጽ፥ የድካማቸውንም መጀመሪያ በካም ድንኳኖች ገደለ።
52 ሕዝቡን ግን እንደ በጎች አሰማራቸው፥ እንደ መንጋም በምድረ በዳ መራቸው።
53 በተስፋም መራቸው አልፈሩምም፥ ጠላቶቻቸውንም ባሕር ደፈናቸው።
54 ወደ መቅደሱም ተራራ አገባቸው፥ ቀኙ ወደ ፈጠረችው ወደዚህች ተራራ፤
55 ከፊታቸውም አሕዛብን አባረረ፥ ርስቱንም በገመድ አካፈላቸው፥ የእስራኤልንም ወገኖች በቤታቸው አኖረ።
56 ነገር ግን ልዑል እግዚአብሔርን ፈተኑት አስቈጡትም፥ ምስክሩንም አልጠበቁም፤
57 ተመለሱም እንደ አባቶቻቸውም ከዱ፤ እንደ ጠማማ ቀስትም ተገለበጡ፤
58 በኰረብታ መስገጃዎቻቸውም አስቈጡት፥ በተቀረጹ ምስሎቻቸውም አስቀኑት።
59 እግዚአብሔርም ይህን ሰምቶ ተቈጣ፥ እስራኤልንም እጅግ ናቀ፤
60 የሴሎምን ማደሪያ ተዋት በሰዎች መካከል ያደረገባትን ድንኳኑን፤
61 ኃይላቸውን ለምርኮ፥ ሽልማቱንም በጠላት እጅ ሰጠ።
62 ሕዝቡንም በጦር ውስጥ ዘጋቸው፥ ርስቱንም ቸል አላቸው።
63 ጕልማሶቻቸውን እሳት በላቸው፥ ቈነጃጅቶቻቸውም አላዘኑም፤
64 ካህናቶቻቸውም በሰይፍ ወደቁ፥ ባልቴቶቻቸውም አላለቀሱላቸውም።
65 እግዚአብሔርም ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፥ የወይን ስካር እንደ ተወው እንደ ኃያልም ሰው፤
66 ጠላቶቹንም በኋላቸው መታ፤ የዘላለምን ኀሣር ሰጣቸው።
67 የዮሴፍንም ድንኳን ተዋት፥ የኤፍሬምንም ወገን አልመረጠውም፤
68 የይሁዳን ወገን ግን መረጠ፥ የወደደውን የጽዮንን ተራራ።
69 መቅደሱን እንደ አርያም ሠራ፥ ለዘላለምም በምድር ውስጥ መሠረታት።
70 ዳዊትንም ባሪያውን መረጠው፥ ከበጎቹም መንጋ ውስጥ ወሰደው፤
የአሳፍ መዝሙር።
1 አቤቱ፥ አሕዛብ ወደ ርስትህ ገቡ፤ የቅድስናህንም መቅደስ አረከሱ፥ ኢየሩሳሌምንም እንደ መደብ አደረጉአት።
2 የባሪያዎችህንም በድኖች ለሰማይ ወፎች መብል አደረጉ፥ የጻድቃንህንም ሥራ ለምድር አራዊት፤
3 ደማቸውንም በኢየሩሳሌም ዙሪያ እንደ ውኃ አፈሰሱ፥ የሚቀብራቸውም አጡ።
4 ለጎረቤቶቻችንም ስድብ ሆንን፥ በዙሪያችንም ላሉ ሣቅና ዘበት።
5 አቤቱ፥ እስከ መቼ ለዘላለም ትቈጣለህ? ቅንዓትህም እንደ እሳት ይነድዳል?
6 ስምህን በማይጠሩ መንግሥታት ላይ በማያውቁህም አሕዛብ ላይ መዓትህን አፍስስ፤
7 ያዕቆብን በልተውታልና፥ ስፍራውንም ባድማ አድርገዋልና።
8 የቀደመውን በደላችንን አታስብብን፥ ምሕረትህ በቶሎ ታግኘን፥ እጅግ ተቸግረናልና።
9 አምላካችንና መድኃኒታችን ሆይ፥ እርዳን፤ ስለ ስምህ ክብር፥ አቤቱ፥ ታደገን፥ ስለ ስምህም ኃጢአታችንን አስተሰርይልን።
10 አሕዛብ፥ አምላካቸው ወዴት ነው? እንዳይሉ፥ የፈሰሰውን የባሪያዎችህን ደም በቀል በዓይኖቻችን ፊት አሕዛብ ያወቁ፤
11 የእስረኞች ጩኸት ወደ ፊትህ ይግባ፤ እንደ ክንድህም ታላቅነት ሊገደሉ የተፈረደባቸውን አድን።
12 አቤቱ፥ የተዘባበቱብህን መዘባበታቸውን ለጎረቤቶቻችን ሰባት እጥፍ በብብታቸው ክፈላቸው።
13 እኛ ሕዝብህ ግን፥ የማሰማርያህም በጎች፥ ለዘላለም እናመሰግንሃለን፤ ለልጅ ልጅም ምስጋናህን እንናገራለን።

1 Give ear, O Shepherd of Israel, thou that leadest Joseph like a flock; thou that dwellest between the cherubims, shine forth.
2 Before Ephraim and Benjamin and Manasseh stir up thy strength, and come and save us.
3 Turn us again, O God, and cause thy face to shine; and we shall be saved.
4 O Lord God of hosts, how long wilt thou be angry against the prayer of thy people?
5 Thou feedest them with the bread of tears; and givest them tears to drink in great measure.
6 Thou makest us a strife unto our neighbours: and our enemies laugh among themselves.
7 Turn us again, O God of hosts, and cause thy face to shine; and we shall be saved.
8 Thou hast brought a vine out of Egypt: thou hast cast out the heathen, and planted it.
9 Thou preparedst room before it, and didst cause it to take deep root, and it filled the land.
10 The hills were covered with the shadow of it, and the boughs thereof were like the goodly cedars.
11 She sent out her boughs unto the sea, and her branches unto the river.
12 Why hast thou then broken down her hedges, so that all they which pass by the way do pluck her?
13 The boar out of the wood doth waste it, and the wild beast of the field doth devour it.
14 Return, we beseech thee, O God of hosts: look down from heaven, and behold, and visit this vine;
15 And the vineyard which thy right hand hath planted, and the branch that thou madest strong for thyself.
16 It is burned with fire, it is cut down: they perish at the rebuke of thy countenance.
17 Let thy hand be upon the man of thy right hand, upon the son of man whom thou madest strong for thyself.
18 So will not we go back from thee: quicken us, and we will call upon thy name.
19 Turn us again, O Lord God of hosts, cause thy face to shine; and we shall be saved.

 

ለመዘምራን አለቃ፤ በዋሽንት፤ የአሳፍ መዝሙር።
1 በረድኤታችን በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፥ ለያዕቆብም አምላክ እልል በሉ።
2 ዝማሬውን አንሡ ከበሮንም ስጡ፥ ደስ የሚያሰኘውን በገና ከመሰንቆ ጋር፤
3 በመባቻ ቀን በከፍተኛው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤
4 ለእስራኤል ሥርዓቱ ነውና፥ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ።
5 ከግብጽ በወጣ ጊዜ ለዮሴፍ ምስክር አቆመው። ያላወቅሁትን ቋንቋ ሰማሁ።
6 ጫንቃውን ከሸክም፥ እጆቹንም በቅርጫት ከመገዛት አራቅሁ።
7 በመከራህ ጊዜ ጠራኸኝ አዳንሁህም፥ በተሰወረ ዐውሎም መለስሁልህ፥ በክርክር ውኃ ዘንድም ፈተንሁህ።
8 ሕዝቤ ሆይ፥ስማኝ እነግርሃለሁም፤ እስራኤል ሆይ፥ እመሰክርልሃለሁ።
9 አንተስ ብትሰማኝ ሌላ አምላክ አይሆንልህም፥ ለሌላ አምላክም አትሰግድም።
10 ከግብጽ ምድር ያወጣሁህ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ነኝና፤ አፍህን አስፋ እሞላዋለሁም።
11 ሕዝቤ ግን ቃሌን አልሰሙኝም፥ እስራኤልም አላዳመጠኝም።
12 እንደ ልባቸው ሥራ ተውኋቸው፥ በልባቸውም አሳብ ሄዱ።
13 ሕዝቤስ ሰምቶኝ ቢሆን፥ እስራኤልም በመንገዴ ሄደው ቢሆን፤
14 ጠላቶቻቸውን ፈጥኜ ባዋረድኋቸው ነበር፥ በሚያስጨንቋቸውም ላይ እጄን በጣልሁ ነበር፤
15 የእግዚአብሔር ጠላቶችም በተገዙለት ነበር፥ ዘመናቸውም ለዘላለም በሆነ ነበር፤
16 ከስንዴም ስብ ባበላቸው ነበር፥ ከዓለቱም ማር ባጠገባቸው ነበር።
የአሳፍ መዝሙር።
1 እግዚአብሔር በአማልክት ማኅበር ቆመ፥ በአማልክትም መካከል ይፈርዳል።
2 እስከ መቼ ሐሰትን ትፈርዳላችሁ? እስከ መቼ ለኃጢአተኞች ፊት ታደላላችሁ?
3 ለድሆችና ለድሀ አደጎች ፍረዱ፤ ለችግረኛውና ለምስኪኑ ጽድቅ አድርጉ፤
4 ብቸኛውንና ችግረኛውን አድኑ፤ ከኃጢአተኞችም እጅ አስጥሉአቸው።
5 አያውቁም፥ አያስተውሉም፤ በጨለማ ውስጥ ይመላለሳሉ፤ የምድር መሠረቶች ሁሉ ተናወጡ።
6 እኔ ግን። አማልክት ናችሁ፥ ሁላችሁም የልዑል ልጆች ናችሁ፤
7 ነገር ግን እንደ ሰው ትሞታላችሁ፥ ከአለቆችም እንደ አንዱ ትወድቃላችሁ አልሁ።
8 አቤቱ፥ ተነሥ፥ በምድር ላይ ፍርድ፥ አንተ አሕዛብን ሁሉ ትወርሳለህና።
የአሳፍ የምስጋና መዝሙር።
1 አቤቱ፥ እንደ አንተ ማን ነው? አቤቱ፥ ዝም አትበል፥ ቸልም አትበል።
2 እነሆ፥ ጠላቶችህ ጮኽዋልና፥ የሚጠሉህም ራሳቸውን አንሥተዋልና።
3 ሕዝብህን በምክር ሸነገሉአቸው፥ በቅዱሳንህም ላይ ተማከሩ።
4 ኑ ከሕዝብ እናጥፋቸው፥ ደግሞም የእስራኤል ስም አይታሰብ አሉ።
5 አንድ ሆነው በአንተ ላይ ተማከሩ፤ በአንተ ላይ ቃል ኪዳን አደረጉ፤
6 የኤዶማውያን ድንኳኖች እስማኤላውያንም፥ ሞዓብም አጋራውያንም፥
7 ጌባል አሞንም አማሌቅም፥ ፍልስጥኤማውያንም ከጢሮስ ሰዎች ጋር፤
8 አሦርም ከእነርሱ ጋር ተባበረ፥ ለሎጥ ልጆችም ረዳት ሆኑአቸው።
9 እንደ ምድያምና እንደ ሲሣራ፥ በቂሶንም ወንዝ እንደ ኢያቢስ አድርግባቸው።
10 በዓይንዶር ጠፉ፥ እንደ ምድርም ጕድፍ ሆኑ።
11 አለቆቻቸውን እንደ ሔሬብና እንደ ዜብ፥ ታላላቆቻቸውንም እንደ ዛብሄልና እንደ ስልማና አድርጋቸው።
12 የእግዚአብሔርን መሠዊያ እንወርሳለን የሚሉትን።
13 አምላኬ ሆይ፥ እንደ ትቢያ በነፋስ ፊትም እንደ ገለባ አድርጋቸው።
14 እሳት ዱርን እንደሚያቃጥል፥ ነበልባልም ተራሮች እንደሚያነድድ፥
15 እንዲሁ በቍጣህ አሳድዳቸው፥ በመቅሠፍትህም አስደንግጣቸው።
16 ፊታቸውን እፍረት ሙላው፥ አቤቱ፥ ስምህንም ይፈልጋሉ።
17 ይፈሩ ለዘላለሙም ይታወኩ፤ ይጐስቍሉ ይጥፉም።
18 ስምህም እግዚአብሔር እንደ ሆነ፥ በምድር ሁሉ ላይም አንተ ብቻ ልዑል እንደ ሆንህ ይወቁ።
ለመዘምራን አለቃ፤ በዋሽንት፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።
1 የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ ማደሪያዎችህ እንደምን የተወደዱ ናቸው!
2 ነፍሴ የእግዚአብሔርን አደባባዮች ትወድዳለች ትናፍቅማለች፤ ልቤም ሥጋዬም በሕያው አምላክ ደስ ተሰኘ።
3 ወፍ ለእርስዋ ቤትን አገኘች፥ ዋኖስም ጫጩቶችዋን የምታኖርበት ቤት አገኘች፤ የሠራዊት አምላክ ንጉሤም አምላኬም ሆይ፥ እርሱ መሠዊያህ ነው።
4 በቤትህ የሚኖሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው፤ ለዓለምና ለዘላለምም ያመሰግኑሃል።
5 አቤቱ፥ እርዳታው ከአንተ ዘንድ የሆነለት፥ በልቡም የላይኛውን መንገድ የሚያስብ ሰው ምስጉን ነው።
6 በልቅሶ ሸለቆ ውስጥ በወሰነው ስፍራ የሕግ መምህር በረከትን ይሰጣልና።
7 ከኃይል ወደ ኃይል ይሄዳሉ፤ የአማልክት አምላክ በጽዮን ይታያል።
8 የሠራዊት አምላክ አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማ፤ የያዕቆብ አምላክ ሆይ፥ አድምጥ።
9 አቤቱ፥ መታመናችንን እይልን፥ ወደ ቀባኸውም ፊት ተመልከት።
10 ከአእላፍ ይልቅ በአደባባዮችህ አንዲት ቀን ትሻላለች፤ በኃጥኣን ድንኳኖች ከመቀመጥ ይልቅ፥ በእግዚአብሔር ቤት እጣል ዘንድ መረጥሁ።
11 እግዚአብሔር አምላክ ምሕረትንና እውነትን ስለ ወደደ፥ ሞገስንና ክብርን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር በቅንነት የሚሄዱትን ከመልካም ነገር አያሳጣቸውም።
12 የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በአንተ የታመነ ሰው ምስጉን ነው።
ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ለምድርህ ሞገስን አደረግህ፥ የያዕቆብንም ምርኮ መለስህ።
2 የሕዝብህን ኃጢአት አስቀረህ፥ አበሳቸውንም ሁሉ ከደንህ።
3 መዓትህንም ሁሉ አስወገድህ፤ ከቍጣህ መቅሠፍት ተመለስህ።
4 የመድኃኒታችን አምላክ ሆይ፥ መልሰን፥ ቍጣህንም ከእኛ መልስ።
5 በውኑ ለዘላለም ትቈጣናለህን? ቍጣህንስ ለልጅ ልጅ ታስረዝማለህን?
6 አቤቱ፥ ትመለሳለህ ታድነንማለህ፤ ሕዝቡም በአንተ ደስ ይላቸዋል።
7 አቤቱ፥ ምሕረትህን አሳየን፥ አቤቱ፥ መድኃኒትህንም ስጠን።
8 እግዚአብሔር አምላክ የሚናገረውን እሰማለሁ፤ ሰላምን ለሕዝቡና ለቅዱሳኑ ልባቸውንም ወደ እርሱ ለሚመልሱ ይናገራልና።
9 ነገር ግን ክብር በምድራችን ያድር ዘንድ ማዳኑ ለሚፈሩት ቅርብ ነው፤
10 ምሕረትና እውነት ተገናኙ፤ ጽድቅና ሰላም ተስማሙ።
11 እውነት ከምድር በቀለች፥ ጽድቅም ከሰማይ ተመለከተች።
12 እግዚአብሔርም በጎ ነገርን ይሰጣል፥ ምድራችንም ፍሬዋን ትሰጣለች።
13 ጽድቅ በፊቱ ይሄዳል፥ ፍለጋውንም በመንገድ ውስጥ ያኖራል።
የዳዊት ጸሎት።
1 አቤቱ፥ ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል አድምጠኝም፥ ችግረኛና ምስኪን ነኝና።
2 ቅዱስ ነኝና ነፍሴን ጠብቅ፤ አምላኬ ሆይ፥ አንተን የታመነውን ባሪያህን አድነው።
3 አቤቱ፥ ቀኑን ሁሉ ወደ አንተ እጮኻለሁና ማረኝ።
4 የባሪያህን ነፍስ ደስ አሰኛት፥ አቤቱ፥ ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁና።
5 አቤቱ፥ አንተ መሓሪና ይቅር ባይ ነህና፥ ምሕረትህም ለሚጠሩህ ሁሉ ብዙ ነውና።
6 አቤቱ፥ ጸሎቴን አድምጥ፥ የልመናዬንም ድምፅ ስማ።
7 ትመልስልኛለህና በመከራዬ ቀን ወደ አንተ እጠራለሁ።
8 አቤቱ፥ ከአማልክት የሚመስልህ የለም፥ እንደ ሥራህም ያለ የለም።
9 ያደረግሃቸው አሕዛብ ሁሉ ይመጣሉ፥ አቤቱ፥ በፊትህም ይሰግዳሉ፥ ስምህንም ያከብራሉ፤
10 አቤቱ፥ ድንቅ የምታደርግ አንተ ታላቅ ነህና፥ አንተም ብቻህን ታላቅ አምላክ ነህና።
11 አቤቱ፥ መንገድህን ምራኝ፥ በእውነትህም እሄዳለሁ፤ ስምህን ለመፍራት ልቤ ደስ ይለዋል።
12 አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ በልቤ ሁሉ አመሰግንሃለሁ፥ ለዘላለምም ስምህን አከብራለሁ፤
13 ምሕረትህ በእኔ ላይ ታላቅ ናትና፥ ነፍሴንም ከታችኛይቱ ሲኦል አድነሃታልና።
14 አቤቱ፥ ዓመፀኞች በእኔ ላይ ተነሥተዋል፥ የክፉዎችንም ማኅበር ነፍሴን ፈለጉአት፤ በፊታቸውም አላደረጉህም።
15 አቤቱ፥ አንተ ግን መሓሪና ርኅሩኅ አምላክ ነህ፤ መዓትህ የራቀ ምሕረትህም እውነትህም የበዛ፤
16 ወደ እኔ ተመልከት ማረኝም፤ ለባሪያህ ኃይልህን ስጥ፥ የሴት ባሪያህንም ልጅ አድን።
17 ምልክትንም ለመልካም ከእኔ ጋር አድርግ፤ የሚጠሉኝ ይዩ ይፈሩም፥ አቤቱ፥ አንተ ረድተኸኛልና፥ አጽንተኸኛልምና።
የቆሬ ልጆች የምስጋና መዝሙር።
1 መሠረቶቹ በተቀደሱ ተራሮች ናቸው፤
2 ከያዕቆብ ድንኳኖች ይልቅ፥ እግዚአብሔር የጽዮንን ደጆች ይወድዳቸዋል።
3 የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ፥ በአንቺ የተከበረ ነገር ይባላል።
4 የሚያውቁኝን ረዓብንና ባቢሎንን አስባቸዋለሁ፤ እነሆ፥ ፍልስጥኤማውያን ጢሮስም የኢትዮጵያም ሕዝብ፥ እነዚህ በዚያ ተወለዱ።
5 ሰው እናታችን ጽዮን ይላል፥ በውስጥዋም ሰው ተወለደ፤ እርሱ ራሱም ልዑል መሠረታት።
6 እግዚአብሔር ለሕዝቡ፥ በውስጥዋም ለተወለዱት አለቆችዋ በመጽሐፍ ይነግራቸዋል።
7 በአንቺ የሚኖሩ ሁሉ ደስ እንደሚላቸው ይነግራቸዋል።
የቆሬ ልጆች የምስጋና መዝሙር። ለመዘምራን አለቃ በማኸላት ለመዘመር፤ የይዝራኤላዊው የኤማን ትምህርት።
1 አቤቱ፥ የመድኃኒቴ አምላክ፥ በቀንና በሌሊት በፊትህ ጮኽሁ፤
2 ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትግባ፥ ጆሮህንም ወደ ጩኸቴ አዘንብል፤
3 ነፍሴ መከራን ጠግባለችና፥ ሕይወቴም ወደ ሲኦል ቀርባለችና።
4 ወደ ጓድጓድ ከሚወርዱ ጋር ተቈጠርሁ፥ ረዳትም እንደሌለው ሰው ሆንሁ።
5 ለዘላለም እንደማታስባቸው፥ እንደ ተገደሉና በመቃብር ውስጥ እንደ ተጣሉ፥ በሙታን ውስጥ እንዳሉ የተጣልሁ ሆንሁ፤ እነርሱም ከእጅህ ተለዩ።
6 በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ፥ በታችኛው ጕድጓድ አስቀመጥኸኝ።
7 በእኔ ላይ ቍጣህ ጸና፥ መቅሠፍትህን ሁሉ በእኔ ላይ አመጣህ።
8 የሚያውቁኝን ከእኔ አራቅህ፤ በእነርሱ ዘንድ ርኵስ አደረግኸኝ፤ ያዙኝ፥ መውጫም የለኝም።
9 ዓይኖቼም በመከራ ፈዘዙ፤ አቤቱ፥ ሁልጊዜ ወደ አንተ ጮኽሁ፥ እጆቼንም ወደ አንተ ዘረጋሁ፥
10 በውኑ ለሙታን ተኣምራት ታደርጋለህን? የሞቱትስ ተነሥተው ያመሰግኑሃልን?
11 በመቃብርስ ውስጥ ቸርነትህን፥ እውነትህንስ በጥፋት ስፍራ ይናገራሉን?
12 ተአምራትህ በጨለማ፥ ጽድቅህንም በመርሳት ምድር ትታወቃለችን?
13 አቤቱ፥ እኔ ግን ወደ አንተ ጮኽሁ፤ በጥዋት ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትደርሳለች።
14 አቤቱ፥ ነፍሴን ለምን ትጥላለህ? ፊትህንስ ከእኔ ለምን ትሰውራለህ?
15 እኔ ከታናሽነቴ ችግረኛ ለሞትም የቀረብሁ ነኝ፤ ከፍ ከፍ ካልሁ በኋላ ግን ተዋረድሁ ተናቅሁም።
16 መቅሠፍትህ በላዬ አለፈ፥ ግርማህም አስደነገጠኝ።
17 ሁልጊዜ እንደ ውኃ ከበቡኝ፥ በአንድነትም ያዙኝ።
18 ወዳጄንና ባልንጀራዬን ዘመዶቼንም ከመከራ የተነሣ ከእኔ አራቅህ።
የይዝራኤላዊው የኤታን ትምህርት።
1 አቤቱ፥ ምሕረትህን ለዘላለም እዘምራለሁ፥ እውነትህንም በአፌ ለልጅ ልጅ እናገራለሁ።
2 እንዲህ ብለሃልና። ምሕረት ለዘላለም ይመሠረታል፥ እውነትህም በሰማይ ይጸናል።
3 ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ፥ ለባሪያዬም ለዳዊት ማልሁ።
4 ዘርህን ለዘላለም አዘጋጃለሁ፥ ዙፋንህንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለሁ።
5 አቤቱ፥ ሰማያት ተኣምራትህን እውነትህንም ደግሞ በቅዱሳን ማኅበር ያመሰግናሉ።
6 እግዚአብሔርን በሰማይ የሚተካከለው ማን ነው? ከአማልክትስ ልጆች እግዚአብሔርን ማን ይመስለዋል?
7 በቅዱሳን ምክር እግዚአብሔር ክቡር ነው፤ በዙሪያው ባሉት ሁሉ ላይ ታላቅና ግሩም ነው።
8 አቤቱ የሠራዊት አምላክ፥ እንደ አንተ ያለ ማን ነው? አቤቱ፥ አንተ ብርቱ ነህ፥ እውነትህም ይከብብሃል።
9 የባሕርን ኃይል አንተ ትገዛለህ፥ የሞገዱንም መናወጥ አንተ ዝም ታሰኘዋለህ።
10 አንተ ረዓብን እንደ ተገደለ አዋረድኸው፥ በኃይልህም ክንድ ጠላቶችህን በተንሃቸው።
11 ሰማያት የአንተ ናቸው፥ ምድርም የአንተ ናት፤ ዓለምንና ሞላውም አንተ መሠረትህ።
12 ሰሜንና ደቡብን አንተ ፈጠርህ፤ ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል።
13 ክንድህ ከኃይልህ ጋር ነው፤ እጅህ በረታች ቀኝህም ከፍ ከፍ አለች።
14 የዙፋንህ መሠረት ጽድቅና ፍርድ ነው፤ ምሕረትና እውነት በፊትህ ይሄዳሉ።
15 እልልታ የሚያውቅ ሕዝብ ምስጉን ነው፤ አቤቱ፥ በፊትህ ብርሃን ይሄዳሉ።
16 በስምህ ቀኑን ሁሉ ደስ ይላቸዋል፥ በጽድቅህም ከፍ ከፍ ይላሉ፤
17 የኃይላቸው ትምክሕት አንተ ነህና፥ በሞገስህም ቀንዳችን ከፍ ከፍ ይላልና።
18 ረድኤታችን ከእግዚአብሔር ከንጉሣችንም ከእስራኤል ቅዱስ ነውና።
19 በዚያ ጊዜ ለልጆችህ በራእይ ተናገርህ እንዲህም አልህ። ረድኤቴን በኃይል ላይ አኖርሁ፤ ከሕዝቤ የተመረጠውን ከፍ ከፍ አደረግሁ።
20 ባሪያዬን ዳዊትን አገኘሁት፥ ቅዱስ ዘይትም ቀባሁት።
21 እጄም ትረዳዋለች፥ ክንዴም ታጸናዋለች።
22 ጠላት በእርሱ ላይ አይጠቀምም፥ የዓመፃ ልጅም መከራ አይጨምርበትም።
23 ጠላቶቹን ከፊቱ አጠፋለሁ፥ የሚጠሉትንም አዋርዳቸዋለሁ።
24 እውነቴና ምሕረቴም ከእርሱ ጋር ነው፥ በስሜም ቀንዱ ከፍ ከፍ ይላል።
25 እጁን በባሕር ላይ ቀኙንም በወንዞች ላይ አኖራለሁ።
26 እርሱ። አባቴ አንተ ነህ፥ አምላኬ የመድኃኒቴም መጠጊያ ይላል።
27 እኔም ደግሞ በኵሬ አደርገዋለሁ፥ ከምድር ነገሥታትም ከፍ ይላል።
28 ለዘላለምም ምሕረቴን ለእርሱ እጠብቃለሁ፥ ኪዳኔም በእርሱ ዘንድ የታመነ ነው።
29 ዘሩንም ለዓለምና ለዘላለም፥ ዙፋኑንም እንደ ሰማይ ዘመን አደርጋለሁ።
30 ልጆቹ ግን ሕጌን ቢተዉ፥ በፍርዴም ባይሄዱ፤
31 ሥርዓቴንም ቢያረክሱ፥ ትእዛዜንም ባይጠብቁ፤
32 ኃጢአታቸውን በበትር፥ በደላቸውንም በመቅሠፍት እጐበኛታለሁ።
33 ምሕረቴን ግን ከእርሱ አላርቅም፥ በእውነቴም አልበድልም፤
34 ኪዳኔንም አላረክስም፥ ከከንፈሬም የወጣውን አልለውጥም።
35 ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልሁ።
36 ዘሩ ለዘላለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሐይ ይኖራል።
37 ለዘላለም እንደ ጨረቃ ይጸናል፤ ምስክርነቱ በሰማይ የታመን ነው።
38 አንተ ግን ናቅኸው ጣልኸውም፥ የቀባኸውንም ጣልኸው።
39 የባሪያህንም ኪዳን አፈረስህ፥ መቅደሱንም በምድር አረከስህ።
40 ቅጥሩን ሁሉ ጣልህ፥ አምባዎቹንም አጠፋህ።
41 መንገድ አላፊም ሁሉ ተናጠቀው፥ ለጎረቤቶቹም ስድብ ሆነ።
42 የጠላቶቹንም ቀኝ ከፍ ከፍ አደረግህ፥ ጠላቶቹንም ሁሉ ደስ አሰኘህ።
43 የሰይፉንም ረድኤት መለስህ፥ በሰልፍም ውስጥ አልደገፍኸውም።
44 ከንጽሕናውም ሻርኸው፥ ዙፋኑንም በምድር ጣልህ።
45 የዙፋኑንም ዘመን አሳነስህ፥ በእፍረትም ሸፈንኸው።
46 አቤቱ፥ እስከ መቼ ለዘላለም ፊትህን ትመልሳለህ? እስከ መቼስ ቍጣህ እንደ እሳት ይነድዳል?
47 ችሎታዬ ምን እንደ ሆነ አስብ፤ በውኑ የሰውን ልጅ ሁሉ ለከንቱ ፈጠርኸውን?
48 ሕያው ሆኖ የሚኖር፥ ሞትንስ የማያይ ማን ነው? ነፍሱንስ ከሲኦል እጅ የሚያድን ማን ነው?
49 ለዳዊት በእውነት የማልህ፥ አቤቱ፥ የቀድሞ ምሕረትህ ወዴት ነው?
50 አቤቱ፥ የባሪያዎችህን ስድብ፥ በብብቴ ብዙ አሕዛብን የተቀበልሁትን፥
51 አቤቱ፥ ጠላቶችህን የሰደቡትን የቀባኸውን ዘመን የሰደቡትን አስብ።
52 እግዚአብሔር ለዘላለም ይባረክ። ይሁን ይሁን።
የእግዚአብሔር ሰው የሙሴ ጸሎት።
1 አቤቱ፥ አንተ ለትውልድ ሁሉ መጠጊያ ሆንህልን።
2 ተራሮች ሳይወለዱ፥ ምድርም ዓለምም ሳይሠሩ፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ አንተ ነህ።
3 ሰውን ወደ ኅሳር አትመልስም፤ የሰው ልጆች ሆይ፥ ተመለሱ ትላለህ፤
4 ሺህ ዓመት በፊትህ እንዳለፈች እንደ ትናንት ቀን፥ እንደ ሌሊትም ትጋት ነውና።
5 ዘመኖች የተናቁ ይሆናሉ፥ በማለዳም እንደ ሣር ያልፋል።
6 ማልዶ ያብባል ያልፋልም፥ በሠርክም ጠውልጎና ደርቆ ይወድቃል።
7 እኛ በቍጣህ አልቀናልና፥ በመዓትህም ደንግጠናልና።
8 የተሰወረውን ኃጢአታችንን በፊትህ ብርሃን፥ በደላችንንም በፊትህ አስቀመጥህ።
9 ዘመናችን ሁሉ አልፎአልና፥ እኛም በመዓትህ አልቀናልና፤ ዘመኖቻችንም እንደ ሸረሪት ድር ይሆናሉ።
10 የዘመኖቻችንም ዕድሜ ሰባ ዓመት፥ ቢበረታም ሰማንያ ዓመት ነው፤ ቢበዛ ግን ድካምና መከራ ነው፤ ከእኛ ቶሎ ያልፋልና፥ እኛም እንገሠጻለንና።
11 የቍጣህን ጽናት ማን ያውቃል? ከቍጣህ ግርማ የተነሣ አለቁ።
12 በልብ ጥበብን እንድንማር፥ ቀኝህን እንዲህ አስታውቀን።
13 አቤቱ፥ ተመለስ፥ እስከ መቼስ ነው? ስለ ባሪያዎችህም ተምዋገት።
14 በማለዳ ምሕረትህን እንጠግባለን፤ በዘመናችን ሁሉ ደስ ይለናል ሐሤትም እናደርጋለን።
15 መከራ ባሳየኸን ዘመን ፈንታ፥ ክፉም ባየንባቸው ዘመኖች ፋንታ ደስ ይለናል።
16 ባሪያዎችህንና ሥራህን እይ፥ ልጆቻቸውንም ምራ።
17 የአምላካችን የእግዚአብሔር ብርሃን በላያችን ይሁን። የእጆቻችንንም ሥራ በላያችን አቅና።

የዳዊት የምስጋና መዝሙር።
1 በልዑል መጠጊያ የሚኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል።
2 እግዚአብሔርን። አንተ መታመኛዬ ነህ እለዋለሁ፤ አምላኬና መሸሸጊያዬ ነው፥ በእርሱም እታመናለሁ።
3 እርሱ ከአዳኝ ወጥመድ ከሚያስደነግጥም ነገር ያድንሃልና።
4 በላባዎቹ ይጋርድሃል፥ በክንፎቹም በታች ትተማመናለህ፤ እውነት እንደ ጋሻ ይከብብሃል።
5 ከሌሊት ግርማ፥ በቀን ከሚበርር ፍላጻ፥
6 በጨለማ ከሚሄድ ክፉ ነገር፥ ከአደጋና ከቀትር ጋኔን አትፈራም።
7 በአጠገብህ ሺህ በቀኝህም አሥር ሺህ ይወድቃሉ፤ ወደ አንተ ግን አይቀርብም።
8 በዓይኖችህ ብቻ ትመለከታለህ፥ የኃጥኣንንም ብድራት ታያለህ።
9 አቤቱ፥ አንተ ተስፋዬ ነህና፤ ልዑልን መጠጊያህ አደረግህ።
10 ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፥ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ አይገባም።
11 በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤
12 እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል።
13 በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ።
14 በእኔ ተማምኖአልና አስጥለዋለሁ፤ ስሜንም አውቆአልና እጋርደዋለሁ።
15 ይጠራኛል እመልስለትማለሁ፥ በመከራውም ጊዜ ከእርሱ ጋራ እሆናለሁ፤ አድነዋለሁ አከብረውማለሁ።
16 ረጅምን ዕድሜ አጠግበዋለሁ፥ ማዳኔንም አሳየዋለሁ።

በሰንበት ቀን የምስጋና መዝሙር።
1 እግዚአብሔርን ማመስገን መልካም ነው፥ ልዑል ሆይ፥ ለስምህም ዝማሬ ማቅረብ፤
2 በማለዳ ምሕረትን፥ በሌሊትም እውነትህን ማውራት
3 አሥር አውታር ባለው በበገና፥ ከምስጋና ጋርም በመሰንቆ።
4 አቤቱ፥ በሥራህ ደስ አሰኝተኸኛልና፤ በእጅህም ሥራ ደስ ይለኛልና።
5 አቤቱ፥ ሥራህ እጅግ ትልቅ ነው፥ አሳብህም እጅግ ጥልቅ ነው።
6 ሰነፍ ሰው አያውቅም። ልብ የሌለውም ይህን አያስተውለውም።
7 ኃጢአተኞች እንደ ሣር ሲበቅሉ ዓመፃ የሚያደርጉ ሁሉ ሲለመልሙ፥ ለዘላለም ዓለም እንዲጠፋ ነው።
8 አቤቱ፥ አንተ ግን ለዘላለም ልዑል ነህ፤
9 አቤቱ፥ እነሆ፥ ጠላቶችህ ይጠፋሉና፥ ዓመፃንም የሚሠሩ ሁሉ ይበተናሉና።
10 ቀንዴ አንድ ቀንድ እንዳለው ከፍ ከፍ ይላል፤ ሽምግልናዬም በዘይት ይለመልማል።
11 ዓይኔም በጠላቶቼ ላይ አየች፥ ጆሮዬም በእኔ ላይ በቆሙ በክፉዎች ላይ ሰማች።
12 ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል፥ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ያድጋል።
13 በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተተክለዋል፥ በአምላካችንም አደባባይ ውስጥ ይበቅላሉ።
14 ያን ጊዜ በለመለመ ሽምግልና ያፈራሉ ደስተኞችም ሆነው ይኖራሉ።
15 አምላኬ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ ይነግራሉ፥ በእርሱም ዘንድ ዓመፃ የለም።

በሰንበት ቀን የምስጋና መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ነገሠ፥ ክብርንም ለበሰ፤ እግዚአብሔር ኃይልን ለበሰ፥ ታጠቀም፤ ዓለምን እንዳትናወጥ አጸናት።
2 ዙፋንህ ከጥንት ጀምሮ የተዘጋጀ ነው፥ አንተም ከዘላለም ነህ።
3 አቤቱ፥ ወንዞች ከፍ ከፍ አደረጉ፥ ወንዞች ቃሎቻቸውን ከፍ ከፍ አደረጉ።
4 ከብዙ ውኆች ድምፅ ከባሕርም ታላቅ ሞገድ ይልቅ እግዚአብሔር በከፍታው ድንቅ ነው።
5 ምስክርህ እጅግ የታመነ ነው፤ አቤቱ፥ እስከ ረጅም ዘመን ድረስ ለቤትህ ቅድስና ይገባል።
በአራተኛ ሰንበት የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር የበቀል አምላክ ነው። የበቀል አምላክ ተገለጠ።
2 የምድር ፈራጅ ሆይ፥ ከፍ ከፍ በል፤ ለትዕቢተኞች ፍዳቸውን ክፈላቸው።
3 አቤቱ፥ ኃጢአተኞች እስከ መቼ? ኃጢአተኞች እስከ መቼ ይጓደዳሉ?
4 ይከራከራሉ፥ ዓመፃንም ይናገራሉ፤ ዓመፃንም የሚያደርጉ ሁሉ ይናገራሉ።
5 አቤቱ፥ ሕዝብን አዋረዱ፥ ርስትህንም አስቸገሩ።
6 ባልቴቲቱንና ድሀ አደጉን ገደሉ፥ ስደተኛውንም ገደሉ።
7 እግዚአብሔር አያይም፥ የያዕቆብ አምላክ አያስተውልም አሉ።
8 የሕዝብ ደንቆሮች ሆይ፥ አስተውሉ፤ ሰነፎችማ መቼ ይጠበባሉ?
9 ጆሮን የተከለው አይሰማምን? ዓይንን የሠራው አያይምን?
10 አሕዛብንስ የሚገሥጸው፥ ለሰውም እውቀት የሚያስተምረው እርሱ አይዘልፍምን?
11 የሰዎች አሳብ ከንቱ እንደ ሆነ እግዚአብሔር ያውቃል።
12 –
13 ለኃጢአተኛ ጕድጓድ እስኪቈፈር ድረስ ከክፉዎች ዘመናት ይወገድ ዘንድ፥ አቤቱ፥ አንተ የገሠጽኸው ሕግህንም ያስተማርኸው ሰው ምስጉን ነው።
14 እግዚአብሔር ሕዝቡን አይጥልምና፥ ርስቱንም አይተውምና
15 ፍርድ ወደ ጽድቅ እስኪመልስ ድረስ ልበ ቅኖችም ሁሉ ይከተሉአታል።
16 በክፉዎች ላይ ለእኔ የሚቆም ማን ነው? ዓመፃንስ በሚያደርጉ ላይ ለእኔ የሚከራከር ማን ነው?
17 እግዚአብሔር የረዳኝ ባይሆን ነፍሴ ለጥቂት ጊዜ በሲኦል ባደረች ነበር።
18 እግሮቼ ተሰናከሉ ባልሁ ጊዜ፥ አቤቱ፥ ምሕረትህ ረዳኝ።
19 አቤቱ፥ ለልቤ እንደ መከራዋ ብዛት ማጽናናትህ ነፍሴን ደስ አሰኛት።
20 በሕግ ላይ ዓመፅን የሚሠራ የዓመፅ ዙፋን ከአንተ ጋር አንድ ይሆናልን?
21 የጻድቅን ነፍስ ያደቡባታል፥ በንጹሕ ደምም ይፈርዳሉ።
22 እግዚአብሔር መጠጊያ ሆነኝ፥ አምላኬ የተስፋዬም ረዳት ነው።
23 እንደ በደላቸውም እንደ ክፋታቸውም ፍዳቸውን ይከፍላቸዋል፥ አምላካችን እግዚአብሔርም ያጠፋቸዋል።
የዳዊት ምስጋና መዝሙር።
1 ኑ፥በእግዚአብሔር ደስ ይበለን፤ ለአምላክ ለመድኃኒታችን እልል እንበል።
2 በምስጋና ወደ ፊቱ እንድረስ፥ በዝማሬም ለእርሱ እልል እንበል፤
3 እግዚአብሔር ታላቅ አምላክ ነውና፥ በአማልክትም ሁሉ ላይ ታላቅ ንጉሥ ነውና።
4 እግዚአብሔር ሕዝቡን አይጥላቸውም፤ የምድር ዳርቻዎችም በእጁ ውስጥ ናቸው፥ የተራሮች ከፍታዎች የእርሱ ናቸው።
5 ባሕር የእርሱ ናት እርሱም አደረጋት፥ የብስንም እጆቹ ሠሩአት።
6 ኑ፥ እንስገድ ለእርሱም እንገዛ፤ በእርሱ ባደረገን በእግዚአብሔር ፊት እንበርከክ፤
7 እርሱ አምላካችን ነውና፥ እኛ የማሰማርያው ሕዝብ የእጁም በጎች ነንና።
8 በምድረ በዳ እንደ ተፈታተኑት እንዳስቈጡት ጊዜ፥ ዛሬ ድምፁን ብትሰሙ ልባችሁን አታጽኑ።
9 የተፈታተኑኝ አባቶቻችሁ ፈተኑኝ ሥራዬንም አዩ።
10 ያችን ትውልድ አርባ ዓመት ተቈጥቻት ነበር። ሁልጊዜ ልባቸው ይስታል፥ እነርሱም መንገዴን አላወቁም አልሁ።
11 ወደ ዕረፍቴም እንዳይገቡ በቁጣዬ ማልሁ።
ከምርኮ በኋላ ቤት በተሠራ ጊዜ።
1 ለእግዚአብሔር አዲስ ምስጋናን አመስግኑ፤ ምድር ሁሉ፥ እግዚአብሔርን አመስግኑ።
2 እግዚአብሔርን አመስግኑ ስሙንም ባርኩ፥ ዕለት ዕለትም ማዳኑን አውሩ።
3 ክብሩን ለአሕዛብ ተኣምራቱንም ለወገኖች ሁሉ ንገሩ፤
4 እግዚአብሔር ታላቅ ምስጋናውም ብዙ ነውና፥ በአማልክትም ሁሉ ላይ የተፈራ ነውና።
5 የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸውና፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።
6 ምስጋናና ውበት በፊቱ፥ ቅዱስነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው።
7 የአሕዛብ ወገኖች፥ ለእግዚአብሔር አምጡ፥ ክብርና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ፤
8 ለስሙ የሚገባ ክብርን ለእግዚአብሔር አምጡ፤ ቍርባን ያዙ ወደ አደባባዮችም ግቡ።
9 በቅድስናው ስፍራ ለእግዚአብሔር ስገዱ፤ ምድር ሁሉ በፊቱ ትነዋወጥ።
10 በአሕዛብ መካከል። እግዚአብሔር ነገሠ በሉ። እንዳይናወጥም ዓለሙን እርሱ አጸናው፥ አሕዛብንም በቅንነት ይፈርዳል።
11 ሰማያት ደስ ይበላቸው፥ ምድርም ሐሤትን ታድርግ፤ ባሕርና ሞላዋ ይናወጡ፤
12 በረሃ በእርስዋም ያሉ ሁሉ ሐሤትን ያድርጉ፤ የዱር ዛፎች ሁሉ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ፊት ደስ ይላቸዋል፤
13 ይመጣልና፤ በምድር ላይ ሊፈርድ ይመጣልና፤ እርሱም ዓለምን በጽድቅ አሕዛብንም በቅንነት ይፈርዳል።
1 እግዚአብሔር ነገሠ፤ ምድር ሐሤትን ታድርግ፥ ብዙ ደሴቶችም ደስ ይበላቸው።
2 ደመና ጭጋግም በዙሪያው ናቸው፤ ጽድቅና ፍርድ የዙፋኑ መሠረት ናቸው።
3 እሳት በፊቱ ይሄዳል፥ ጠላቶቹንም በዙሪያው ያቃጥላል።
4 መብረቆቹ ለዓለም አበሩ፤ ምድር አየችና ተናወጠች።
5 ተራሮችም ከእግዚአብሔር ፊት፥ ከምድር ሁሉ ጌታ ፊት እንደ ሰም ቀለጡ።
6 ሰማያት የእርሱን ጽድቅ አወሩ፥ አሕዛብም ሁሉ ክብሩን አዩ።
7 ለተቀረጸ ምስል የሚሰግዱ ሁሉ፥ በጣዖቶቻቸውም የሚመኩ ይፈሩ፤ መላእክቱ ሁሉ፥ ስገዱለት።
8 አቤቱ፥ ስለ ፍርድህ ጽዮን ሰምታ ደስ አላት፥ የይሁዳም ሴት ልጆች ደስ አላቸው፤
9 አንተ፥ እግዚአብሔር፥ በምድር ላይ ሁሉ ልዑል ነህና፥ በአማልክትም ሁሉ ላይ እጅግ ከፍ ከፍ ብለሃልና።
10 እግዚአብሔርን የምትወዱ፥ ክፋትን ጥሉ፤ እግዚአብሔር የቅዱሳኑን ነፍሶች ይጠብቃል፥ ከኃጥኣንም እጅ ያድናቸዋል።
11 ብርሃን ለጻድቃን፥ ደስታም ለልበ ቅኖች ወጣ።
12 ጻድቃን፥ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፥ ለቅድስናውም መታሰቢያ አመስግኑ።
የዳዊት መዝሙር።
1 ለእግዚአብሔር አዲስ ምስጋናን አመስግኑ፥ እግዚአብሔር ተኣምራትን አድርጎአልና፤ ቀኙ የተቀደሰም ክንዱ ለእርሱ ማዳን አደረገ።
2 እግዚአብሔር ማዳኑን አስታወቀ፥ በአሕዛብም ፊት ጽድቁን ገለጠ።
3 ለያዕቆብ ምሕረቱን ለእስራኤልም ቤት እውነቱን አሰበ፤ የምድር ዳርቻዎች ሁሉ የአምላካችንን ማዳን አዩ።
4 ምድር ሁሉ ሆይ፥ ለእግዚአብሔር እልል በሉ፤ አመስግኑ፥ ደስ ይበላችሁ፥ ዘምሩም።
5 ለእግዚአብሔር በመሰንቆ፥ በመሰንቆና በዝማሬ ድምፅ ዘምሩ።
6 በዋሽንትና በመለከት ድምፅ በንጉሥ በእግዚአብሔር ፊት እልል በሉ።
7 ባሕርና ሞላዋ፥ ዓለምም በእርስዋም የሚኖሩ ይናወጡ።
8 ወንዞችም በአንድነት በእጅ ያጨብጭቡ፤ ተራሮች ደስ ይበላቸው፥ በምድር ሊፈርድ ይመጣልና።
9 ለዓለምም በጽድቅ ለአሕዛብም በቅንነት ይፈርዳል።
የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ነገሠ፥ አሕዛብ ይደንግጡ፤ በኪሩቤል ላይ ተቀመጠ፥ ምድር ትናወጥ።
2 እግዚአብሔር በጽዮን ታላቅ ነው፤ እርሱም በአሕዛብ ሁሉ ላይ ከፍ ከፍ አለ።
3 ግሩምና ቅዱስ ነውና ሁሉ ታላቅ ስምህን ያመስግኑ።
4 የንጉሥ ክብር ፍርድን ይወድዳል፤ አንተ ቅንነትን አጸናህ፥ ለያዕቆብ ፍርድንና ጽድቅን አንተ አደረግህ።
5 አምላካችንን እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ አድርጉት፥ ቅዱስ ነውና ወደ እግሩ መረገጫ ስገዱ።
6 ሙሴና አሮን በካህናቱ ዘንድ፥ ሳሙኤልም ስሙን በሚጠሩት ዘንድ ናቸው። እግዚአብሔርን ጠሩት፥ እርሱም መለሰላቸው።
7 በደመና ዓምድም ተናገራቸው፤ ምስክሩንና የሰጣቸውን ትእዛዝ ጠበቁ።
8 አቤቱ አምላክችን ሆይ፥ አንተ ሰማሃቸው፤ አቤቱ፥ አንተ ማርሃቸው፥ ሥራቸውን ሁሉ ግን ተበቀልሃቸው።
9 አምላካችንን እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ አድርጉት፥ በቅዱስ ተራራውም ስገዱ፤ አምላካችን እግዚአብሔር ቅዱስ ነውና።
የምስጋና መዝሙር።
1 ምድር ሁሉ፥ ለእግዚአብሔር እልል በሉ፥
2 በደስታም ለእግዚአብሔር ተገዙ፥ በሐሤትም ወደ ፊቱ ግቡ።
3 እግዚአብሔር እርሱ አምላክ እንደ ሆነ እወቁ፤ እርሱ ሠራን እኛም አይደለንም፤ እኛስ ሕዝቡ የማሰማርያውም በጎች ነን።
4 ወደ ደጆቹ በመገዛት፥ ወደ አደባባዮቹም በምስጋና ግቡ፤ አመስግኑት፥ ስሙንም ባርኩ፤
5 እግዚአብሔር ቸር፥ ምሕረቱም ለዘላለም፥ እውነቱም ለልጅ ልጅ ነውና።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ምሕረትንና ፍርድን እቀኝልሃለሁ።
2 እዘምራለሁ፥ ንጹሕ መንገዱንም አስተውላለሁ፤ ወደ እኔ መቼ ትመጣለህ? በቤቴ መካከል በልቤ ቅንነት እሄዳለሁ።
3 በዓይኔ ፊት ክፉን ነገር አላኖርሁም፤ ሕግ ተላላፊዎችን ጠላሁ።
4 ጠማማ ልብም አልተጠጋኝም፤ ክፉ ከእኔ በራቀ ጊዜ አላወቅሁም።
5 ባልንጀራውን በቀስታ የሚያማን እርሱን አሳደድሁ፤ በዓይኑ ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም።
6 ከእኔ ጋር ይኖሩ ዘንድ፤ ዓይኖቼ በምድር ምእመናን ላይ ናቸው፤ በቀና መንገድ የሚሄድ እርሱ ያገለግለኛል።
7 ትዕቢትን የሚያደርግ በቤቴ መካከል አይኖርም፤ ዓመፅን የሚናገር በዓይኔ ፊት አይቀናም።
8 ዓመፃ የሚያደርጉትን ሁሉ ከእግዚአብሔር ከተማ አጠፋቸው ዘንድ፥ የምድርን ኃጢአተኞች ሁሉ በማለዳ እገድላቸዋለሁ።
ባዘነና ልመናውን በእግዚአብሔር ፊት ባፈሰሰ ጊዜ የችግረኛ ጸሎት።
1 አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማኝ፥ ጩኸቴም ወደ አንተ ይድረስ።
2 በመከራዬ ቀን ፊትህን ከኔ አትመልስ፤ ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል፤ በጠራሁህ ቀን ፈጥነህ ስማኝ።
3 ዘመኔ እንደ ጢስ አልቃለችና፥ አጥንቶቼም እንደ መቃጠያ ተቃጥለዋልና።
4 እህል መብላት ተረስቶኛልና ተቀሠፍሁ ልቤም እንደ ሣር ደረቀ።
5 ከጩኸቴ ድምፅ የተነሣ አጥንቶቼ ከሥጋዬ ጋር ተጣበቁ።
6 እንደ ምድረ በዳ እርኩም መሰልሁ፤ በፈረሰ ቤት እንዳለ እንደ ጕጕት ሆንሁ።
7 ተጋሁ፥ በሰገነትም እንደሚኖር ብቸኛ ድንቢጥ ሆንሁ።
8 ጠላቶቼ ሁልጊዜ ይሰድቡኛል፥ የሚያሳድዱኝም ተማማሉብኝ።
9 አመድን እንደ እህል ቅሜአለሁና፥ መጠጤንም ከእንባዬ ጋር ቀላቅያለሁና፥
10 ከቍጣህና ከመዓትህም የተነሣ፤ አንሥተኸኛልና፥ ጥለኸኝማልና።
11 ዘመኖቼ እንደ ጥላ አዘንብለዋል፤ እኔም እንደ ሣር ደርቄአለሁ።
12 አንተ ግን፥ አቤቱ፥ ለዘላለም ትኖራለህ፥ መታሰቢያህም ለልጅ ልጅ ነው።
13 አንተ ተነሥ ጽዮንንም ይቅር በላት፥ የምሕረትዋ ጊዜ ነውና፥ ዘመንዋም ደርሶአልና፤
14 ባሪያዎችህም ድንጋዮችዋን ወድደዋልና፥ ለመሬትዋም አዝነዋልና።
15 አቤቱ፥ አሕዛብ ስምህን፥ ነገሥታትም ሁሉ ክብርህን ይፈራሉ፤
16 እግዚአብሔር ጽዮንን ይሠራታልና፥ በክብሩም ይገለጣልና።
17 ወደ ችግረኞች ጸሎት ተመለከተ፥ ልመናቸውንም አልናቀም።
18 ይህ ለሚመጣ ትውልድ ይጻፍ፥ የሚፈጠርም ሕዝብ ለእግዚአብሔር እልል ይላል፤
19 እግዚአብሔር ከመቅደሱ ከፍታ ሆኖ ተመልክቶአልና፥ ከሰማይ ሆኖ ምድርን አይቶአልና፤
20 የእስረኞችን ጩኸት ይሰማ ዘንድ፥ ሊገድሉ የተፈረደባቸውን ያድን ዘንድ፤
21 የእግዚአብሔርን ስም በጽዮን ምስጋናውንም በኢየሩሳሌም ይናገሩ ዘንድ፤
22 አሕዛብ በአንድነት በተሰበሰቡ ጊዜ መንግሥታትም ለእግዚአብሔር ይገዙ ዘንድ።
23 በኃይሉ ጎዳና መለሰለት። የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ።
24 በዘመኔ እኵሌታ አትውሰደኝ፤ ዓመቶችህ ለልጅ ልጅ ናቸው።
25 አቤቱ፥ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ፥ ሰማያትም የእጅህ ሥራ ናቸው።
26 እነርሱ ይጠፋሉ፥ አንተ ግን ትኖራለህ፤ ሁላቸው እንደ ልብስ ያረጃሉ፥ እንደ መጐናጸፊያም ትለውጣቸዋለህ፥ ይለወጡማል፤
27 አንተ ግን ያው አንተ ነህ፥ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም።
28 የባሪያዎችህም ልጆች ይኖራሉ፥ ዘራቸውም ለዘላለም ትጸናለች።
የዳዊት መዝሙር።
1 ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ፥ አጥንቶቼም ሁሉ፥ የተቀደሰ ስሙን።
2 ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ፥ ምስጋናውንም ሁሉ አትርሺ፤
3 ኃጢአትሽን ሁሉ ይቅር የሚል፥ ደዌሽንም ሁሉ የሚፈውስ፥
4 ሕይወትሽን ከጥፋት የሚያድናት፥ በምሕረቱና በቸርነቱ የሚከልልሽ፥
5 ምኞትሽን ከበረከቱ የሚያጠግባት፥ ጕልማስነትሽን እንደ ንስር ያድሳል።
6 እግዚአብሔር ይቅርታ አድራጊ ነው፤ ለተበደሉ ሁሉ ይፈርዳል።
7 ለሙሴ መንገዱን አስታወቀ፥ ለእስራኤል ልጆችም አደራረጉን።
8 እግዚአብሔር መሓሪና ይቅር ባይ ነው፥ ከቍጣ የራቀ ምሕረቱም የበዛ።
9 ሁልጊዜም አይቀሥፍም፥ ለዘላለምም አይቈጣም።
10 እንደ ኃጢአታችን አላደረገብንም፥ እንደ በደላችንም አልከፈለንም።
11 ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፥ እንዲሁ እግዚአብሔር ምሕረቱን በሚፈሩት ላይ አጠነከረ።
12 ምሥራቅ ከምዕራብ እንደሚርቅ፥ እንዲሁ ኃጢአታችንን ከእኛ አራቀ።
13 አባት ለልጆቹ እንደሚራራ እንዲሁ እግዚአብሔር ለሚፈሩት ይራራል፤
14 ፍጥረታችንን እርሱ ያውቃልና፤ አቤቱ፥ እኛ አፈር እንደ ሆንን አስብ።
15 ሰውስ ዘመኑ እንደ ሣር ነው፤ እንደ ዱር አበባ እንዲሁ ያብባል፤
16 ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ያልፋልና፥ ስፍራውንም ደግሞ አያውቀውምና።
17 የእግዚአብሔር ምሕረት ግን ከዘላለም እስከ ዘላለም በሚፈሩት ላይ፥ ጽድቁም በልጅ ልጆች ላይ ነው፤
18 ቃል ኪዳኑን በሚጠብቁ፥ ትእዛዙንም ያደርጉአት ዘንድ በሚያስቡ ላይ ነው።
19 እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አዘጋጀ፥ መንግሥቱም ሁሉን ትገዛለች።
20 ቃሉን የምትፈጽሙ፥ ብርቱዎችና ኃያላን፥ የቃሉንም ድምፅ የምትሰሙ መላእክቱ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ።
21 ሠራዊቱ ሁሉ፥ ፈቃዱን የምታደርጉ አገልጋዮቹ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ።
22 ፍጥረቶቹ ሁሉ በግዛቱ ስፍራ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ።

የዳዊት መዝሙር።
1 ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ፤ አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ አንተ እጅግ ታላቅ ነህ፤ ክብርንና ግርማን ለበስህ።
2 ብርሃንን እንደ ልብስ ለበስህ፤ ሰማይንም እንደ መጋረጃ ዘረጋህ፤
3 እልፍኙን በውኃ የሚሠራ፥ ሰረገላውን ደመና የሚያደርግ፥ በነፋስ ክንፍም የሚሄድ፥
4 መላእክቱን መንፈስ የሚያደርግ፥ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል።
5 ለዘላለም እንዳትናወጥ ምድርን በመሠረትዋ ላይ መሠረታት።
6 በጥልቅ እንደ ልብስ ከደንሃት፥ በተራሮችም ላይ ውኆች ይቆማሉ።
7 ከዘለፋህም ይሸሻሉ፥ ከነጐድጓድህም ድምፅ ይደነግጣሉ፤
8 ወደ ተራሮች ይወጣሉ፥ ወደ ቈላዎች ወዳዘጋጀህላቸው ስፍራ ይወርዳሉ፤
9 እንዳያልፉትም ድንበር አደረግህላቸው ምድርን ይከድኑ ዘንድ እንዳይመለሱ።
10 ምንጮችን ወደ ቈላዎች ይልካል፤ በተራሮች መካከል ውኆች ያልፋሉ፤
11 የዱር አራዊትን ሁሉ ያጠጣሉ፥ የበረሃ አህያዎችም ጥማታቸውን ይረካሉ።
12 የሰማይም ወፎች በእነርሱ ዘንድ ያድራሉ፥ በድንጋዩ ስንጥቅ መካከልም ይጮኻሉ።
13 ተራሮችን ከላይ የሚያጠጣቸው፤ ከሥራህ ፍሬ ምድር ትጠግባለች።
14 እንጀራን ከምድር ያወጣ ዘንድ ለምለሙን ለሰው ልጆች ጥቅም፥ ሣርንም ለእንስሳ ያበቅላል።
15 ወይን የሰውን ልብ ደስ ያሰኛል፥ ዘይትም ፊትን ያበራል፥ እህልም የሰውን ጕልበት ያጠነክራል።
16 የእግዚአብሔር ዛፎች እርሱም የተከላቸው የሊባኖስ ዝግባዎች ይጠግባሉ።
17 በዚያም ወፎች ይዋለዳሉ፥ የሽመላ ቤትም የእነርሱ ጎረቤት ነው።
18 ረጃጅም ተራራዎች ለዋላዎች፥ ድንጋዮችም ለእሽኮኮች መሸሻ ናቸው።
19 ጨረቃን ለጊዜዎች አደረገ፤ ፀሐይም መግቢያውን ያውቃል።
20 ጨለማ ታደርጋለህ ሌሊትም ይሆናል፤ በእርሱም የዱር አራዊት ሁሉ ይወጡበታል።
21 የአንበሳ ግልገሎች ለመንጠቅ ይጮኻሉ፥ ከእግዚአብሔርም ምግባቸውን ይሻሉ።
22 ፀሐይ ስትወጣ ይሰበሰባሉ በየዋሻቸውም ይተኛሉ።
23 ሰው ወደ ተግባሩ፥ እስኪመሽም ድረስ ወደ ሥራው ይወጣል።
24 አቤቱ፥ ሥራህ እጅግ ብዙ ነው፤ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፥ ምድርም ከፍጥረትህ ተሞላች።
25 ይህች ባሕር ታላቅና ሰፊ ናት፤ በዚያ ስፍራ ቍጥር የሌለው ተንቀሳቃሽ፥ ታላላቆችና ታናናሾች እንስሶች አሉ።
26 በዚያ ጊዜ መርከቦች ይሄዳሉ፥ በዚያም ላይ የፈጠርኸው ዘንዶ ይጫወትበታል።
27 ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸው ዘንድ እነዚህ ሁሉ አንተን ተስፋ ያደርጋሉ።
28 በሰጠሃቸውም ጊዜ ይሰበስባሉ፤ እጅህን ትከፍታለህ፥ ከመልካም ነገርም ይጠግባሉ።
29 ፊትህን ስትሰውር ይደነግጣሉ፤ ነፍሳቸውን ታወጣለህ ይሞታሉም፥ ወደ አፈራቸውም ይመለሳሉ።
30 መንፈስህን ትልካለህ ይፈጠራሉም፥ የምድርንም ፊት ታድሳለህ።
31 የእግዚአብሔር ክብር ለዘላለም ይሁን፤ እግዚአብሔር በሥራው ደስ ይለዋል።
32 ምድርን ያያል እንድትንቀጠቀጥም ያደርጋል፤ ተራሮችን ይዳስሳል ይጤሳሉም።
33 በሕይወቴ ሳለሁ ለእግዚአብሔር እቀኛለሁ፥ ለአምላኬም በምኖርበት ዘመን ሁሉ እዘምራለሁ።
34 ቃሌ ለእርሱ ይጣፍጠው፥ እኔም በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል።
35 ኅጥኣን ከምድር ይጥፉ፤ ዓመፀኞች እንግዲህ አይገኙ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ። ሃሌ ሉያ።

ሃሌ ሉያ።
1 እግዚአብሔርን አመስግኑ ስሙንም ጥሩ፥ ለአሕዛብም ሥራውን አውሩ።
2 ተቀኙለት፥ ዘምሩለት፥ ተአምራቱንም ሁሉ ተናገሩ።
3 በቅዱስ ስሙ ተጓደዱ፤ እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ ደስ ይበለው።
4 እግዚአብሔርን ፈልጉት ትጸናላችሁም፤ ሁልጊዜ ፊቱን ፈልጉ።
5
6 ባሪያዎቹ የአብርሃም ዘር፥ ለእርሱም የተመረጣችሁ የያዕቆብ ልጆች ሆይ፥ የሠራትን ድንቅ አስቡ፥ ተአምራቱን የአፉንም ፍርድ።
7 እርሱ እግዚአብሔር አምላካችን ነው፤ ፍርዱ በምድር ሁሉ ነው።
8 ቃል ኪዳኑን ለዘላለም፥ እስከ ሺህ ትውልድ ያዘዘውን ቃሉን አሰበ፥
9 ለአብርሃም ያደረገውን፥ ለይስሐቅም የማለውን፤
10 ለያዕቆብ ሥርዓት እንዲሆን ለእስራኤልም የዘላለም ኪዳን እንዲሆን አጸና።
11 እንዲህም አለ። ለአንተ የከነዓንን ምድር የርስታችሁን ገመድ እሰጣለሁ፤
12 ይህም የሆነው እነርሱ በቍጥር ጥቂቶች ሰዎች፥ እጅግ ጥቂቶችና ስደተኞች ሲሆኑ ነው።
13 ከሕዝብ ወደ ሕዝብ፥ ከመንግሥታትም ወደ ሌላ ሕዝብ አለፉ።
14 –
15 የቀባኋቸውን አትዳስሱ፥ በነቢያቴም ክፉ አታድርጉ ብሎ፥ ሰው ግፍ ያደርግባቸው ዘንድ አልፈቀደም፥ ስለ እነርሱም ነገሥታትን ገሠጸ።
16 በምድር ላይ ራብን ጠራ፥ የእህልን ኃይል ሁሉ ሰበረ።
17 በፊታቸው ሰውን ላከ፤ ዮሴፍ ለባርነት ተሸጠ።
18 እግሮቹም በእግር ብረት ደከሙ፥ እርሱም በብረት ውስጥ ገባ።
19 ቃሉ እስኪመጣለት ድረስ፥ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው።
20 ንጉሥ ላከ ፈታውም፥ የአሕዛብም አለቃ አስፈታው።
21 የቤቱ ጌታ፥ የጥሪቱ ሁሉ ገዢ አደረገው፥
22 አለቆቹን እንደ ፈቃዱ ይገሥጽ ዘንድ፥ ሽማግሌዎቹንም ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ።
23 እስራኤልም ወደ ግብጽ ገባ፥ ያዕቆብም በካም አገር ተቀመጠ።
24 ሕዝቡንም እጅግ አበዛ፥ ከጠላቶቻቸውም ይልቅ አበረታቸው።
25 ሕዝቡን ይጠሉ ዘንድ በባሪያዎቹም ላይ ይተነኰሉ ዘንድ ልባቸውን ለወጠ።
26 ባሪያውን ሙሴን የመረጠውንም አሮንን ላከ።
27 የተኣምራቱን ነገር በላያቸው ድንቁንም በካም አገር አደረገ።
28 ጨለማን ላከ ጨለመባቸውም፤ በቃሉም ዐመፁ።
29 ውኃቸውን ወደ ደም ለወጠ፥ ዓሦቻቸውንም ገደለ።
30 ምድራቸው የንጉሦቻቸውም ቤቶች በጓጕንቸር ሞሉ።
31 ተናገረ፥ የውሻ ዝንብ ትንኝም በዳርቻቸው መጡ።
32 ዝናባቸውን በረዶ አደረገው፥ እሳትም በምድራቸው ተቃጠለች።
33 ወይናቸውንና በለሳቸውን መታ፥ የአገራቸውንም ዛፍ ሁሉ ሰበረ።
34 ተናገረ፥ አንበጣም ስፍር ቍጥር የሌለውም ኩብኩባ መጣ፥
35 የአገራቸውንም ለምለም ሁሉ በላ፥ የምድራቸውንም ፍሬ በላ።
36 የአገራቸውንም በኵር ሁሉ፥ የጕልበታቸውን መጀመሪያ ሁሉ መታ።
37 ከወርቅና ከብርም ጋር አወጣቸው፥ በወገናቸውም ውስጥ ደዌ አልነበረም።
38 ፈርተዋቸው ነበርና ግብጽ በመውጣታቸው ደስ አላት።
39 ደመናን ለመሸፈኛ ዘረጋባቸው፥ እሳትንም በሌሊት ያበራላቸው ዘንድ ዘረጋ።
40 ለመኑ፥ ድርጭትንም አመጣላቸው፥ የሰማይንም እንጀራ አጠገባቸው።
41 ዓለቱን ሰነጠቀ፥ ውኃውም ፈሰሰ፤ ወንዞች በበረሃ ሄዱ፤
42 ለባሪያው ለአብርሃም የነገረውን ቅዱስ ቃሉን አስቦአልና።
43 ሕዝቡንም በደስታ የተመረጡትንም በእልልታ አወጣ።
44 የአሕዛብንም አገሮች ሰጣቸው፥ የወገኖችንም ድካም ወረሱ፥
45 ሕጉን ይጠብቁ ዘንድ፥ ሥርዓቱንም ይፈልጉ ዘንድ። ሃሌ ሉያ

ምዕራፍ 106
1 ሃሌ ሉያ፤ ቸር ነውና፥ ምህረቱም ለዘላለም ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ።
2 የእግዚአብሔርን ኃይል ሥራ ማን ይናገራል? ምስጋናውንስ ሁሉ ማን ያሰማል?
3 ፍርድን የሚጠብቁ፥ ጽድቅንም ሁልጊዜ የሚያደርጉ ምስጉኖች ናቸው።
4 አቤቱ፥ በሕዝብህ ሞገስ አስበን፥ በመድኃኒትህም ጐብኘን፤
5 የመረጥሃቸውን በጎነት እናይ ዘንድ፥ በሕዝብህም ደስታ ደስ ይለን ዘንድ፥ ከርስትህም ጋር እንጓደድ ዘንድ።
6 ከአባቶቻችን ጋር ኃጢአትን ሠራን፥ ዐመፅንም፥ በደልንም።
7 አባቶቻችን በግብጽ ሳሉ ተኣምራትህን አላስተዋሉም፥ የምሕረትህንም ብዛት አላሰቡም፤ በኤርትራ ባሕር ባለፉ ጊዜ ዐመፁብህ።
8 ኃይሉን ግን ለማስታወቅ። ስለ ስሙ አዳናቸው።
9 የኤርትራንም ባሕር ገሠጸ እርሱም ደረቀ፤ እንደ ምድረ በዳ በጥልቅ መራቸው።
10 ከሚጠሉአቸውም እጅ አዳናቸው፥ ከጠላትም እጅ ተቤዣቸው።
11 ያሳደዱአቸውንም ውኃ ደፈናቸው፥ ከእነርሱም አንድ አልቀረም።
12 በዚያን ጊዜ በቃሉ አመኑ፥ ምስጋናውንም ዘመሩ።
13 ፈጥነውም ሥራውን ረሱ፥ በምክሩም አልታገሡም።
14 በምድረ በዳም ምኞትን ተመኙ፥ በበረሃም እግዚአብሔርን ተፈታተኑት።
15 የለመኑትንም ሰጣቸው፤ ለነፍሳቸው ግን ክሳትን ላከ።
16 ሙሴንም እግዚአብሔር የቀደሰውንም አሮንን በሰፈር ተመቀኙአቸው።
17 ምድርም ተከፈተች ዳታንንም ዋጠችው፥ የአቤሮንንም ወገን ደፈነች፤
18 በማኅበራቸውም እሳት ነደደች፥ ነበልባልም ኅጥኣንን አቃጠላቸው።
19 በኮሬብም ጥጃን ሠሩ፥ ቀልጦ ለተሠራ ምስልም ሰገዱ።
20 ሣርም በሚበላ በበሬ ምሳሌ ክብራቸውን ለወጡ።
21 –
22 ታላቅ ነገርንም በግብጽ፥ ድንቅንም በካራን ምድር፥ ግሩም ነገርንም በኤርትራ ባሕር ያደረገውን ያዳናቸውንም እግዚአብሔርን ረሱ።
23 እንዳያጠፋቸው ቍጣውን ይመልስ ዘንድ የተመረጠው ሙሴ በመቅሠፍት ጊዜ በፊቱ ባይቆም ኖሮ፥ ያጠፋቸው ዘንድ ተናገረ።
24 የተወደደችውን ምድር ናቁ፥ በቃሉም አልታመኑም፥
25 በድንኳኖቻቸውም ውስጥ አንጐራጐሩ፤ የእግዚአብሔርን ቃል አልሰሙም።
26 –
27 በምድረ በዳም ይጥላቸው ዘንድ፥ ዘራቸውንም በአሕዛብ መካከል ይጥል ዘንድ፥ በየአገሩም ይበትናቸው ዘንድ፥ እጁን አነሣባቸው።
28 በብዔል ፌጎርም ተባበሩበት፥ የሙታንንም መሥዋዕት በሉ።
29 በሥራቸውም አስመረሩት፥ ቸነፈርም በላያቸው በዛ።
30 ፊንሐስም ተነሥቶ ፈረደባቸው፥ ቸነፈሩም ተወ፤
31 ያም እስከ ዘላለም ለልጅ ልጅ ጽድቅ ሆኖ ተቈጠረለት።
32 –
33 በክርክር ውኃ ዘንድም አስቈጡት፥ መንፈሱን አስመርረዋታልና፤ ስለ እነርሱም ሙሴ ተበሳጨ፤ በከንፈሮቹም በስንፍና ተናገረ።
34 እግዚአብሔርም እንዳላቸው አሕዛብን አላጠፉም፤
35 ከአሕዛብም ጋር ተደባለቁ፥ ሥራቸውንም ተማሩ።
36 ለጣዖቶቻቸውም ተገዙ፥ ወጥመድም ሆኑባቸው።
37 ወንዶች ልጆቻቸውንና ሴቶች ልጆቻቸውን ለአጋንንት ሠው፤
38 የወንዶች ልጆቻቸውንና የሴቶች ልጆቻቸን ደም፥ ለከነዓን ጣዖቶች የሠውአቸውን ንጹሕ ደም አፈሰሱ፥ ምድርም በደም ረከሰች።
39 በሥራቸው ረከሱ፥ በማድረጋቸውም አመነዘሩ።
40 የእግዚአብሔርም ቍጣ በሕዝቡ ላይ ነደደ፥ ርስቱንም ተጸየፈ።
41 ወደ አሕዛብም እጅ አሳለፋቸው፥ የሚጠሉአቸውም ገዙአቸው።
42 ጠላቶቻቸውም ግፍ አደረጉባቸው፥ ከእጃቸውም በታች ተዋረዱ።
43 ብዙ ጊዜ አዳናቸው፤ ነገር ግን በምክራቸው አስመረሩት፥ በኃጢአታቸውም ተዋረዱ።
44 እርሱ ግን ጩኸታቸውን በሰማ ጊዜ ጭንቃቸውን ተመለከተ፤
45 ለእነርሱም ኪዳኑን አሰበ፥ እንደ ምሕረቱም ብዛት ተጸጸተ።
46 በማረኩአቸውም ሁሉ ፊት ሞገስን ሰጣቸው።
47 አምላካችን እግዚአብሔር ሆይ፥ አድነን፤ ቅዱስ ስምህን እናመሰግን ዘንድ፥ በምስጋናህም እንመካ ዘንድ፥ ከአሕዛብ መካከል ሰብስበን።
48 ከዘላለም እስከ ዘላለም የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይባረክ ሕዝብም ሁሉ አሜን ይበል። ሃሌ ሉያ።

ሃሌ ሉያ።
1 ቸር ነውና፥ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ፤
2 እግዚአብሔር ያዳናቸው፥ ከጠላቶች እጅ ያዳናቸው ይናገሩ።
3 ከምሥራቅና ከምዕራብ፥ ከሰሜንና ከባሕር፥ ከየአገሩ ሰበሰባቸው።
4 ውኃ በሌለበት ምድረ በዳ ተቅበዘበዙ፤ የሚኖሩበትንም ከተማ መንገድ አላገኙም።
5 ተራቡ ተጠሙም፥ ነፍሳቸውም በውስጣቸው አለቀች።
6 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፥ ከመከራቸውም አዳናቸው፤
7 ወደሚኖሩበት ከተማ ይሄዱ ዘንድ የቀና መንገድን መራቸው።
8 ለሰው ልጆች ስላደረገው ተኣምራት ስለ ምሕረቱም እግዚአብሔርን ያመስግኑ፤
9 የተራበችን ነፍስ አጥግቦአልና፥ የተራቈተችንም ነፍስ በበረከት ሞልቶአልና።
10 በጨለማ በሞትም ጥላ የተቀመጡ፥ በችግር በብረትም የታሰሩ፤
11 የእግዚአብሔርን ቃል ስለ ዐመፁ፥ የልዑልንም ምክር ስለ ናቁ፥
12 ልባቸው በድካም ተዋረደ፤ ታመሙ የሚረዳቸውም አጡ።
13 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፥ በመከራቸውም አዳናቸው።
14 ከጨለማና ከሞት ጥላ አወጣቸው፥ እስራታቸውንም ሰበረ።
15 ለሰው ልጆች ስላደረገው ተኣምራት ስለ ምሕረቱም እግዚአብሔርን ያመስግኑ፤
16 የናሱን ደዶች ሰብሮአልና፥ የብረቱንም መወርወሪያ ቈርጦአልና።
17 ስለ ዓመፃቸው ሰነፉ፥ ስለ ኃጢአታቸውም ተቸገሩ።
18 ሰውነታቸው መብልን ሁሉ ተጸየፈች፥ ወደ ሞትም ደጆች ቀረቡ።
19 በተጨነቁ ጊዜም ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፥ ከመከራቸውም አዳናቸው።
20 ቃሉን ላከ ፈወሳቸውም፥ ከጥፋታቸውም አዳናቸው።
21 ለሰው ልጆች ስላደረገው ተኣምራት ስለ ምሕረቱም እግዚአብሔርን ያመሰግኑ፤
22 የምስጋና መሥዋዕትንም ይሠውለት፥ በእልልታም ሥራውን ይንገሩ።
23 በመርከቦች ወደ ባሕር የሚወርዱ፥ በታላቅ ውኃ ሥራቸውን የሚሠሩ፥
24 እነርሱ የእግዚአብሔርን ሥራ፥ በጥልቅም ያለችውን ድንቁን አዩ።
25 ተናገረ፥ ዐውሎ ነፋስም ተነሣ፥ ሞገድም ከፍ ከፍ አለ።
26 ወደ ሰማይ ይወጣሉ ወደ ጥልቅም ይወርዳሉ፤ ነፍሳቸውም በመከራ ቀለጠች።
27 ደነገጡ እንደ ስካርም ተንገደገዱ፥ ጥበባቸውም ሁሉ ተዋጠች።
28 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፥ ከመከራቸውም አዳናቸው።
29 ዐውሎንም ጸጥ አደረገ፥ ሞገዱም ዝም አለ።
30 ዝም ብሎአልና ደስ አላቸው፤ ወደ ፈለጉትም ወደብ መራቸው።
31 ለሰው ልጆች ስላደረገው ተአምራት ስለ ምሕረቱም እግዚአብሔርን ያመስግኑ።
32 በአሕዛብ ጉባኤ ከፍ ከፍ ያድርጉት፥ በሽማግሌዎችም ሸንጎ ያመስግኑት።
33 ወንዞችን ምድረ በዳ፥ የውኃውንም ምንጮች ደረቅ አደረጋቸው፤
34 ከተቀመጡባት ክፋት የተነሣ ፍሬያማዋን ምድር ጨው አደረጋት።
35 ምድረ በዳን ለውኃ መቆሚያ፥ ደረቁንም ምድር የውኃ ምንጮች አደረገ።
36 በዚያም ራብተኞችን አስቀመጠ፥ የሚኖርባትንም ከተማ ሠሩ።
37 እርሻዎችንም ዘሩ ወይኖችንም ተከሉ፥ የእህልንም ሰብል አደረጉ።
38 ባረካቸውም እጅግም በዙ፤ እንስሶቻቸውንም አላሳነሰባቸውም።
39 እነርሱ በችግር በክፋት በጭንቀት ተዋረዱ እያነሱም ሄዱ፤
40 በአለቶችም ላይ ኅሣርን፥ አፈሰሰ፥ መንገድም በሌለበት በምድረ በዳ አሳታቸው።
41 ችግረኛንም ከችግሩ ረዳው፤ እንደ በጎች መንጋ ወገን አደረገው።
42 ቅኖች ያያሉ፥ ደስም ይላቸዋል፤ ኃጢአትም ሁሉ አፍዋን ትዘጋለች።
43 ጥበበኛ የሆነና ይህን የሚጠብቅ ማን ነው? እርሱ የእግዚአብሔርን ምሕረት ያስተውላል።
የዳዊት የምስጋና መዝሙር።
1 ልቤ ጽኑ ነው፥ አቤቱ፥ ልቤ ጽኑ ነው፤ እቀኛለሁ በክብሬም እዘምራለሁ።
2 በገና ሆይ፥ ተነሥ፥ መሰንቆም፤ እኔም ማልጄ እነሣለሁ።
3 አቤቱ፥ በአሕዛብ መካከል አመሰግንሃለሁ፥ በወገኖችም መካከል እዘምርልሃለሁ፤
4 ምሕረትህ በሰማይ ላይ ታላቅ ናትና፥ እውነትህም እስከ ደመናት ድረስ ነውና።
5 አቤቱ፥ በሰማያት ላይ ከፍ ከፍ በል፥ ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትሁን።
6 ወዳጆችህ ይድኑ ዘንድ፤ በቀኝህ አድን አድምጠኝም።
7 እግዚአብሔር በቅድስናው ተናገረ። ደስ ይለኛል፥ ሴኬምንም እካፈላለሁ፥ የሱኮትንም ሸለቆ እሰፍራለሁ።
8 ገለዓድ የእኔ ነው ምናሴም የእኔ ነው፤ ኤፍሬም የራሴ መጠጊያ ነው። ይሁዳ ንጉሤ ነው።
9 ሞዓብ መታጠቢያዬ ነው፥ በኤዶምያስ ላይም ጫማዬን እዘረጋለሁ፤ ፍልስጥኤም ይገዙልኛል።
10 ወደ ጽኑ ከተማ ማን ይወስደኛል? ማንስ እስከ ኤዶምያስ ይመራኛል?
11 አቤቱ፥ የጣልኸኝ አንተ አይደለህምን? አምላክ ሆይ፥ ከሠራዊታችን ጋር አትወጣም።
12 በመከራችን ረድኤትን ስጠን፤ የሰውም ማዳን ከንቱ ነው።
13 በእግዚአብሔር ኃይልን እናደርጋለን፤ እርሱም የሚያስጨንቁንን ያዋርዳቸዋል።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አምላክ ሆይ፥ ምሥጋናዬን ዝም አትበል፥
2 የኃጢአተኛ አፍና የተንኰለኛ አፍ በላዬ ተላቅቀውብኛልና፤ በሽንገላ አንደበትም በላዬ ተናገሩ፤
3 በጥል ቃል ከበቡኝ፥ በከንቱም ተሰለፉብኝ።
4 በወደድኋቸው ፋንታ አጣሉኝ፥ እኔ ግን እጸልያለሁ።
5 በመልካም ፋንታ ክፉን በወደድኋቸውም ፋንታ ጠላትነትን መለሱልኝ።
6 በላዩ ኃጢአተኛን ሹም፤ ሰይጣንም በቀኙ ይቁም።
7 በተምዋገተም ጊዜ ተረትቶ ይውጣ፤ ጸሎቱም ኃጢአት ትሁንበት።
8 ዘመኖቹም ጥቂት ይሁኑ፤ ሹመቱንም ሌላ ይውሰድ።
9 ልጆቹም ድሀ አደግ ይሁኑ፥ ሚስቱም መበለት ትሁን።
10 ልጆቹም ተናውጠው ይቅበዝበዙ ይለምኑም፥ ከስፍራቸውም ይባረሩ።
11 ባለዕዳም ያለውን ሁሉ ይበርብረው፥ እንግዶችም ድካሙን ሁሉ ይበዝብዙት።
12 የሚያግዘውንም አያግኝ። ለድሀ አደግ ልጆቹም የሚራራ አይኑር።
13 ልጆቹ ይጥፉ፤ በአንድ ትውልድ ስሙ ይደምሰስ።
14 የአባቶቹ ኃጢአት በእግዚአብሔር ፊት ትታሰብ፤ የእናቱም ኃጢአት አትደምሰስ።
15 በእግዚአብሔር ፊት ሁልጊዜ ይኑሩ፤ መታሰቢያቸው ከምድር ይጥፋ።
16 ምሕረትን ያደርግ ዘንድ አላሰበምና ችግረኛንና ምስኪንን ልቡ የተሰበረውንም ሰው ይገድል ዘንድ አሳደደ።
17 መርገምን ወደደ ወደ እርሱም መጣች፤ በረከትንም አልመረጠም ከእርሱም ራቀች።
18 መርገምን እንደ ልብስ ለበሳት፥ እንደ ውኃም ወደ አንጀቱ፥ እንደ ቅባትም ወደ አጥንቱ ገባች።
19 እንደሚለብሰው ልብስ። ሁልጊዜም እንደሚታጠቀው ትጥቅ ይሁነው።
20 ይህ ሥራ ከእግዚአብሔር ዘንድ በሚያጣሉኝ በነፍሴም ላይ ክፉን በሚናገሩ ነው።
21 አንተ ግን አቤቱ ጌታዬ፥ ስለ ስምህ ምሕረትህን በእኔ ላይ አድርግ፤ ምሕረትህ መልካም ናትና አድነኝ።
22 እኔ ችግረኛ ምስኪንም ነኝና፥ ልቤም በውስጤ ደነገጠብኝ።
23 እንዳለፈ ጥላ አለቅሁ፥ እንደ አንበጣም እረገፍሁ።
24 ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅቤ በማጣት ከሳ።
25 እኔም በእነርሱ ዘንድ ለነውር ሆንሁ፤ ባዩኝ ጊዜ ራሳቸውን ነቀነቁ።
26 አቤቱ አምላኬ፥ እርዳኝ፥ እንደ ምሕረትህም አድነኝ።
27 አቤቱ፥ እጅህ ይህች እንደ ሆነች፥ አንተም ይህችን እንዳደረግህ ይወቁ።
28 እነርሱ ይራገማሉ አንተ ግን ባርክ፤ በእኔ ላይ የሚነሡ ይፈሩ፥ ባሪያህ ግን ደስ ይበለው።
29 የሚያጣሉኝ እፍረትን ይልበሱ፤ እፍረታቸውን እንደ መጐናጸፊያ ይልበሱአት።
30 እግዚአብሔርን በአፌ እጅግ አመሰግነዋለሁ። በብዙዎችም መካከል አከብረዋለሁ፤
31 ነፍሱን ከሚያሳድዱአት ያድን ዘንድ በድሀ ቀኝ ቆሞአልና።

የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ጌታዬን። ጠላቶችህን ለእግርህ መቀመጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው።
2 እግዚአብሔር የኃይልን በትር ከጽዮን ይልክልሃል፤ በጠላቶችህም መካከል ግዛ።
3 ከአንተ ጋር ቀድሞ በኃይልህ ቀን፥ በቅዱሳን ብርሃን፥ ከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ከሆድ ወለድሁህ።
4 እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዓት አንተ ለዘላለም ካህን ነህ ብሎ፥ እግዚአብሔር ማለ አይጸጸትም።
5 እግዚአብሔር በቀኝህ ነገሥታትን በቍጣው ቀን ይቀጠቅጣቸዋል።
6 በአሕዛብ መካከል ይፈርዳል፥ ሬሳዎችንም ያበዛል፤ በሰፊ ምድር ላይ ራሶችን ይቀጠቅጣል።
7 በመንገድ ከፈሳሽ ውኃ ይጠጣል፤ ስለዚህ ራስ ከፍ ከፍ ይላል።
1 ሃሌ ሉያ። አቤቱ፥ በቅኖች ሸንጎ በጉባኤም በፍጹም ልቤ አመሰግንሃለሁ።
2 የእግዚአብሔር ሥራ ታላቅ ናት፥ ደስ በሚሰኙባት ሁሉ ዘንድ የተፈለገች ናት።
3 ሥራው ምስጋናና ግርማ ነው፤ ጽድቁም ለዘላለም ይኖራል።
4 ለተአምራቱ መታሰቢያን አደረገ፤ እግዚአብሔር መሓሪና ይቅር ባይ ነው።
5 ለሚፈሩት ምግብን ሰጣቸው፤ ኪዳኑንም ለዘላለም ያስባል።
6 የአሕዛብን ርስት ይሰጣቸው ዘንድ ለሕዝቡ የሥራውን ብርታት አሳየ።
7 የእጆቹ ሥራ እውነትና ፍርድ ነው፤ ትእዛዙም ሁሉ የታመነ ነው፥
8 ለዘላለምም የጸና ነው፥ በእውነትና በቅንም የተሠራ ነው።
9 መድኃኒትንም ለሕዝቡ ሰደደ፥ ኪዳኑንም ለዘላለም አዘዘ፤ ስሙ የተቀደሰና የተፈራ ነው።
10 የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፥ ለሚያደርጓትም ሁሉ ደኅና ማስተዋል አላቸው፤ ምስጋናውም ለዘላለም ይኖራል።
1 ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን የሚፈራ፥ ትእዛዙንም እጅግ የሚወድድ ሰው ምስጉን ነው።
2 ዘሩ በምድር ላይ ኃያል ይሆናል፤ የቅኖች ትውልድ ትባረካለች።
3 ክብርና ባለጠግነት በቤቱ ነው፥ ጽድቁም ለዘላለም ይኖራል።
4 ለቅኖች ብርሃን በጨለማ ወጣ፤ መሓሪና ይቅር ባይ ጻድቅም ነው።
5 ቸር ሰው ይራራል ያበድራልም፥ በፍርድም ነገሩን ይፈጽማል።
6 ለዘላለም አይናወጥም፤ የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል።
7 ከክፉ ነገር አይፈራም፤ በእግዚአብሔር ለመታመን ልቡ የጸና ነው።
8 በጠላቶቹ ላይ እስኪያይ ድረስ ልቡ ጽኑ ነው፥ አይፈራም።
9 በተነ ለችግረኞችም ሰጠ፤ ጽድቁ ለዘላለም ዓለም ይኖራል፤ ቀንዱ በክብር ከፍ ከፍ ይላል።
10 ኃጢአተኛም አይቶ ይቈጣል፥ ጥርሱንም ያፋጫል፥ ይቀልጣልም፤ የኃጢአተኞችም ምኞት ትጠፋለች።
1 ሃሌ ሉያ። የእግዚአብሔር ባሪያዎች ሆይ፥ አመስግኑት፥ የእግዚአብሔርንም ስም አመስግኑ።
2 ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ የእግዚአብሔር ስም ቡሩክ ይሁን።
3 ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያው ድረስ የእግዚአብሔር ስም ይመስገን።
4 እግዚአብሔር በአሕዛብ ሁሉ ላይ ከፍተኛ ነው፥ ክብሩም ከሰማያት በላይ ነው።
5 እንደ አምላካችን እንደ እግዚአብሔር ማን ነው? በላይ የሚኖር፤
6 በሰማይና በምድር የተዋረዱትን የሚያይ፤
7 – 8 ከአለቆች ጋር ከሕዝቡም አለቆች ጋር ያኖረው ዘንድ ችግረኛን ከመሬት የሚያነሣ፥ ምስኪኑንም ከፋንድያ ከፍ ከፍ የሚያደርግ፤
9 መካኒቱን በቤት የሚያኖራት፥ ደስ የተሰኘችም የልጆች እናት የሚያደርጋት። ሃሌ ሉያ።
ሃሌ ሉያ።
1 እስራኤል ከግብጽ፥ የያዕቆብም ቤት ከእንግዳ ሕዝብ በወጣ ጊዜ፥
2 ይሁዳ መቅደሱ፥ እስራኤልም ግዛቱ ሆነ።
3 ባሕር አየች ሸሸችም፥ ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ።
4 ተራሮች እንደ ኮርማዎች፥ ኮረብቶችም እንደ ጠቦቶች ዘለሉ።
5 አንቺ ባሕር የሸሸሽ፥ አንቺም ዮርዳኖስ ወደ ኋላሽ የተመለስሽ፥ምን ሆናችኋል?
6 እናንተም ተራሮች፥ እንደ ኮርማዎች፥ ኮረብቶችስ፥ እንደ ጠቦቶች ለምን ዘለላችሁ?
7 ከያዕቆብ አምላክ ፊት፥ ከጌታ ፊት ምድር ተናወጠች፤
8 ድንጋዩን ወደ ውኃ መቆሚያ፥ ጭንጫውንም ወደ ውኃ ምንጭ ከለወጠ።
1 ለእኛ አይደለም፥ አቤቱ፥ ለእኛ አይደለም፥ ነገር ግን ለስምህ ስለ ምሕረትህ ስለ እውነትህም ምስጋናን ስጥ።
2 አሕዛብ። አምላካቸው ወዴት ነው? አይበሉ።
3 አምላካችንስ በላይ በሰማይ ነው፤ በሰማይም በምድርም የፈቀደውን ሁሉ አደረገ።
4 የአሕዛብ ጣዖታቶች የወርቅና የብር፥ የሰው እጅ ሥራ ናቸው።
5 አፍ አላቸው አይናገሩምም፤ ዓይን አላቸው አያዩምም፤
6 ጆሮ አላቸው አይሰሙምም፤ አፍንጫ አላቸው አያሸትቱምም፤
7 እጅ አላቸው አይዳሰሱምም፤ እግር አላቸው አይሄዱምም፤ በጕሮሮአቸውም አይናገሩም።
8 የሚሠሩአቸውም የሚያምኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁኑ።
9 የእስራኤል ቤት ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።
10 የአሮን ቤት ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።
11 እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።
12 እግዚአብሔር አሰበን ይባርከንማል፤ የእስራኤልን ቤት ይባረካል፥ የአሮንንም ቤት ይባረካል።
13 እግዚአብሔርን የሚፈሩትን፥ ትንንሾችንና ትልልቆችን ይባርካል።
14 እግዚአብሔር በላያችሁ፥ በላያችሁና በልጆቻችሁ ላይ ይጨምር።
15 እናንተ ሰማይንና ምድርን ለሠራ ለእግዚአብሔር የተባረካችሁ ናችሁ።
16 የሰማያት ሰማይ ለእግዚአብሔር ነው፤ ምድርን ግን ለሰው ልጆች ሰጣት።
17 አቤቱ፥ ሙታን የሚያመሰግኑህ አይደሉም ወደ ሲኦልም የሚወርዱ ሁሉ፤
18 እኛ ሕያዋን ግን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እግዚአብሔርን እንባርካለን። ሃሌ ሉያ።
ሃሌ ሉያ።
1 እግዚአብሔር የልመናዬን ድምፅ ሰምቶአልና ወደድሁት።
2 ጆሮውን ወደ እኔ አዘንብሎአልና በዘመኔ ሁሉ እጠራዋለሁ።
3 የሞት ጣር ያዘኝ፥ የሲኦልም ሕማም አገኘኝ፤ ጭንቀትንና መከራን አገኘሁ።
4 የእግዚአብሔርንም ስም ጠራሁ። አቤቱ፥ ነፍሴን አድናት።
5 እግዚአብሔር መሓሪና ጻድቅ ነው፥ አምላካችንም ይቅር ባይ ነው።
6 እግዚአብሔር ሕፃናትን ይጠብቃል፤ ተቸገርሁ እርሱም አዳነኝ።
7 ነፍሴ ሆይ፥ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሺ፥ እግዚአብሔር መልካም አድርጎልሻልና፤
8 ነፍሴን ከሞት፥ ዓይኔንም ከእንባ፥ እግሬንም ከመሰናከል አድኖአልና።
9 በሕያዋን አገር በእግዚአብሔር ፊት እሄዳለሁ።
10 አመንሁ ስለዚህም ተናገርሁ፤ እኔም እጅግ ተቸገርሁ።
11 እኔም ከድንጋጤዬ የተነሣ። ሰው ሁሉ ሐሰተኛ ነው አልሁ።
12 ስላደረገልኝ ሁሉ ለእግዚአብሔር ምንን እመልሳለሁ?
13 የመድኃኒትን ጽዋ እቀበላለሁ፥ የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
14 በሕዝቡ ሁሉ ፊት ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ።
15 የቅዱሳኑ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው።
16 አቤቱ፥ እኔ ባሪያህ ነኝ፥ ባሪያህ ነኝ፥ የሴት ባሪያህም ልጅ ነኝ፤ ሰንሰለቴን ሰበርህ።
17 ለአንተ የምስጋና መሥዋዕትን እሠዋለሁ፥ የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
18 በሕዝቡ ሁሉ ፊት ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ፥
19 በእግዚአብሔር ቤት አደባባይ፥ ኢየሩሳሌም ሆይ፥ በመካከልሽም። ሃሌሉያ

ሃሌ ሉያ።
1 አሕዛብ ሁላችሁ፥ እግዚአብሔርን አመስግኑት፥ ወገኖችም ሁሉ ያመስግኑት፤
2 ምሕረቱ በእኛ ላይ ጸንታለችና፤ የእግዚአብሔርም እውነት ለዘላለም ትኖራለች። ሃሌ ሉያ።;
ሃሌ ሉያ።
1 እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ ቸር ነውና፤ ምሕረቱ ለዘላለም ናትና።
2 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘላለም እንደ ሆነች የእስራኤል ቤት አሁን ይንገሩ።
3 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘላለም እንደ ሆነች የአሮን ቤት አሁን ይንገሩ።
4 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘላለም እንደ ሆነች እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሁሉ አሁን ይንገሩ።
5 በተጨነቅሁ ጊዜ እግዚአብሔርን ጠራሁት፤ ሰማኝ አሰፋልኝም።
6 እግዚአብሔር ረዳቴ ነው፥ አልፈራም ሰው ምን ያደርገኛል?
7 እግዚአብሔር ረዳቴ ነው፥ እኔም በጠላቶቼ ላይ አያለሁ።
8 በሰው ከመታመን ይልቅ በእግዚአብሔር መታመን ይሻላል።
9 በገዦች ተስፋ ከማድረግ ይልቅ በእግዚአብሔር ተስፋ ማድረግ ይሻላል።
10 አሕዛብ ሁሉ ከበቡኝ፥ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው፤
11 መክበቡንስ ከበቡኝ፥ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው፤
12 ንብ ማርን እንዲከብብ ከበቡኝ፥ እሳትም በእሾህ ውስጥ እንዲነድድ ነደዱ፥ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው።
13 ገፋኸኝ፥ ለመውደቅም ተንገዳገድሁ፤ እግዚአብሔር ግን አገዘኝ።
14 ኃይሌም ዝማሬዬም እግዚአብሔር ነው፥ እርሱም መድኃኒት ሆነልኝ።
15 የእልልታና የመድኃኒት ድምፅ በጻድቃን ድንኳን ነው፤ የእግዚአብሔር ቀኝ ኃይልን አደረገች።
16 የእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ አደረገችኝ፤ የእግዚአብሔር ቀኝ ኃይልን አደረገች።
17 አልሞትም በሕይወት እኖራለሁ እንጂ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እናገራለሁ።
18 መገሠጽስ እግዚአብሔር ገሠጸኝ፤ ለሞት ግን አልሰጠኝም።
19 የጽድቅን ደጆች ክፈቱልኝ፤ ወደ እነርሱ ገብቼ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ።
20 ይህች የእግዚአብሔር ደጅ ናት፤ ወደ እርስዋ ጻድቃን ይገባሉ።
21 ሰምተኸኛልና፥ መድኃኒትም ሆነኸኛልና አመሰግንሃለሁ።
22 ግንበኞች የናቁት ድንጋይ፥ እርሱ የማዕዘን ራስ ሆነ፥
23 ይህች ከእግዚአብሔር ዘንድ ሆነች፥ ለዓይናችንም ድንቅ ናት።
24 እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት፤ ሐሤትን እናድርግ፥ በእርስዋም ደስ ይበለን።
25 አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አድን፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አቅና።
26 በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ ከእግዚአብሔር ቤት መረቅናችሁ።
27 እግዚአብሔር አምላክ ነው፥ ለእኛም በራልን፤ እስከ መሠዊያው ቀንዶች ድረስ የበዓሉን መሥዋዕት በገመድ እሰሩት።
28 አንተ አምላኬ ነህ አመሰግንህማለሁ። አንተ አምላኬ ነህ፥ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ፤ ሰምተኸኛልና፥ መድኃኒትም ሆነኸኛልና አመሰግንሃለሁ።
29 እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ ቸር ነውና፤ ምሕረቱ ለዘላለም ናትና።
1 በመንገዳቸው ንጹሐን የሆኑ፥ በእግዚአብሔርም ሕግ የሚሄዱ ምስጉኖች ናቸው።
2 ምስክሩን የሚፈልጉ፥ በፍጹም ልብ የሚሹት ምስጉኖች ናቸው፤
3 ዓመፅንም አያደርጉም፥ በመንገዶቹም ይሄዳሉ።
4 ትእዛዛትህን እጅግ እንጠብቅ ዘንድ አንተ አዘዝህ።
5 ሥርዓትህን ለመጠበቅ፤ መንገዶቼ ይቀኑ ዘንድ እወድድ ነበር።
6 ትእዛዝህን ሁሉ ስመለከት በዚያን ጊዜ አላፍርም።
7 አቤቱ፥ የጽድቅህን ፍርድ ስማር በቅን ልብ አመሰግንሃለሁ።
8 ሥርዓትህን እጠብቃለሁ፤ በፍጹም አትጣለኝ። ቤት
9 ጕልማሳ መንገዱን በምን ያነጻል? ቃልህን በመጠበቅ ነው።
10 በፍጹም ልቤ ፈለግሁህ፥ ከትእዛዝህ አታርቀኝ።
11 አንተ እንዳልበድል፥ ቃልህን በልቤ ሰወርሁ።
12 አቤቱ፥ አንተ ቡሩክ ነህ፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ።
13 የአፍህን ፍርድ ሁሉ በከንፈሬ ነገርሁ።
14 እንደ ብልጥግና ሁሉ በምስክርህ መንገድ ደስ አለኝ።
15 ትእዛዝህን አሰላስላለሁ፥ መንገድህንም እፈልጋለሁ።
16 በትእዛዝህ ደስ ይለኛል፤ ቃልህንም አልረሳም። ጋሜል
17 ለባሪያህ መልካም አድርግ ሕያው እንድሆን፥ ቃልህንም እንድጠብቅ።
18 ዓይኖቼን ክፈት፥ ከሕግህም ተኣምራትህን አያለሁ።
19 እኔ በምድር እንግዳ ነኝ፤ ትእዛዛትህን ከእኔ አትሰውር።
20 ነፍሴ ሁልጊዜ ፍርድህን እጅግ ናፈቀች።
21 ከትእዛዛትህ የሳቱትን ትዕቢተኞችንና ርጉማንን ዘለፍህ።
22 ምስክርህን ፈልጌአለሁና። ስድብንና ነውርን ከእኔ አርቅ።
23 አለቆች ደግሞ ተቀምጠው እኔን አሙኝ፤ ባሪያህ ግን ሕግህን ያሰላስል ነበር።
24 ምስክርህም ተድላዬ ነው፥ ሥርዓትህም መካሪዬ ነው። ዳሌጥ
25 ነፍሴ ወደ ምድር ተጠጋች፤ እንደ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
26 መንገድህን ነገርሁ ሰማኸኝም፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ።
27 የሥርዓትህን መንገድ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ተኣምራትህንም አሰላስላለሁ።
28 ከኀዘን የተነሣ ነፍሴ አንቀላፋች፤ በቃልህ አጠንክረኝ።
29 የዓመፅን መንገድ ከእኔ አርቅ፥ በሕግህም ማረኝ፤
30 የእውነትህን መንገድ መረጥሁ፥ ፍርድህንም አልረሳሁም።
31 አቤቱ፥ ምስክርህን ተጠጋሁ፤ አታሳፍረኝ።
32 ልቤን ባሰፋኸው ጊዜ፥ በትእዛዝህ መንገድ ሮጥሁ። ሄ
33 አቤቱ፥ የሥርዓትህን መንገድ አስተምረኝ፥ ሁልጊዜም እፈልገዋለሁ።
34 እንዳስተውል አድርገኝ፥ ሕግህንም እፈልጋለሁ፤ በፍጹም ልቤም እጠብቀዋለሁ።
35 እርስዋን ወድጃለሁና የትእዛዝህን መንገድ ምራኝ።
36 ልቤን ወደ ምስክርህ አዘንብል፥ ወደ ስስትም አይሁን።
37 ከንቱ ነገርን እንዳያዩ ዓይኖቼን መልስ፤ በመንገድህ ሕያው አድርገኝ።
38 እንዲፈራህ ባሪያህን በቃልህ አጽና።
39 ፍርድህ መልካም ናትና የተጠራጠርሁትን ስድብ ከእኔ አርቅ።
40 እነሆ፥ ትእዛዝህን ናፈቅሁ፤ በጽድቅህ ሕያው አድርገኝ ዋው
41 አቤቱ፥ እንደ ቃልህ፥ ምሕረትህና መድኃኒትህ ይምጡልኝ።
42 በቃልህ ታምኛለሁና ለሚሰድቡኝ በነገር እመልስላቸዋለሁ።
43 በፍርድህም ታምኛለሁና የእውነትን ቃል ከአፌ ፈጽመህ አታርቅ።
44 ለዘላለም ዓለም ሁልጊዜ ሕግህን እጠብቃለሁ።
45 ትእዛዛትህንም ፈልጌአለሁና አስፍቼ እሄዳለሁ።
46 በነገሥታት ፊት ምስክርህን እናገራለሁ፥ አላፍርምም፤
47 እጅግም በወደድኋቸው በትእዛዛትህ ደስ ይለኛል።
48 እጆቼንም ወደ ወደድኋቸው ወደ ትእዛዛትህ አነሣለሁ፤ ሥርዓትህንም አሰላስላሁ። ዛይ
49 ለባሪያህ ተስፋ ያስደረግኸውን ቃልህን አስብ።
50 ቃልህ ሕያው አድርጎኛልና ይህች በመከራዬ ደስ አሰኘችኝ።
51 ትዕቢተኞች እጅግ ዐመፁ፤ እኔ ግን ከሕግህ አልራቅሁም።
52 ከጥንት የነበረውን ፍርድህን አሰብሁ፥ አቤቱ፥ ተጽናናሁም።
53 ሕግህን ከተዉ ከኃጢአተኞች የተነሣ ኅዘን ያዘኝ።
54 በእንግድነቴ አገር ሥርዓትህ መዝሙር ሆነችኝ።
55 አቤቱ፥ በሌሊት ስምህን አሰብሁ፥ ሕግህንም ጠበቅሁ።
56 ትእዛዛትህንም ፈልጌአለሁና፤ ይህች ሆነችልኝ። ሔት
57 እግዚአብሔር ክፍሌ ነው፤ ሕግህን እጠብቃለሁ አልሁ።
58 በፍጹም ልቤ ወደ ፊትህ ተማለልሁ፤ እንደ ቃልህ ማረኝ።
59 ስለ መንገዶችህ አሰብሁ፥ እግሬንም ወደ ምስክሮችህ መለስሁ።
60 ትእዛዝህን ለመጠበቅ ጨከንሁ አልዘገየሁምም።
61 የኃጥኣን ገመዶች ተተበተቡብኝ፤ ሕግህን ግን አልረሳሁም።
62 ስለ ጽድቅህ ፍርድ፥ በእኩለ ሌሊት አመሰግንህ ዘንድ እነሣለሁ።
63 እኔ ለሚፈሩህ ሁሉ፥ ትእዛዝህንም ለሚጠብቁ ባልንጀራ ነኝ።
64 አቤቱ፥ ምሕረትህ በምድር ሁሉ ሞላች፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ። ጤት
65 አቤቱ፥ እንደ ቃልህ ለባሪያህ መልካም አደረግህ።
66 በትእዛዛትህ ታምኛለሁና መልካም ምክርና እውቀትን አስተምረኝ።
67 እኔ ሳልጨነቅ ሳትሁ፤ አሁን ግን ቃልህን ጠበቅሁ።
68 አቤቱ፥ አንተ ቸር ነህ፥ በቸርነትህም ሥርዓትህን አስተምረኝ።
69 የትዕቢተኞች ዓመፅ በላዬ በዛ፤ እኔ ግን በፍጹም ልቤ ትእዛዛትህን እፈልጋለሁ።
70 ልባቸው እንደ ወተት ረጋ፤ እኔ ግን በሕግህ ደስ ይለኛል።
71 ሥርዓትህን እማር ዘንድ ያስጨነቅኸኝ መልካም ሆነልኝ።
72 ከአእላፋት ወርቅና ብር ይልቅ የአፍህ ሕግ ይሻለኛል። ዮድ
73 እጆችህ ሠሩኝ አበጃጁኝም፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ትእዛዛትህንም እማራለሁ።
74 በቃልህ ታምኛለሁና የሚፈሩህ እኔን አይተው ደስ ይላቸዋል።
75 አቤቱ፥ ፍርድህ ጽድቅ እንደ ሆነች፥ በእውነትህም እንዳስቸገርኸኝ አወቅሁ።
76 ምሕረትህ ለመጽናናቴ ትሁነኝ፥ እንደ ቃልህም ለባሪያህ ይሁነው።
77 ሕግህ ተድላዬ ናትና ቸርነትህ ትምጣልኝ፥ በሕይወትም ልኑር።
78 ትዕቢተኞች በዓመፅ ጠምመውብኛልና ይፈሩ፤ እኔ ግን በትእዛዝህ እጫወታለሁ።
79 የሚፈሩህና ምስክሮችህን የሚያውቁ ወደ እኔ ይመለሱ።
80 እንዳላፍር ልቤ በሥርዓትህ የቀና ይሁን። ካፍ
81 ነፍሴ መድኃኒትህን ናፈቀች፤ በቃልህም ታመንሁ።
82 መቼ ታጽናናኛለህ እያልሁ ዓይኖቼ ስለ ቃልህ ፈዘዙ።
83 በጢስ እንዳለ አቁማዳ ሆኛለሁና፤ ሥርዓትህን ግን አልረሳሁም።
84 የባሪያህ ዘመኖች ስንት ናቸው? በሚያሳድዱኝስ ላይ መቼ ትፈርድልኛለህ?
85 ኃጢአተኞች ጨዋታን ነገሩኝ፥ አቤቱ፥ እንደ ሕግህ ግን አይደለም።
86 ትእዛዛትህ ሁሉ እውነት ናቸው፤ በዓመፅ አሳድደውኛል፤ እርዳኝ።
87 ከምድር ሊያጠፉኝ ጥቂት ቀርቶአቸው ነበር፤ እኔ ግን ትእዛዛትህን አልተውሁም።
88 እንደ ምሕረትህ ሕያው አድርገኝ፤ የአፍህንም ምስክር እጠብቃለሁ። ላሜድ
89 አቤቱ፥ ቃልህ በሰማይ ለዘላለም ይኖራል።
90 እውነትህ ለልጅ ልጅ ናት፤ ምድርን መሠረትሃት እርስዋም ትኖራለች።
91 ሁሉም ባሪያዎችህ ናቸውና ቀኑ በትእዛዝህ ይኖራል።
92 ሕግህ ተድላዬ ባይሆን፥ ቀድሞ በጐስቍልናዬ በጠፋሁ ነበር።
93 በእርሱ ሕያው አድርገኸኛልና ፍርድህን ለዘላለም አልረሳም።
94 እኔ የአንተ ነኝ፤ ፍርድህን ፈልጌአልሁና አድነኝ።
95 ኃጢአተኞች ያጠፉኝ ዘንድ ጠበቁኝ፤ ምስክርህን ግን መረመርሁ።
96 የሥራህን ሁሉ ፍጻሜ አየሁ፤ ትእዛዝህ ግን እጅግ ሰፊ ነው። ሜም
97 አቤቱ፥ ሕግህን እንደ ምን እጅግ ወደድሁ! ቀኑን ሁሉ እርሱ ትዝታዬ ነው።
98 ለዘላለም ለእኔ ነውና ትእዛዝህ ከጠላቶቼ ይልቅ አስተዋይ አደረገኝ።
99 ምስክርህ ትዝታዬ ነውና ካስተማሩኝ ሁሉ ይልቅ አስተዋልሁ።
100 ትእዛዝህን ፈልጌአለሁና ከሽማግሌዎች ይልቅ አስተዋልሁ።
101 ቃልህን እጠብቅ ዘንድ ከክፉ መንገድ ሁሉ እግሬን ከለከልሁ።
102 አስተምረኸኛልና ከፍርድህ አልራቅሁም።
103 ቃልህ ለጕሮሮዬ ጣፋጭ ነው፤ ከማርና ከወለላ ይልቅ ለአፌ ጣፈጠኝ።
104 ከትእዛዝህ የተነሣ አስተዋልሁ፤ ስለዚህ የሐሰትን መንገድ ጠላሁ። ኖን
105 ሕግህ ለእግሬ መብራት፥ ለመንገዴ ብርሃን ነው።
106 የጽድቅህን ፍርድ እጠብቅ ዘንድ ማልሁ፥ አጸናሁም።
107 እጅግ ተቸገርሁ፤ አቤቱ፥ እንደ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
108 አቤቱ፥ ከአፌ የሚወጣውን ቃል ውደድ፥ ፍርድህንም አስተምረኝ።
109 ነፍሴ ሁልጊዜ በእጅህ ውስጥ ናት፤ ሕግህን ግን አልረሳሁም።
110 ኃጢአተኞች ወጥመድን ዘረጉብኝ፤ ከትእዛዝህ ግን አልሳትሁም።
111 የልቤ ደስታ ነውና ምስክርህን ለዘላለም ወረስሁ።
112 ለዘላለም ለፍጻሜውም ትእዛዝህን አደርግ ዘንድ ልቤን አዘነበልሁ። ሳምኬት
113 ዓመፀኞችን ጠላሁ፥ ሕግህን ግን ወደድሁ።
114 አንተ ረዳቴና መጠጊያዬ ነህ፥ በቃልህም ተማመንሁ።
115 እናንተ ኃጢአተኞች፥ ከእኔ ራቁ፥ የአምላኬንም ትእዛዝ ልፈልግ።
116 እንደ ቃልህ ደግፈኝ፥ ሕያውም እሆናለሁ። ከተስፋዬም አልፈር።
117 እርዳኝ እድናለሁም፥ ሁልጊዜም ሥርዓትህን እመረምራለሁ።
118 ምኞታቸው ዓመፃ ነውና ከሥርዓትህ የሚርቁትን ሁሉ አጐሳቈልሃቸው።
119 የምድርን ኃጢአተኞች ሁሉ እንደ ርኵሰት አጠፋሃቸው፤ ስለዚህ ምስክርህን ወደድሁ።
120 ሥጋዬ አንተን ከመፍራት የተነሣ ደንገጠ፤ ከፍርድህ የተነሣ ፈርቻለሁ። ዔ
121 ፍርድንና ጽድቅን ሠራሁ፤ ለሚያስጨንቁኝ አሳልፈህ አትስጠኝ።
122 ባሪያህን በመልካም ጠብቀው፤ ትዕቢተኞችም አይጋፉኝ።
123 ዓይኖቼ ለማዳንህ፥ ለጽድቅህም ቃል ፈዘዙ።
124 ለባሪያህ እንደ ምሕረትህ አድርግ፥ ሥርዓትህንም አስተምረኝ።
125 እኔ ባሪያህ ነኝ፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ምስክርህንም አውቃለሁ።
126 ለእግዚአብሔር የሥራ ጊዜ ነው፥ ሕግህንም ሻሩት።
127 ስለዚህ ከወርቅና ከዕንቍ ይልቅ ትእዛዝህን ወደድሁ።
128 ስለዚህ ወደ ትእዛዝህ ሁሉ አቀናሁ፥ የዓመፅንም መንገድ ሁሉ ጠላሁ። ፌ
129 ምስክሮችህ ድንቆች ናቸው፤ ስለዚህ ነፍሴ ፈለገቻቸው።
130 የቃልህ ፍቺ ያበራል፥ ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል።
131 አፌን ከፈትሁ፥ አለከለክሁም፤ ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና።
132 ስምህን ለሚወድዱ እንድምታደርገው ፍርድ፥ ወደ እኔ ተመልከተ ማረኝም።
133 አካሄድን እንደ ቃልህ አቅና፤ ኃጢአትም ሁሉ አይግዛኝ።
134 ከሰው ግፍ አድነኝ፤ ትእዛዝህንም እጠብቃለሁ።
135 በባሪያህ ላይ ፊትህን አብራ፥ ሥርዓትህንም አሰተምረኝ።
136 ሕግህን አልጠበቅሁምና የውኃ ፈሳሽ ከዓይኖቼ ፈሰሰ። ጻዴ
137 አቤቱ፥ አንተ ጻድቅ ነህ፥ ፍርድህም ቅን ነው።
138 ምስክርህን በጽድቅ አዘዝህ፥ እጅግም ቅን ነው።
139 ጠላቶቼ ቃልህን ረስተዋልና የቤትህ ቅንዓት አቀለጠኝ።
140 ቃልህ እጅግ የነጠረ ነው፥ ባሪያህም ወደደው።
141 እኔ ታናሽና የተናቅሁ ነኝ፤ ትእዛዛትህን ግን አልረሳሁም።
142 ጽድቅህ የዘላለም ጽድቅ ነው፥ ቃልህም እውነት ነው።
143 መከራና ችግር አገኙኝ፤ ትእዛዛትህ ግን ተድላዬ ናቸው።
144 ምስክርህ ለዘላለም ጽድቅ ነው፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ በሕይወትም አኑረኝ። ቆፍ
145 በፍጹም ልቤ ጮኽሁ፥ አቤቱ፥ ስማኝ፤ ሥርዓትህን እፈልጋለሁ።
146 ወደ አንተ ጮኽሁ፤ አድነኝ፥ ምስክርህንም እጠብቃለሁ።
147 ማለዳ ጮኽሁ፤ ቃልህንም ተስፋ አድርጌአለሁ።
148 ቃልህን አስብ ዘንድ ዓይኖቼ ለመማለድ ቀደሙ።
149 አቤቱ፥ እንደ ቸርነትህ ድምፄን ስማ፤ እንደ ፍርድህ ሕያው አድርገኝ።
150 በዓመፃ የሚያሳድዱኝ ቀረቡ፥ ከሕግህም ራቁ።
151 አቤቱ፥ አንተ ቅርብ ነህ፥ መንገዶችህም ሁሉ ቅኖች ናቸው።
152 ከዘላለም እንደ መሠረትኸው ከቀድሞ ጀምሮ ከምስክርህ የተነሣ አወቅሁ። ሬስ
153 ሕግህን አልረሳሁምና ችግሬን ተመልከት አድነኝም።
154 ፍርዴን ፍረድ አድነኝም፤ ስለ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
155 መድኃኒት ከኅጥኣን ሩቅ ነው፥ ሥርዓትህን አልፈለጉምና።
156 አቤቱ፥ ቸርነትህ እጅግ ብዙ ነው፤ እንደ ፍርድህ ሕያው አድርገኝ።
157 ያሳደዱኝና ያስጨነቁኝ ብዙዎች ናቸው፤ ከምስክር ግን ፈቀቅ አላልሁም።
158 ቃልህን አልጠበቁምና ሰነፎችን አይቼ አዘንሁ።
159 ትእዛዝህን እንደ ወደድሁ ተመልከት፤ አቤቱ፥ በምሕረትህ ሕያው አድርገኝ።
160 የቃልህ መጀመሪያ እውነት ነው፥ የጽድቅህንም ፍርድ ሁሉ ለዘላለም ነው። ሳን
161 ገዢዎች በከንቱ አሳደዱኝ፤ ከቃልህ የተነሣ ግን ልቤ ደነገጠብኝ።
162 ብዙ ምርኮ እንዳገኘ በቃልህ ደስ አለኝ።
163 ዓመፃን ጠላሁ ተጸየፍሁም፤ ሕግን ግን ወደድሁ።
164 ስለ ጽድቅህ ፍርድ ሰባት ጊዜ በቀን አመሰግንሃለሁ።
165 ሕግህን ለሚወድዱ ብዙ ሰላም ነው፥ ዕንቅፋትም የለባቸውም።
166 አቤቱ፥ ማዳንህን ተስፋ አደርግሁ፥ ትእዛዛትህንም ጠበቅሁ።
167 ነፍሴ ምስክርህን ጠበቀች እጅግም ወደደችው።
168 መንገዶቼ ሁሉ በፊትህ ናቸውና ትእዛዝህንና ምስክርህን ጠበቅሁ። ታው
169 አቤቱ፥ ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትቅረብ፤ እንደ ቃልህም አስተዋይ አድርገኝ።
170 ልመናዬ ወደ ፊትህ ትድረስ፤ እንደ ቃልህ አድነኝ።
171 ሥርዓትህን አስተምረኸኛልና ከንፈሮቼ ምስጋናን አወጡ።
172 ትእዛዛትህ ሁሉ ጽድቅ ናቸውና አንደበቴ ቃልህን ተናገረ።
173 ትእዛዛትህን መርጫለሁና እጅህ የሚያድነኝ ይሁን።
174 አቤቱ፥ ማዳንህን ናፈቅሁ፤ ሕግህም ተድላዬ ነው።
175 ነፍሴ ትኑርልኝ ታመሰግንህማለች፥ ፍርድህም ይርዳኝ።
176 እንደ ጠፉ በግ ተቅበዘበዝሁ፤ ትእዛዛትህን አልረሳሁምና ባሪያህን ፈልገው።
የመዓርግ መዝሙር።
1 በተጨነቅሁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፥ ሰማኝም።
2 ከዓመፀኛ ከንፈር ከሸንጋይም አንደበት፥ አቤቱ፥ ነፍሴን አድናት።
3 ስለ ሽንገላ አንደበት ምንም ይሰጡሃል? ምንስ ይጨምሩልሃል?
4 እንደ በረሃ እንጨት ፍም የኃያላን ፍላጾች የተሳሉ ናቸው።
5 መኖሪያዬ የራቀ እኔ ወዮልኝ፤ በቄዳር ድንኳኖች አደርሁ።
6 ሰላምን ከሚጠሉ ጋር ነፍሴ ብዙ ጊዜ ኖረች።
7 እኔ ሰላማዊ ነኝ፤ በተናገኋቸው ጊዜ ግን በከንቱ ተሰለፉብኝ።
የመዓርግ መዝሙር።
1 ዓይኖቼ ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረዳቴ ከወዴት ይምጣ?
2 ረዳቴ ሰማይና ምድርን ከሠራ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።
3 እግርህን ለመናወጥ አይሰጠውም፤ የሚጠብቅህም አይተኛም።
4 እነሆ፥ እስራኤልን የሚጠብቅ አይተኛም አያንቀላፋምም።
5 እግዚአብሔር ይጠብቅሃል፥ እግዚአብሔርም በቀኝ እጅህ በኩል ይጋርድሃል።
6 ፀሐይ በቀን አያቃጥልህም ጨረቃም በሌሊት።
7 እግዚአብሔር ከክፉ ሁሉ ይጠብቅሃል፥ ነፍስህንም ይጠብቃታል።
8 ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እግዚአብሔር መውጣትህና መግባትህን ይጠብቃል።
የዳዊት የመዓርግ መዝሙር።
1 ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሄድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ።
2 ኢየሩሳሌም ሆይ፥ እግሮቻችን በአደባባይሽ ቆሙ።
3 ኢየሩሳሌምስ እርስ በርስዋ እንደ ተገጠገጠች ከተማ ተሠርታለች።
4 የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ ዘንድ፥ ለእስራኤል ምስክር ሊሆኑ የእግዚአብሔር ነገዶች ወደዚያ ይወጣሉ።
5 ዙፋኖች በዚያ ለፍርድ ተቀምጠዋልና፥ የዳዊት ቤት ዙፋኖች።
6 ለኢየሩሳሌም ሰላምን ለምኑ፤ አንተንም ለሚወድዱ ልማት ይሁን።
7 በኃይልህ ሰላም፥ በጌጠኛ ቤትህም ልማት ይሁን።
8 ስለ ወንድሞቼ ስለ ባልንጀሮቼም፥ በውስጥሽ ሰላም ይሁን አልሁ።
9 ስለ አምላካችን ስለ እግዚአብሔር ቤት ላንቺ መልካምነትሽን ፈለግሁ።
የመዓርግ መዝሙር።
1 በሰማይ የምትኖር ሆይ፥ ዓይኖቼን ወደ አንተ አነሣሁ።
2 እነሆ፥ የባሪያዎች ዓይኖች ወደ ጌታቸው እጅ እንደ ሆኑ፥ የባሪያይቱም ዓይን ወደ እመቤትዋ እጅ እንደ ሆነ፥ እንዲሁ እስኪምረን ድረስ ዓይናችን ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ነው።
3 ማረን፥ አቤቱ፥ ማረን፤ ንቀትን እጅግ ጠግበናልና፤
4 የባለጠጎች ስድብና የትዕቢተኞችን ንቀት ነፍሳችን እጅግ ጠገበች።
የዳዊት የመዓርግ መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ባይሆን እስራኤል እንዲህ ይበል።
2 እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ባይሆን ሰዎች በእኛ ላይ በተነሡ ጊዜ፥
3 ቍጣቸውን በላያችን በነደደ ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ ሕያዋን ሳለን በዋጡን ነበር፤
4 በዚያን ጊዜ ውኃ ባሰጠመን ነበር፥ በነፍሳችንም ላይ ፈሳሽ ባለፈ ነበር፤
5 በዚያን ጊዜ የጐርፍ ውኃ በነፍሳችን ላይ ባለፈ ነበር።
6 ለጥርሳቸው ንክሻ ያላደረገን እግዚአብሔር ይባረክ።
7 ነፍሳችን እንደ ወፍ ከአዳኞች ወጥመድ አመለጠች። ወጥመድ ተሰበረ እኛም አመለጥን።
8 ረድኤታችን ሰማይንና ምድርን በሠራ በእግዚአብሔር ስም ነው።
የመዓርግ መዝሙር።
1 በእግዚአብሔር የታመኑ እንደማይታወክ ለዘላለም እንደሚኖር እንደ ጽዮን ተራራ ናቸው።
2 ተራሮች በኢየሩሳሌም ዙሪያ እንደ ሆኑ፥ ከዛሬ ጀምሮ ለዘላለም፤ እግዚአብሔር በሕዝቡ ዙሪያ ነው።
3 ጻድቃን እጃቸውን ወደ ክፋት እንዳይዘረጉ የኃጥኣን በትር በጻድቃን ዕጣ ላይ አይኖርም።
4 አቤቱ፥ ለቸሮች ልባቸውም ለቀና መልካምን አድርግ።
5 ወደ ጠማማነት የሚመለሱትን ግን ዓመፃን ከሚሠሩት ጋር እግዚአብሔር ይወስዳቸዋል። ሰላም በእስራኤል ላይ ይሁን።
የመዓርግ መዝሙር።
1 እግዚአብሔር የጽዮንን ምርኮ በመለሰ ጊዜ፥ እጅግ ደስተኞች ሆንን።
2 በዚያን ጊዜ አፋችን ደስታን፥ አንደበታችንም ሐሴትን ሞላ፤ በዚያን ጊዜ በአሕዛብ ዘንድ። እግዚአብሔር ታላቅ ነገርን አደረገላቸው ተባለ።
3 እግዚአብሔር ታላቅ ነገርን አደረገልን፥ ደስም አለን።
4 አቤቱ፥ በደቡብ እንዳሉ ፈሳሾች ምርኮአችንን መልስ።
5 በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይለቅማሉ።
6 በሄዱ ጊዜ፥ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ።
የመዓርግ መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ፥ ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ፤ እግዚአብሔር ከተማን ካልጠበቀ፥ ጠባቂ በከንቱ ይተጋል።
2 በማለዳ መገሥገሣችሁም ከንቱ ነው። ለወዳጆቹ እንቅልፍን በሰጠ ጊዜ፥ እናንተ የመከራን እንጀራ የምትበሉ፥ ከተቀመጣችሁበት ተነሡ።
3 እነሆ፥ ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው፥ የሆድም ፍሬ የእርሱ ዋጋ ነው።
4 በኃያል እጅ እንዳሉ ፍላጾች፥ የጐልማስነት ልጆች እንዲሁ ናቸው።
5 ከእነርሱ ዘንድ ምኞቱን የሚፈጽም ብፁዕ ሰው ነው፤ ጠላቶቻቸውን በአደባባይ በተናገሩ ጊዜ እርሱ አያፍርም።
የመዓርግ መዝሙር።
1 እግዚአብሔርን የሚፈሩት ሁሉ፥ በመንገዶቹም የሚሄዱ ምስጉኖች ናቸው።
2 የድካምህንም ፍሬ ትመገባለህ፤ ምስጉን ነህ መልካምም ይሆንልሃል።
3 ሚስትህ በቤትህ እልፍኝ ውስጥ እንደሚያፈራ ወይን ናት፤ ልጆችህ በማዕድህ ዙሪያ እንደ ወይራ ቡቃያ ናቸው።
4 እነሆ፥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው እንዲህ ይባረካል።
5 እግዚአብሔር ከጽዮን ይባርክህ፤ በሕይወትህ ዘመን ሁሉ፥ የኢየሩሳሌምን መልካምነትዋን ታያለህ።
6 የልጆችህንም ልጆች ታያለህ። በእስራኤል ላይ ሰላም ይሁን።
የመዓርግ መዝሙር።
1 እስራኤል። ከትንሽነቴ ጀምሮ ብዙ ጊዜ ተሰለፉብኝ ይበል፤
2 ከትንሽነቴ ጀምሮ ብዙ ጊዜ ተሰለፉብኝ፤ ነገር ግን አላሸነፉኝም።
3 ኃጢአተኞች በጀርባዬ ላይ መቱኝ፥ ኃጢአታቸውንም አስረዘሙአት።
4 እግዚአብሔር ጻድቅ ነው፤ የኃጢአተኞችን አንገታቸውን ቈረጠ።
5 ጽዮንን የሚጠሉ ሁሉ ይፈሩ፥ ወደ ኋላቸውም ይመለሱ።
6 በሰገነት ላይ እንደ በቀለ ሣር፥ ሳይነቀል እንደሚደርቅ፥
7 ለሚያጭደው እጁን፥ ነዶዎቹን ለሚሰበስብ እቅፉን እንደማይሞላ ይሁኑ።
8 በመንገዱም የሚያልፉ። የእግዚአብሔር በረከት በእናንተ ላይ ይሁን፤ በእግዚአብሔር ስም እንመርቃችኋለን አይሉም።
የመዓርግ መዝሙር።
1 አቤቱ፥ አንተን ከጥልቅ ጠራሁህ።
2 አቤቱ፥ ድምፄን ስማ፤ ጆሮህ የልመናዬን ቃል የሚያደምጥ ይሁን።
3 አቤቱ፥ ኃጢአትንስ ብትጠባበቅ፥ አቤቱ፥ ማን ይቆማል?
4 ይቅርታ ከአንተ ዘንድ ነውና።
5 አቤቱ፥ ስለ ስምህ ተስፋ አደረግሁህ፤ ነፍሴ በሕግህ ታገሠች።
6 ከማለዳው ሰዓት ጀምሮ እስከ ሌሊት ነፍሴ በእግዚአብሔር ታመነች።
7 ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረት፥ በእርሱም ዘንድ ብዙ ማዳን ነውና እስራኤል በእግዚአብሔር ይታመን።
8 እርሱም እስራኤልን ከኃጢአቱ ሁሉ ያድነዋል።
የዳዊት መዓርግ መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ልቤ አይታበይብኝ፥ ዓይኖቼም ከፍ ከፍ አይበሉብኝ፤ ከትልልቆች ጋር፥ ከእኔም ይበልጥ ከሚከበሩ ጋር አልሄድሁም።
2 ነፍሴን አሳረፍኋት፥ የእናቱንም ጡት እንዳስተውት ዝም አሰኘኋት፤ ነፍሴ የእናቱን ጡት እንዳስተውት በእኔ ውስጥ ናት።
3 ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እስራኤል በእግዚአብሔር ይታመን።
የመዓርግ መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ዳዊትን ገርነቱንም ሁሉ አስብ፤
2 ለእግዚአብሔር እንደ ማለ፥ ለያዕቆብም አምላክ እንደ ተሳለ።
3 በእውነት ወደ ቤቴ ድንኳን አልገባም፥ ወደ ምንጣፌም አልጋ አልወጣም፥
4 ለዓይኖቼም መኝታ ለሽፋሽፍቶቼም እንቅልፍ፥ ለጕንጮቼም ዕረፍትን አልሰጥም፥
5 ለእግዚአብሔር ስፍራ፥ ለያዕቆብ አምላክ ማደሪያ እስካገኝ ድረስ ብሎ።
6 እነሆ፥ በኤፍራታ ሰማነው፥ በዱር ውስጥም አገኘነው።
7 ወደ ማደሪያዎቹ እንገባለን፤ እግሮቹ በሚቆሙበት ስፍራ እንሰግዳለን።
8 አቤቱ፥ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት።
9 ካህናቶችህ ጽድቅን ይልበሱ፥ ቅዱሳንህም ደስ ይበላቸው።
10 ስለ ዳዊት ስለ ባሪያህ የቀባኸውን ሰው ፊት አትመልስ።
11 እግዚአብሔር ለዳዊት በእውነት ማለ አይጸጸትምም፥ እንዲህ ብሎ። ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ።
12 ልጆችህ ኪዳኔን፥ ይህንም የማስተምራቸውን ምስክሬን ቢጠብቁ፥ ልጆቻቸው ደግሞ በዙፋንህ ላይ ለዘላለም ይቀመጣሉ።
13 እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ እንዲህ ብሎ።
14 ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።
15 አሮጊቶችዋን እጅግ እባርካለሁ፥ ድሆችዋንም እንጀራ አጠግባለሁ።
16 ካህናቶችዋንም ደኅንነትን አለብሳቸዋለሁ፥ ቅዱሳኖችዋም እጅግ ደስ ይላቸዋል።
17 በዚያ ለዳዊት ቀንድን አበቅላለሁ፥ ለቀባሁትም ሰው መብራትን አዘጋጃለሁ።
18 ጠላቶችንም እፍረትን አለብሳቸዋለሁ፤ በእርሱ ግን ቅድስናዬ ያብባል።

የዳዊት የመዓርግ መዝሙር።
1 ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ፥ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው።
2 ከራስ እስከ ጢም እንደሚፈስስ፥ እስከ አሮን ጢም፥ በልብሱ መደረቢያ እንደሚወርድ ሽቱ ነው።
3 በጽዮን ተራሮች እንደሚወርድ እንደ አርሞንዔም ጠል ነው፤ በዚያ እግዚአብሔር በረከቱን ሕይወትንም እስከ ዘላለም አዝዞአልና።
የመዓረግ መዝሙር።
1 እነሆ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ፥ በአምላካችን ቤት አደባባዬች የምትቆሙ እናንተ የእግዚአብሔር ባሪያዎች ሁላችሁ።
2 በሌሊት በቤተ መቅደስ ውስጥ እጆቻችሁን አንሡ፥ እግዚአብሔርንም ባርኩ።
3 ሰማይንና ምድርን የሠራ እግዚአብሔር ከጽዮን ይባርክህ።
ሃሌ ሉያ። የእግዚአብሔርን ስም አመስግኑ፤ እናንተ 1 የእግዚአብሔር ባሪያዎች ሆይ፥ አመስግኑት፥
2 በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ፥ በአምላካችን ቤት አደባባይ የምትቆሙ።
3 እግዚአብሔር ቸር ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ ለስሙ ዘምሩ፥ መልካም ነውና፤
4 እግዚአብሔር ያዕቆብን ለራሱ፥ እስራኤልንም ለመዝገቡ መርጦታልና፤
5 እግዚአብሔር ታላቅ እንደ ሆነ፥ ጌታችንም ከአማልክት ሁሉ እንዲበልጥ አውቄአለሁና።
6 በሰማይና በምድር በባሕርና በጥልቆች ሁሉ፥ እግዚአብሔር የወደደውን ሁሉ አደረገ።
7 ከምድር ዳር ደመናትን ያወጣል፤ በዝናብ ጊዜ መብረቅን አደረገ፤ ነፋሳትንም ከመዛግብቱ ያወጣል።
8 የግብጽን በኵር ልጆች ከሰው ጀምሮ እስከ እንስሳ ድረስ መታ።
9 ግብጽ ሆይ፥ በመካከልሽ በፈርዖንና በባሪያዎቹ ሁሉ ላይ ተኣምራትንና ድንቅን ሰደደ።
10 ብዙ አሕዛብን መታ፥ ብርቱዎችንም ነገሥታት ገደለ።
11 የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን፥ የባሳንንም ንጉሥ ዐግን፥ የከነዓንን መንግሥታት ሁሉ ገደለ፤
12 ምድራቸውንም ርስት አድርጎ ለእስራኤል ለሕዝቡ ርስት ሰጠ።
13 አቤቱ፥ ስምህ ለዘላለም ነው፥ ዝክርህም ለልጅ ልጅ ነው፤
14 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ይፈርዳልና፥ ባሪያዎቹንም ይረዳልና።
15 የአሕዛብ ጣዖታት የብርና የወርቅ፥ የሰው እጅ ሥራ ናቸው።
16 አፍ አላቸው፥ አይናገሩምም፤ ዓይን አላቸው፥ አያዩምም፤
17 ጆሮ አላቸው፥ አይሰሙምም፤ እስትንፋስም በአፋቸው የለም።
18 የሚሠሩአቸው ሁሉ የሚታመኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁን።
19 የእስራኤል ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት። የአሮን ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት፤
20 የሌዊ ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት።
21 በኢየሩሳሌም የሚያድር እግዚአብሔር ከጽዮን የተባረከ ነው። ሃሌ ሉያ።

1 እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ ቸር ነውና፥ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
2 የአማልክትን አምላክ አመስግኑ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
3 የጌቶችን ጌታ አመስግኑ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
4 እርሱ ብቻውን ታላቅ ተኣምራትን ያደረገ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
5 ሰማያትን በብልሃት የሠራ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
6 ምድርን በውኃ ላይ ያጸና፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
7 ብቻውን ታላላቅ ብርሃናትን የሠራ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
8 ለፀሐይ ቀንን ያስገዛው፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
9 ለጨረቃና ለከዋክብትም ሌሊትን ያስገዛቸው፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
10 ከበኵራቸው ጋር ግብጽን የመታ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
11 እስራኤልንም ከመካከላቸው ያወጣ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
12 በጸናች እጅ በተዘረጋችም ክንድ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
13 የኤርትራን ባሕር በየክፍሉ የከፈለ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
14 እስራኤልን በመካከሉ ያሳለፈ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
15 ፈርዖንንና ሠራዊቱን በኤርትራ ባሕር የጣለ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
16 ሕዝቡን በምድረ በዳ የመራ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
17 ታላላቅ ነገሥታትን የመታ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
18 ብርቱዎችንም ነገሥታት የገደለ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
19 የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
20 የባሳንን ንጉሥ ዐግን፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
21 ምድራቸውን ርስት አድርጎ የሰጠ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
22 ለባሪያው ለእስራኤል ርስት፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
23 እኛን በመዋረዳችን አስቦናልና፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
24 ከጠላቶቻችንም እጅ አድኖናልና፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤
25 ለሥጋ ሁሉ ምግብን የሚሰጥ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
26 የሰማይን አምላክ አመስግኑ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
1 በባቢሎን ወንዞች አጠገብ በዚያ ተቀመጥን፤ ጽዮንንም ባሰብናት ጊዜ አለቀስን።
2 በአኻያ ዛፎችዋ ላይ መሰንቆቻችንን ሰቀልን።
3 የማረኩን በዚያ የዝማሬን ቃል ፈለጉብን፥ የወሰዱንም። የጽዮንን ዝማሬ ዘምሩልን አሉን።
4 የእግዚአብሔርን ዝማሬ በባዕድ ምድር እንዴት እንዘምራለን?
5 ኢየሩሳሌም ሆይ፥ ብረሳሽ፥ ቀኜ ትርሳኝ።
6 ባላስብሽ፥ ምላሴ በጕሮሮዬ ይጣበቅ፤ ከደስታዬ ሁሉ በላይ ኢየሩሳሌምን ባልወድድ።
7 አቤቱ፥ በኢየሩሳሌም ቀን የኤዶምን ልጆች አስብ። እስከ መሠረትዋ ድረስ አፍርሱ አፍርሱ ያሉአትን።
8 አንቺ ወራዳ የባቢሎን ልጅ ሆይ፥ ስለ ተበቀልሽን የሚበቀልሽ የተመሰገነ ነው።
9 ሕፃናቶችሽን ይዞ በዓለት ላይ የሚፈጠፍጣቸው የተመሰገነ ነው።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ በፍጹም ልቤ አመሰግንሃለሁ፥ የአፌን ነገር ሰምተኸኛልና፤ በመላእክት ፊት እዘምርልሃለሁ።
2 ወደ ቅዱስ መቅደስህ እሰግዳለሁ፤ ስለ ምሕረትህና ስለ እውነትህ ስምህንም አመሰግናለሁ፥ በሁሉ ላይ ቅዱስ ስምህን ከፍ ከፍ አድርገሃልና።
3 በጠራሁህ ቀን በፍጥነት አድምጠኝ፤ ነፍሴን በኃይልህ በብዙ አጸናሃት።
4 አቤቱ፥ የምድር ነገሥታት ሁሉ ያመሰግኑሃል፤ የአፍህን ቃል ሁሉ ሰምተዋልና።
5 በእግዚአብሔርም መንገድ ይዘምራሉ፤ የእግዚአብሔር ክብር ታላቅ ነውና።
6 እግዚአብሔር ከፍ ያለ ነውና፥ ወደ ችግረኞችም ይመለከታልና፤ ትዕቢተኞችንም ከሩቅ ያውቃል።
7 በመከራ መካከል እንኳ ብሄድ፥ አንተ ሕያው ታደርገኛለህ፤ በጠላቶቼ ቍጣ ላይ እጆቼን ትዘረጋለህ፥ ቀኝህም ታድነኛለች።
8 እግዚአብሔር ብድራትን ይመልስልኛል፤ አቤቱ፥ ምሕረትህ ለዘላለም ነው፤ አቤቱ፥ የእጅህን ሥራ ቸል አትበል።
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ መረመርኸኝ፥ አወቅኸኝም።
2 አንተ መቀመጤንና መነሣቴን አወቅህ፤ አሳቤን ሁሉ ከሩቅ አስተዋልህ።
3 ፍለጋዬንና ዕረፍቴን አንተ መረመርህ፤ መንገዶቼን ሁሉ ቀድመህ አወቅህ፥
4 የዓመፃ ቃል በአንደበቴ እንደሌለ።
5 አቤቱ፥ አንተ እነሆ የቀድሞውንና የኋላውን አወቅህ፤ አንተ ፈጠርኸኝ፥ እጅህንም በላዬ አደረግህ።
6 እውቀትህ ከእኔ ይልቅ ተደነቀች፤ በረታች፥ ወደ እርስዋም ለመድረስ አልችልም።
7 ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ?
8 ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ አለህ። ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ።
9 እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥
10 በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች።
11 በውኑ ጨለማ ትሸፍነኛለች ብል፥ ሌሊት በዙሪያዬ ብርሃን ትሆናለች፤
12 ጨለማ በአንተ ዘንድ አይጨልምምና፥ ሌሊትም እንደ ቀን ታበራለችና፤ እንደ ጨለማዋ እንዲሁ ብርሃንዋ ነው።
13 አቤቱ፥ አንተ ኵላሊቴን ፈጥረሃልና፥ በእናቴም ሆድ ሰውረኸኛል።
14 ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ፤ ሥራህ ድንቅ ነው፥ ነፍሴም እጅግ ታውቀዋለች።
15 እኔ በስውር በተሠራሁ ጊዜ፥ አካሌም በምድር ታች በተሠራ ጊዜ አጥንቶቼ ከአንተ አልተሰወሩም።
16 ያልተሠራ አካሌን ዓይኖችህ አዩኝ፤ የተፈጠሩ ቀኖቼ ሁሉ አንድ ስንኳ ሳይኖር በመጽሐፍህ ተጻፉ።
17 አቤቱ፥ አሳቦችህ በእኔ ዘንድ እንደ ምን እጅግ የተከበሩ ናቸው! ቍጥራቸውም እንደ ምን በዛ!
18 ብቈጥራቸው ከአሸዋ ይልቅ ይበዛሉ፤ ተነሣሁም፥ እኔም ገና ከአንተ ጋር ነኝ።
19 አቤቱ፥ አንተ ኃጢአተኞችን የምትገድል ከሆንህስ፥ የደም ሰዎች ሆይ፥ ከእኔ ፈቀቅ በሉ።
20 በክፋት ይናገሩብሃልና፤ ጠላቶችህም በከንቱ ያምፁብሃል።
21 አቤቱ፥ የሚጠሉህን እኔ የጠላሁ አይደለሁምን? ስለ ጠላቶችህም አልተሰቀቅሁምን?
22 ፍጹም ጥል ጠላኋቸው፥ ጠላቶችም ሆኑኝ።
23 አቤቱ፥ መርምረኝ ልቤንም እወቅ፤ ፍተነኝ መንገዴንም እወቅ፤
24 በደልንም በእኔ ውስጥ ብታገኝ እይ፤ የዘላለምንም መንገድ ምራኝ።
ለመዘምራን አለቃ የዳዊት መዝሙር።
2 አቤቱ፥ ከክፉ ሰው አድነኝ፥ በልባቸውም ክፉ ካሰቡ ከዓመፀኞች ሰዎች ጠብቀኝ፤ ቀኑን ሁሉ ለሰልፍ ይከማቻሉ።
3 ምላሳቸውን እንደ እባብ ሳሉ፤ ከከንፈራቸው በታች የእፉኝት መርዝ ነው።
4 አቤቱ፥ ከኃጢአተኞች እጅ ጠብቀኝ፥ እርምጃዬንም ሊያሰናክሉ ከመከሩ ከዓመፀኞች አድነኝ።
5 ትዕቢተኞች ወጥመድን ሰወሩብኝ፥ ለእግሮቼም የወጥመድ ገመድን ዘረጉ፤ በመንገድ ዕንቅፋትን አኖሩ።
6 እግዚአብሔርንም። አንተ አምላኬ ነህ፤ የልመናዬን ቃል፥ አቤቱ፥ አድምጥ አልሁት።
7 አቤቱ፥ ጌታዬ፥ የመድኃኒቴ ጕልበት፥ በሰልፍ ቀን ራሴን ሸፈንህ።
8 አቤቱ፥ ከምኞቴ የተነሣ ለኃጢአተኞች አትስጠኝ፤ በላዬ ተማከሩ፤ እንዳይጓደዱ አትተወኝ።
9 የሚከብቡኝን ራስ የከንፈራቸው ክፋት ይክደናቸው።
10 የእሳት ፍም በላያቸው ይውደቅ፤ እንዳይነሡም ወደ እሳትና ወደ ማዕበል ይጣሉ።
11 ተናጋሪ ሰው በምድር ውስጥ አይጸናም፤ ዓመፀኛን ሰው ክፋት ለጥፋት ይፈልገዋል።
12 እግዚአብሔር ለድሀ ዳኝነትን ለችግረኛም ፍርድን እንዲያደርግ አወቅሁ።
13 ጻድቃንም በእውነት ስምህን ያመሰግናሉ፤ ቀኖችም በፊትህ ይኖራሉ።
የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ፤ ስማኝ፤ ወደ አንተ ስጮኽም የልመናዬን ቃል አድምጥ።
2 ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፥ እጅ መንሣቴም እንደ ሠርክ መሥዋዕት ትሁን።
3 አቤቱ፥ ለአፌ ጠባቂ አኑር፥ የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ።
4 ልቤን ወደ ክፉ ነገር አትመልሰው፥ ዓመፃን ከሚያደርጉ ሰዎች ጋር ለኃጢአት ምክንያት እንዳልሰጥ፤ ከምርጦቻቸውም ጋር አልተባበር።
5 ጻድቅ በምሕረት ይገሥጸኝ፥ ይዝለፈኝም፥ የኃጢአተኛ ዘይት ግን ራሴን አይቅባ፤ ጸሎቴ ገና በክፋታቸው ላይ ነውና።
6 ኃያላኖቻቸው በዓለት አጠገብ ተጣሉ፤ ጣፋጭ ናትና ቃሌን ይሰማሉ።
7 በምድር ላይ እንደ ተሰነጠቀ እንደ መሬት ጓል፥ እንዲሁ አጥንቶቻችን በሲኦል ተበተኑ።
8 አቤቱ ጌታ፥ ዓይኖቼ ወደ አንተ ናቸውና፤ በአንተ ታመንሁ፥ ነፍሴን አታውጣት።
9 ከሰወሩብኝ ወጥመድ፥ ዓመፅንም ከሚያደርጉ ሰዎች ዕንቅፋት ጠብቀኝ።
10 እኔ ብቻዬን እስካልፍ ድረስ ኃጢአተኞች በወጥመዳቸው ይውደቁ።
ጸሎት፤ በዋሻ በነበረ ጊዜ፤ የዳዊት ትምህርት።
1 በቃሌ ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፤ በቃሌ ወደ እግዚአብሔር ለመንሁ።
2 ልመናዬን በፊቱ አፈስሳለሁ፤ መከራዬንም በፊቴ እናገራለሁ።
3 ነፍሴ በውስጤ ባለቀች ጊዜ መንገዴን አወቅሁ፤ በምሄድባት በዚያች መንገድ ወጥመድን ሰወሩብኝ።
4 ወደ ቀኝ ተመለከትሁ አየሁም፥ የሚያውቀኝም አጣሁ፤ መሸሸጊያም የለኝም፥ ስለ ነፍሴም የሚመራመር የለም።
5 አቤቱ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ። አንተ ተስፋዬ ነህ፥ በሕያዋንም ምድር አንተ እድል ፈንታዬ ነህ አልሁ።
6 እጅግ ተቸግሬአለሁና ወደ ልመናዬ አድምጥ፤ በርትተውብኛልና ከሚያሳድዱኝ አድነኝ።
7 አቤቱ፥ ስምህን አመሰግን ዘንድ፤ ነፍሴን ከወህኒ አውጣት፤ ዋጋዬን እስክትሰጠኝ ድረስ ጻድቃን እኔን ይጠብቃሉ።
ልጁ ባሳደደው ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማ፤ በእውነትህ ልመናዬን አድምጥ፥ በጽድቅህም መልስልኝ።
2 ሕያው ሁሉ በፊትህ ጻድቅ አይደለምና ከባሪያህ ጋር ወደ ፍርድ አትግባ።
3 ጠላትህ ነፍሴን አሳድዶአታል፥ ሕይወቴንም በምድር ውስጥ አጐስቍሎአታል፤ ቀድሞ እንደ ሞተ ሰው በጨለማ አኑሮኛል።
4 ነፍሴ በውስጤ አለቀችብኝ፥ ልቤም በውስጤ ደነገጠብኝ።
5 የቀድሞውን ዘመን አሰብሁ፥ ሥራህንም ሁሉ አሰላሰልሁ፤ የእጅህንም ሥራ ተመለከትሁ።
6 እጆቼን ወደ አንተ ዘረጋሁ፤ ነፍሴም እንደ ምድረ በዳ አንተን ተጠማች።
7 አቤቱ፥ ፈጥነህ ስማኝ፤ ነፍሴ አልቃለች፤ ፊትህን ከኔ አትመልስ፥ ወደ ጕድጓድም እንደሚወርዱ አልሁን።
8 አንተን ታምኛለሁና በማለዳ ምሕረትህን አሰማኝ፤ አቤቱ፥ ነፍሴን ወደ አንተ አንሥቻለሁና የምሄድበትን መንገድ አስታውቀኝ።
9 አቤቱ፥ ወደ አንተ ተማፅኛለሁና ከጠላቶቼ አድነኝ።
10 አንተ አምላኬ ነህና ፈቃድህን ለማድረግ አስተምረኝ፤ ቅዱስ መንፈስህም በጽድቅ ምድር ይምራኝ።
11 አቤቱ፥ ስለ ስምህ ሕያው አድርገኝ፤ በጽድቅህም ነፍሴን ከመከራዋ አውጣት።
12 በምሕረትህ ጠላቶቼን ደምስሳቸው፥ እኔ ባሪያህ ነኝና ነፍሴን የሚያስጨንቁአትን ሁሉ አጥፋቸው።
ስለ ጎልያድ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር አምላኬ ይባረክ፥ ለእጆቼ ሰልፍን፥ ለጣቶቼም ዘመቻን የሚያስተምር፤
2 መሓሪዬና መሸሸጊያዬ፥ መጠጊያዬና መድኃኒቴ፤ ረዳቴና መታመኛዬም፤ ሕዝቤንም ከእኔ በታች የሚያስገዛልኝ።
3 አቤቱ፥ እርሱን ታውቀው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ታስብለት ዘንድ የሰው ልጅ ምንድር ነው?
4 ሰው ከንቱን ነገር ይመስላል፤ ዘመኑ እንደ ጥላ ያልፋል።
5 አቤቱ፥ ሰማዮችህን ዝቅ ዝቅ አድርጋቸው ውረድም፤ ተራሮችን ዳስሳቸው ይጢሱም።
6 መብረቆችህን ብልጭ አድርጋቸው በትናቸውም፤ ፍላጾችህን ላካቸው አስደንግጣቸውም።
7 –
8 እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም ከብዙ ውኆች፥ አፋቸውም ምናምንን ከሚናገር፥ ቀኛቸው የሐሰት ቀኝ ከሆነ፥ ከባዕድ ልጆች እጅ አስጥለኝ።
9 አቤቱ፥ አዲስ ቅኔ እቀኛልሃለሁ፤ አሥር አውታር ባለው በገና እዘምርልሃለሁ።
10 ለነገሥታት መድኃኒትን የሚሰጥ፥ ባሪያውን ዳዊትን ከክፉ ሰይፍ የሚያድነው እርሱ ነው።
11 አድነኝ፥ አፋቸውም ምናምንን ከሚናገር፥ ቀኛቸውም የሐሰት ቀኝ ከሆነ፥ ከባዕድ ልጆች እጅ አስጥለኝ።
12 ልጆቻቸው በጕልማስነታቸው እንደ አዲስ አትክልት የሆኑ፥ ሴቶች ልጆቻቸውም እንደ እልፍኝ ያማሩና ያጌጡ፤
13 ዕቃ ቤቶቻቸውም የተሞሉ በየዓይነቱ ዕቃ የሚሰጡ፥ በጎቻቸውም ብዙ የሚወልዱ፥ በማሰማርያቸውም የሚበዙ፥
14 ላሞቻቸውም የሚሰቡ፤ ቅጥራቸውም መፍረሻና መውጫ የሌለው፥ በአደባባዮቻቸውም ዋይታ የሌለ፤
15 እንደዚህ የሚሆን ሕዝብ የተመሰገነ ነው፤ እግዚአብሔር አምላኩ የሆነ ሕዝብ ምስጉን ነው።
የዳዊት የምስጋና መዝሙር።
1 አምላኬ ንጉሤ ሆይ፥ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ፥ ስምህንም ለዘላለም ዓለምም እባርካለሁ።
2 በየቀኑ ሁሉ እባርክሃለሁ፥ ስምህንም ለዘላለም ዓለምም አመሰግናለሁ።
3 እግዚአብሔር ታላቅ ነው እጅግም የተመሰገነ ነው፤ ለታላቅነቱም ፍጻሜ የለውም።
4 ትውልደ ትውልድ ሥራህን ያመሰግናሉ፥ ኃይልህንም ያወራሉ።
5 የቅድስናህን ግርማ ክብር ይናገራሉ፥ ተኣምራትህንም ይነጋገራሉ።
6 የግርማህንም ኃይል ይናገራሉ፥ ታላቅነትህንም ይነጋገራሉ፥ ብርታትህንም ይነጋገራሉ።
7 የቸርነትህን ብዛት መታሰብ ያወጣሉ፥ በጽድቅህም ሐሤትን ያደርጋሉ።
8 እግዚአብሔር ርኅሩኅና መሓሪ ነው፥ ከቍጣ የራቀ፥ ምሕረቱም ብዙ ነው፤
9 እግዚአብሔር ለሚታገሡት ቸር ነው። ምሕረቱም በሥራው ሁሉ ላይ ነው።
10 አቤቱ፥ ሥራህ ሁሉ ያመሰግኑሃል፥ ቅዱሳንህም ይባርኩሃል።
11 የመንግሥትህን ክብር ይናገራሉ፥ ኃይልህንም ይነጋገራሉ፥
12 ለሰው ልጆች ኃይልህን የመንግሥትህንም ግርማ ክብር ያስታውቁ ዘንድ
13 መንግሥትህ የዘላለም መንግሥት ናት፥ ግዛትህም ለልጅ ልጅ ነው።
14 እግዚአብሔር በቃሎቹ የታመነ ነው፥ በሥራውም ሁሉ ጻድቅ ነው፤ እግዚአብሔር የተፍገመገሙትን ሁሉ ይደግፋቸዋል፥ የወደቁትንም ያነሣቸዋል።
15 የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፤ አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ።
16 አንተ እጅህን ትከፍታለህ፥ ሕይወት ላለውም ሁሉ መልካምን ታጠግባለህ።
17 እግዚአብሔር በመንገዱ ሁሉ ጻድቅ ነው በሥራውም ሁሉ ቸር ነው።
18 እግዚአብሔር ለሚጠሩት ሁሉ፥ በእውነት ለሚጠሩት ሁሉ ቅርብ ነው።
19 ለሚፈሩት ምኞታቸውን ያደርጋል፥ ልመናቸውንም ይሰማል ያድናቸዋልም።
20 እግዚአብሔር የሚወድዱትን ሁሉ ይጠብቃል፤ ኃጢአተኞችንም ሁሉ ያጠፋል።
21 አፌ የእግዚአብሔርን ምስጋና ይናገራል፤ ሥጋም ሁሉ ለዘላለም ዓለም የተቀደሰውን ስሙን ይባርክ።
የሐጌና የዘካርያስ መዝሙር።
1 ሃሌ ሉያ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን አመስግኚ።
2 በሕይወቴ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፤ በምኖርበት ዘመን ሁሉ ለአምላኬ እዘምራለሁ።
3 ማዳን በማይችሉ በሰው ልጆችና በአለቆች አትታመኑ።
4 ነፍሱ ትወጣለች ወደ መሬቱም ይመለሳል፤ ያን ጊዜ ምክሩ ሁሉ ይጠፋል።
5 የያዕቆብ አምላክ ረዳቱ የሆነ ተስፋውም በአምላኩ በእግዚአብሔር የሆነ ሰው ምስጉን ነው፤
6 እርሱም ሰማይንና ምድርን ባሕርንም፥ በእነርሱ ያለውንም ሁሉ የፈጠረ፤ እውነትን ለዘላለም የሚጠብቅ፤
7 ለተበደሉት የሚፈርድ፥ ለተራቡ ምግብን የሚሰጥ ነው። እግዚአብሔር የታሰሩትን ይፈታል፤
8 እግዚአብሔር የወደቁትን ያነሣል፤ እግዚአብሔር ዕውሮችን ጥበበኞች ያደርጋቸዋል፤ እግዚአብሔር ጻድቃንን ይወድዳል፤
9 እግዚአብሔር ስደተኞችን ይጠብቃል፤ ድሀ አደጎችንና ባልቴቶችን ይቀበላል፤ የኃጢአተኞችንም መንገድ ያጠፋል።
10 እግዚአብሔር ለዘላለም ይነግሣል፤ ጽዮን ሆይ፥ አምላክሽ ለልጅ ልጅ ነው። ሃሌ ሉያ።

የሐጌና የዘካርያስ መዝሙር።
1 እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ መዝሙር መልካም ነውና። ለአምላካችን ምስጋና ያማረ ነው።
2 እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን ይሠራል፥ ከእስራኤልም የተበተኑትን ይሰበስባል።
3 ልባቸውን የቈሰሉትን ይፈውሳል፥ ሕማማቸውንም ይጠግናል።
4 የከዋክብትንም ብዛት ይቈጥራል፥ ሁሉንም በየስማቸው ይጠራቸዋል።
5 ጌታችን ታላቅ ነው፥ ኃይሉም ታላቅ ነው፥ ለጥበቡም ቍጥር የለውም።
6 እግዚአብሔር የዋሃንን ያነሣል፥ ኃጢአተኞችን ግን እስከ ምድር ድረስ ያዋርዳል።
7 ለእግዚአብሔር በምስጋና ዘምሩ፥ ለአምላካችንም በመሰንቆ ዘምሩ፤
8 ሰማዩን በደመናት ይሸፍናል ለምድርም ዝናብን ያዘጋጃል፤ ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል፤ ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም።
9 ለሚጠሩት ለቍራዎች ጫጩቶች ለእንስሶችም ምግባቸውን ይሰጣል።
10 የፈረስን ኃይል አይወድድም፥ በሰውም ጭን አይደሰትም።
11 እግዚአብሔር በሚፈሩት፥ በምሕረቱም በሚታመኑት ይደሰታል።
12 ኢየሩሳሌም ሆይ፥ እግዚአብሔርን አመስግኚ፥
13 ጽዮንም ሆይ፥ ለአምላክሽ እልል በዪ፤ የደጆችሽን መወርወሪያ አጽንቶአልና፥ ልጆችንም በውስጥሽ ባርኮአልና።
14 በወሰንሽም ሰላምን አደረገ፥ የስንዴንም ስብ አጠገበሽ።
15 ነገሩን ወደ ምድር ይሰድዳል፥ ቃሉም እጅግ ፈጥኖ ይሮጣል።
16 አመዳዩን እንደ ባዘቶ ይሰጣል፤ ጉሙን እንደ አመድ ይበትነዋል፤
17 በረዶውን እንደ ፍርፋሪ ያወርዳል፤ በበረዶውስ ፊት ማን ይቆማል?
18 ቃሉን ልኮ ያቀልጠዋል፤ ነፋሱን ያነፍሳል፥ ውኆችንም ያፈስሳል።
19 ቃሉን ለያዕቆብ፥ ሥርዓቱንና ፍርዱን ለእስራኤል ይናገራል።
20 ለሌሎች አሕዛብ ሁሉ እንዲህ አላደረገም፥ ፍርዱንም አልገለጠላቸውም። ሃሌ ሉያ።

የሐጌና የዘካርያስ መዝሙር።
1 ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን ከሰማያት አመስግኑት፤ በአርያም አመስግኑት።
2 መላእክቱ ሁሉ፥ አመስግኑት፤ ሠራዊቱ ሁሉ፥ አመስግኑት።
3 ፀሐይና ጨረቃ፥ አመስግኑት፤ ከዋክብትና ብርሃን ሁሉ፥ አመስግኑት።
4 ሰማየ ሰማያት፥ አመስግኑት የሰማያት በላይም ውኃ።
5 እርሱ ብሎአልና፥ ሆኑም፤ እርሱም አዝዞአልና፥ ተፈጠሩም፤ የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑት።
6 ለዘላለም ዓለም አቆማቸው፤ ትእዛዝን ሰጠ፥ አያልፉምም።
7 እባቦች ጥልቆችም ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ከምድር አመስግኑት፤
8 እሳትና በረዶ አመዳይና ውርጭ፥ ቃሉን የሚያደርግ ዐውሎ ነፋስም፤
9 ተራሮች ኰረብቶችም ሁሉ፥ የሚያፈራም ዛፍ ዝግባም ሁሉ፤
10 አራዊትም እንስሳትም ሁሉ፥ ተንቀሳቃሾችም የሚበርሩ ወፎችም፤
11 የምድር ነገሥታት አሕዛብም ሁሉ፥ አለቆች የምድርም ፈራጆች ሁሉ፥
12 ጕልማሶችና ቈነጃጅቶች፥ ሽማግሌዎችና ልጆች፤
13 የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ፤ ስሙ ብቻውን ከፍ ከፍ ብሎአልና፥ ምስጋናውም በሰማይና በምድር ላይ ነው።
14 የሕዝቡንም ቀንድ ከፍ ከፍ ያደርጋል፤ የቅዱሳኑንም ሁሉ ምስጋና ወደ እርሱ ለቀረበ ለእስራኤል ልጆች ሕዝብ ከፍ ከፍ ያደርጋል። ሃሌ ሉያ።

1 ሃሌ ሉያ። ለእግዚአብሔር አዲሱን ቅኔ ተቀኙለት፤ ምስጋናው በቅዱሳኑ ጉባኤ ነው።
2 እስራኤል በፈጣሪው ደስ ይበለው፥ የጽዮንም ልጆች በንጉሣቸው ሐሤትን ያድርጉ።
3 ስሙን በዘፈን ያመስግኑ፥ በከበሮና በመሰንቆም ይዘምሩለት።
4 እግዚአብሔር በሕዝቡ ተደስቶአልና፥ የዋሃንንም በማዳኑ ከፍ ከፍ ያደርጋልና።
5 ቅዱሳን በክብር ይመካሉ፤ በምንጣፋቸውም ላይ ሐሤትን ያደርጋሉ።
6 የእግዚአብሔር ምስጋና በጕሮሮአቸው ነው፤ ሁለት አፍ ያለውም ሰይፍ በእጃቸው ነው፥
7 በአሕዛብ ላይ በቀልን በሰዎችም መካከል ቅጣትን ያደርጉ ዘንድ፤
8 ንጉሦቻቸውን በሰንሰለት፥ አለቆቻቸውንም በእግር ብረት ያስሩ ዘንድ፤
9 የተጻፈውን ፍርድ ያደርጉባቸው ዘንድ። ለቅዱሳን ሁሉ ይህች ክብር ናት። ሃሌ ሉያ።
1 ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ አመስግኑት፤ በኃይሉ ጠፈር አመስግኑት።
2 በችሎቱ አመስግኑት፤ በታላቅነቱ ብዛት አመስግኑት።
3 በመለከት ድምፅ አመስግኑት፤ በበገናና በመሰንቆ አመስግኑት።
4 በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት።
5 ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑት፤ እልልታ ባለው ጸናጽል አመስግኑት።
6 እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን። ሃሌ ሉያ።

ilovejesus1.com

My name is Eden Fessehaye and i build ilovejesus1.com website for everyone to have access to the bible and audio bible as well.  There is Amharic, Tigrigna and English bible.  Also, the English bible can be translated to any languages for everyone to have access to...

Trust in Christ and receive Him as your Savior.

Christ is ready. “Here I am! I stand at the door and knock. If anyone hears my voice and opens the door, I will go in” (Revelation 3:20). Receive him now. “Yet to all who received him, to those who believed in his name, he gave the right to become children of God”...

You must repent and ask God for forgiveness.

“He who conceals his sins does not prosper, but whoever confesses and renounces them finds mercy” (Proverbs 28:13).  Forgiveness is promised. “If we confess our sins, he is faithful and just and will forgive us our sins and purify us from all unrighteousness” (1 John...

Jesus Christ died and rose again for our sins.

Jesus Christ died in our place. “But God demonstrates his own love for us in this: While we were still sinners, Christ died for us” (Romans 5:8). He is the way to new life. “Therefore, if anyone is in Christ, he is a new creation; the old has gone, the new has come!”...

Sin separates you from God

Everyone has sinned. “For all have sinned and fall short of the glory of God” (Romans 3:23). Sin brings death. “For the wages of sin is death” (Romans 6:23). “For it is by grace you have been saved, through faith and this not from yourselves, it is the gift of God-not...

Recognize that God loves you

“For God so loved the world that he gave his one and only Son, that whoever believes in him shall not perish but have eternal life” (John 3:16). He has new life for you. “I have come that they may have life, and have it to the full” (John 10:10).

The light of Jesus

Then Jesus again spoke to them, saying, “I am the Light of the world; he who follows Me will not walk in the darkness, but will have the Light of life.” (John 8:12, NASB) While I am in the world, I am the Light of the world.”...

Second Coming of Christ

Revelation 7:14 - “...they are the people who are coming out safely through the terrible tribulation. The blood of the Lamb has washed and made white their robes.” Revelation 19:7 - “They will be Christ's bride and will have...